የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ረቡኒ መጽሐፍ – የኢየሱስ ወዳጅነት

የዲ/ን አሸናፊ መኰንን ገጽ
እሑድ  ግንቦት ፫፣  ፳፻፮ ዓ/ም
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
                                  የኢየሱስ ወዳጅነት
ዮሐንስ ወንጌሉን ሲጽፍ ራሱን፡– «ኢየሱስ ይወደው የነበረ» በማለት ጠቅሷል፡፡ መጠሪያው እንዲሆን የፈለገው የኢየሱስ ክርስቶስንወዳጅነት ነው፡፡ የፍቅር በረሃ በሆነችው፣እየወደድናቸው ብዙዎች በራቁን ዓለም ላይ የኢየሱስ ክርስቶስን ፍቅር እንደ መስማት ነፍስን በሐሤት የሚያፍለቀልቅ ነገር የለም፡፡ ይህ ዮሐንስ በሌላ ስፍራ ላይ፡– «ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊትከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ. በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻው ወደዳቸው» (ዮሐ. 131) በማለት ተናግሯል፡፡ ከሰዎች ወገን የነገ ወዳጃችን ማን መሆኑን በርግጠኝነትመናገር አንችልም፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ገና ባልኖርንበት ዘመን እንኳ ይወደናል፡፡ የእርሱ ፍቅር በሁኔታ፣ በምክንያት፣ በጊዜ የተደገፈ ሳይሆን ከመለኮታዊውህልውናው ጋር ለዘላለም የፀና ነው፡፡
ወድቀን ሲያነሣን፣በድለን የንስሐ ዕድል ሲሰጠን፣ ስንሸሸው ሲከተለን ብዙ ጊዜ «ለምን ወደድከኝብለነዋል፡፡ እኛ ብቻ ሳንሆን በየዘመናቱየነበሩ ሰዎች ሁሉ ይህን ጥያቄ ጠይቀዋል(ሚል. 12)፡፡ እርሱ ግን በምክንያትተደግፎ ሳይሆን በራሱ ፍቅር ይወደናል፡፡ የፍቅር ጀማሪ እኛ አይደለንም፡፡ እርሱ አስቀድሞ ወደደን ተብሎ ተጽፎአል(1 ዮሐ. 410)፡፡ ስለወደደን ወደድነው እንጂ ስለወደድነው አልወደደንም፡፡ ወንጌሉን የጻፈው ዮሐንስ ስሙን ለመጥቀስ አልደፈረም፡፡ በሌላ ስፍራ ላይም እንደ ጻፈው፡– «ኢየሱስ ይወደው የነበረው» በማለት ስለ ራሱ ተናግሯል፡፡ ማንም ሰው ሊሰማ የሚወደው ነገር ቢኖር ስሙን ነው፡፡ መጽሐፍ ሲጽፍም የገዛ ስሙን ፊደል አይገድፍም፡፡ ደጋግሞ የሚያየው ስሙን ነው፡፡ ዮሐንስ ግን «ኢየሱስ ይወደው የነበረ» የሚለውን እንደ ማዕረግና እንደ ተጸውዖ < /span>በስሙ ላይ ደርቦ ጻፈና ስሜ ይህ ነው አለ፡፡

ጌታዬ
መግደላዊት ማርያም ሞቶም «ጌታዬ» ትለዋለች፡፡ሞቶ እንኳ ጌታዋ እንደሆነ አምናለች፡፡ ኦ፣ እርሱ እንዲህ ለሚሸነፉለትይሸነፋል፡፡ በጣም የምናከብራቸው ሰዎች ተይዘው ሲታሠሩ፣ በፍርድ ሲገደሉ በቀድሞ አጠራራችን ሳይሆን በተለየ የንቀት አጠራር እንጠራቸዋለን፡፡ ማንንም የምናከብረውይዞ ሲገኝ ብቻ ነው፡፡ የተሸነፈን በቀድሞ ክብሩ አናከብረውም፡፡ ለጊዜው የተሸነፈ የሚመስለውን፣ ይነሣል ብላ ያላመነችውን ጌታዬ ማለቷ ይደንቃል፡፡ እኛ ትንሣኤውን ያመንን ከእርሷ ይልቅ ጌታዬ ልንለው ይገባናል፡፡ ለእርሱ ያለን ፍቅርና አክብሮትም መቀጣጠልናመንደድ  ይገባዋል፡፡ አሁንም ጌታዋ ነው፡፡ አላፈረችበትም፡፡ ሞቱ ለእርሱ ያላትን ክብር አልቀነሰባትም፡፡ ብዙዎችን ያሰናከለ ሞቱ አላሰናከላትም፡፡ ሞቶም በፍቅሩ የገዛት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡
  ብዙ ሰዎች፡ዮሐንስ በመቃብሩ ስፍራ ስለ አንዲት ሴት ይዘግባል፤ማርቆስ ግን ስለ ብዙ ሴቶች ይዘግባል(ዮሐ. 2011-18 ማር. 161)፡፡ ስለዚህ ታሪኩ ልክ
አይደለም ይላሉ፡፡ ነገር ግን ይህ ወንጌላውያኑ ከተለያየ አቅጣጫ ትንሣኤውን መዘገባቸው እንጂ ታሪኩ መቃረኑን አያሳይም፡፡ዮሐንስ ስለ እነዚያ ሁሉ በመዘገብ አሳቡ እንዲበታተንበት አልፈለገም፡፡ መሻቱ፡በጽናት ኢየሱስ ክርስቶስንየምታገኝ የአንዲት ሴት ስዕልን ማሳየት ነው፡፡ በዚህ ምክንያት የዮሐንስና የማርቆስ ዘገባ የተለያየ ይመስላል፡፡ መግደላዊትማርያም ግን፡– «አናውቅም» (ዮሐ. 202) በሚለው ንግግሯ ከእርሷ ጋር ሌሎችም እንዳሉ ገልጣለች፡፡ አራቱም ወንጌላውያን ትንሣኤውን ቢዘግቡም ትንሣኤውን ያዩት ከተለያየ አቅጣጫ ነበር፡፡ ይህ የትንሣኤውን ሙሉ ገጽታ ለማየት በብዙ ጠቅሞናል፡፡አንድን ነገር ከተለያየ አራት አቅጣጫ ማየት ሙሉ ሥዕልን ያሳያልና፡፡
ሞቱን እንዳመኑ
ትንሣኤውን አላመኑም
«ስለዚህ ጴጥሮስና ሌላው ደቀ መዝሙር ወጥተው ወደ መቃብሩ ሄዱ፡፡ ሁለቱም አብረው ሮጡ፤ ሌላው ደቀ መዝሙርም ከጴጥሮስ ይልቅ ፈጥኖ ወደፊት ሮጠና አስቀድሞ ከመቃብሩ ደረሰ፤ ዝቅም ብሎ ቢመለከት የተልባ እግሩን ልብስ ተቀምጦ አየ፤ ነገር ግን አልገባም፡፡ ስምዖን ጴጥሮስም ተከትሎት መጣ፤ ወደ መቃብሩም ገባ፤ የተልባ እግሩ ልብስ ተቀምጦ አየ፤ ደግሞሞ በራሱ የነበረውን ጨርቅ ለብቻው በአንድ ስፍራ ተጠምጥሞ እንደነበር እንጂ ከተልባ እግር ልብስ ጋር ተቀምጦ እንዳልነበረአየ፡፡ በዚያን ጊዜ አስቀድሞ ወደ መቃብር የመጣውም ሌላው ደቀ መዝሙር ገባ አየም፤ አመነም ከሙታን ይነሣ ዘንድ እንዲገባው የሚለውን የመጽሐፉን ቃል ገና አላወቁም ነበርና፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ወደ ቤታቸው ሄዱ» (ዮሐ. 203-10)፡፡
ስምዖን ጴጥሮስና ዮሐንስ፣ መግደላዊት ማርያም ያመጣችውን የመሰረቁን ዜና ገና ሲሰሙ የአፏን ቃል ሳትጨርስ ወደ መቃብሩ  ስፍራ ገሰገሱ፡፡ ዮሐንስ  በዕድሜ ገና ጎበዝ ስለ ነበር ወደ መቃብሩ ስፍራ ቀድሞ ደረሰ፡፡ ነገር ግን ፈጥኖ ቢደርስም ወደ ውስጥ ግን አልገባም፡፡ ነገሩ ምን ይሆን? የሚለውን ለማጣራት ወደ መቃብሩ አልዘለቀም፡፡ አንደኛ በመድረሱ ብቻ ረክቶ ቆመ፡፡ አንደኛ የወጣበት ሩጫ ግን ምንም ፋይዳ የሌለው ከንቱ ሩጫ ነበር፡፡ ስምዖን ጴጥሮስ ግን በሽምግልና አቅሙ እያለከለከ ደረሰ፡፡ በሩጫው ሁለተኛ ቢወጣም ከዮሐንስ ይልቅ ወደ መቃብሩ ውስጠኛ ክፍል ዘልቆ በመግባት የመግነዙን ጨርቅ እያገላበጠ የኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ አለመኖሩን ተረዳ፡፡ በዚህ ጊዜ ዮሐንስ ተከትሎ ገባ፡፡ መግደላዊትማርያም የነገረቻቸው እውነት መሆኑን አመኑ፡፡ ልብ አድርጉ ያመኑት ግን ትንሣኤውን ሳይሆን ቅዱስ ሥጋው መወሰዱን ነው፡፡ ያመኑት በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ሳይሆን በጠላቶቹ የክፋት ኃይል ነው፡፡ አለመኖሩን ካረጋገጡ በኋላ ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡
ሦስተኛዋና የመጨረሻዋሯጭ መግደላዊት ማርያም ግን ከእነርሱ ኋላ ብትደርስም ኢየሱስ ክርስቶስንካላገኘሁ አልንቀሳቀስም ብላ በመቃብሩ ስፍራ ፍለጋዋን ቀጠለች፡፡ዝቅ ብለን እንደምናነበው ኢየሱስ ክርስቶስንያገኘችው ይህች ሴት ናት፡፡ አንደኛ የመጣውም ሁለተኛ የደረሰውምአላገኙትም፡፡ የመጨረሻዋሯጭና ቆራጧ ሴት ግን ኢየሱስ ክርስቶስንአገኘችው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚገኘው አንደኛ ለወጡት ሳይሆን ለሚፈልጉትናቆርጠው ለወጡት ነው፡፡ አንደኛ በመድረሳቸው የሚመኩ በእግዚአብሔር ቤት ብዙ ዘመን ያስቆጠሩ ሰዎች ዛሬም ኢየሱስ ክርስቶስንአላዩትም፡፡ ምንም የሚመኩበት የሌላቸው ግን እነርሱ አይተውታል፡፡ እርሱ የሚገለጸው በብርቱ ለሚፈልጉትናጸንተው ለሚፈልጉት ነው (ማቴ. 201-16)፡፡ በእግዚአብሔር ቤት ዛሬም ሦስት ዓይነት ሰዎች አሉ፡
ማወቅ የማይፈልጉ
ማረጋገጫ የሚፈልጉ
መዳን የሚፈልጉ
1-ማወቅ የማይፈልጉ
ዮሐንስ በጉብዝናውታግዞ አንደኛ ደረሰ፡፡ ነገር ግን በመቃብሩ ደጆች ላይ ቆመ እንጂ ወደ ውስጥ ዘልቆ ማወቅ አልፈለገም፡፡ በቀዳዳ እያየ እዚያው ቀረ፡፡ በእግዚአብሔር ቤትም ገና በማለዳ እንደመጡ የሚያስቡ ደጃፉ ላይ የቆሙ ነገር ግን መንፈሳዊውንምሥጢር ጠልቆ ማወቅ የማይፈልጉ እግዚአብሔር የሚገኘው በሞኝነት ነው በሚል እሳቤ የሚኖሩ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ስለ እግዚአብሔርማንነት ስለ ክርስቶስ ሥራ የማወቅ ምንም ዓይነት ፍላጎት የሌላቸው በአንደኝነታቸው ብቻ ረክተው የተቀመጡ ናቸው፡፡ እውቀትን ይሸሻሉ፤ የሚያውቁትንም ሰዎች ይሸሻሉ፡፡ ባሕልና ሃይማኖትንመለየት እስኪያቅታቸው ተቀላቅሎባቸዋል፡፡ የሃይማኖት አድናቂ እንጂ የእግዚአብሔር ወዳጅ አይደሉም፡፡ እነዚህ ሰዎች ካወቁ ተጠያቂ የሚሆኑ የሚመስላቸው፣ ካወቅን እንሳሳታለንየሚል አስተሳሰብ ያሰራቸው እግዚአብሔርን በመገለጡ ሳይሆን በመጋረጃ ሊያመልኩት የሚፈልጉ ናቸው፡፡
ለእምነት ግን እውቀት ገባር ነው፡፡ ያወቅነውን እንወደዋለን፣ የወደድነውንእናምነዋለን፡፡ እግዚአብሔርንም የምናምነው ስንወደው ነው፤ የምንወደውም ስናውቀው መሆኑን እነዚህ ሰዎች አልተገነዘቡም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል የእውቀትን አስፈላጊነት ሲገልጽ፡– «ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል፤ አንተም እውቀትን ጠልተሃልና» (ሆሴ. 46) ይላል፡፡ የዘላለም ሕይወትም ከእውቀት ጋር የተያያዘ መሆኑን ጌታችን በጌቴሴማኒጸሎቱ ገልጧል፡– «እውነተኛ አምላክ ብቻ የሆንህ አንተን የላክኸውንምኢየሱስ ክርስቶስን ያውቁ ዘንድ ይህች የዘላላም ሕይወት ናት» (ዮሐ. 173)፡፡ ጳውሎስም እግዚአብሔር በመታወቅ የሚመለክ አምላክ መሆኑን ገልጧል፡፡ለምን? ስንል እውነት ነውና፡፡ ሰይጣን ግን ተከታዮቹ እንዳያውቁት ዓይናቸውንካሳወረ በኋላ ይመለካል፡፡ለምን? ስንል ሐሰት ነውና (2ቆሮ. 44)፡፡ እግዚአብሔርየማወቂያ መሣሪያ የሆነውን አእምሮ የሰጠን እውቀት አስፈላጊ ስለሆነ ነው፡፡ ስለዚህ ተፈጥሮ በራሱ የእውቀትን አስፈላጊነትይተርክልናል፡፡ በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ በልማድ መመላለስ፣ የጠለቀውንየእግዚአብሔርን አሳብ አለመረዳት ከመንግሥቱ በአፍኣ /ውጭ/ ያደርገናል፡፡
…….ይቀጥላል…..
ረቡኒ
በዲ/ን አሸናፊ መኰንን
የመጀመሪያ እትም ሚያዝያ 2002 ዓ/ም
አድራሻ – 0911 39 35 21/0911 67 82 51
ፖ.ሳ.ቁ. 62552
አ.አ. ኢትዮጵያ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ