የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ረቡኒ /ክፍል2

 ምድር ብዙ ነገሮችን ተሸክማለች ፣ የአምላኳን ሞት ግን መታገሥ አልቻለችም ። ትንሣኤውንም መደበቅ አቅቷት ተናውጣለች ። ነገሥታትና ጠቢባን ሁሉ ለሞት ተገዝተዋል ፣ ሞት ግን በትንሣኤ ተሸንፏል ። ሰው ከሞት ላያድን ንግሥናን ለምን ይፈልጋል ? እግዚአብሔር ታላቅ ኃያሉን በትንሣኤ ገልጧል ። በትንሣኤው ያመኑ የብርሃን ልጆች ናቸው ። ከምድር ነገሥታት ፣ ከዓለም ጠቢባን ይበልጣሉ ። መግደላዊት ማርያም ትጓዝ የነበረው ይህን ሁሉ አስባ አልነበረም ። ጌታዋን አልቅሳ ለመጨረሻ ጊዜ ለመሰናበት ነበር ። አልዓዛርን እንዳስነሣ አይታለች ፣ እርሱ እንደሚነሣ ግን አላመነችም ። እኛም ትንሣኤውን አምነናል ፣ በእርሱ ሥልጣን እንደምንነሣ በማመን ኀዘናችንን ገደብ ልንሰጠው ይገባል ። ትንሣኤ ኀዘንን ያቋረጠ ፣ የልቅሶን ጅረት የከፈለ ነው ። ጌታ ግን ወደ ኋላ የሚተርኩት ሳይሆን ዛሬም ለዘላለምም ሕያው ነው ። የሃይማኖት ምሥጢራት በልኩ አልገቡኝም ብለን ከእግዚአብሔር ቤት መራቅ አይገባም ። እግዚአብሔር ንጋትንና እውቀትን በጊዜው ያመጣል ። ባወቅነው መጠን ስንታመን የማናውቀውን ነገር እያወቅን እንመጣለን ። እውቀት ጠል ሁኖ አለመኖር ፣ ገናም ለማወቅ መኖር እርሱ የብርሃን መገኛ ነው ። ወደ እግዚአብሔር ቤት በትንሣኤ እግሮች ይገሠግሣሉ ፣ ቅኔው ዝማሬው ብዙ ምሥጢር ያለው ነው ፤ የሚረዱት ግን ጥቂቶች ናቸው ። ብዙ ብናውቅም የምንባረከው በማመን ነው ።

መናወጦች ሦስት ጊዜ ይሆናሉ ። ጠቢባን ይህ ዓለም የታላቅ ፍንዳታ ውጤት ነው ይላሉ ። ስለ ነውጥ የሚያምኑት በፍጥረት መገኘት ላይ ነው ። እግዚአብሔር ግን በዝምታ ሰማይና ምድርን ፈጠረ ። መናወጥ ግን ሦስት ጊዜ ይሆናል ። ክርስቶስ ሲሞት ፣ ክርስቶስ ሲነሣ ፣ ክርስቶስ ዳግም ሲመጣ ። ክርስቶስ ሲሞትና ሲነሣ ምድር ተናወጠች ። በዳግም ምጽአት ግን ሰማይም ይናወጣል ። በክርስቶስ ሞት መናወጡ የሆነውን መሸከም አለመቻሉ ነው ። ሲነሣ መናወጡ ደግሞ ኃይሉን ማውራቱ ነው ። በዳግም ምጽአት መናወጡ ግን ለአዲሱ ሰማይና ምድር ስፍራ መልቀቁ ነው ። በሕይወታችንም ሦስት መናወጦች ይሆናሉ ። ለዓለም ስንሞትና መስቀሉን ለመሸከም ዝቅ ስንል ቤተሰቦቻችን መናወጥ ይጀምራሉ ። አእምሮውን ቢያጣ ፣ አቅሉን ቢስት ነው ይላሉ ። ለእግዚአብሔር ለመኖር ስንነሣ ዓለም ይናወጣል ። ከሀዲ ነው ፣ ውሸታም ነው ይላል ። አሮጌውን ጥለን አዲሱን ብቻ ስንይዝም ፣ ለዘመናት በውስጣችን የኖረው ድካም ተቀርፎ ሲወድቅ ፣ ወደ ክርስቶስ ድል ስንደርስ በፈታኙ ዓለም መናወጥ ይሆናል ።
መግደላዊት ማርያም በእነዚህ ተአምራት ተስባ የመጣች ሳትሆን በፍቅሩ ተነክታ የመጣች ናት ። ብዙ ተአምራት እነዚያን ሰቃዮች አላሳመናቸውም ።በመጨረሻው ቀን ቅዱስ እንደሚቀደስ ርኩሱም እንደሚረክስ በዕለተ ዓርብም እንደዚያ ነበረ ።
የሮማ ወታደሮችና የካህናት ሎሌዎች ፣ ሮማዊው ጲላጦስና ኤዶማዊው ሄሮድስ ለወትሮ የሚዋደዱ አልነበሩም ። ክርስቶስን በመግደል ግን አንድ ሆኑ ። በጌታችን ሞት ብዙ አስደናቂ ነገሮች ተከናውነዋል ። በሊቀ ካህናቱ የሚመራው የአይሁድ ሸንጎ በቀን የማይገኘው በሌሊት ችሎት አስችሏል ። የሄሮድስን ሥልጣን ለማሳነስ የመጣው ጲላጦስና ግዛቱ የተከፈለበት ሄሮድስ በዚያ ቀን ፍቅር ሆኑ ። ለቄሣር ሞት የሚለምኑ አይሁድ የቄሣር ወዳጅ አይደለህም በማለት ክርስቶስን እንዲሰቅል ጲላጦስን አግባቡት ። በርባን መፈታቱ ፣ የቀኙ ወንበዴ/ፈያታዊ ዘየማን ገነት መግባቱ አስደናቂ ነው ። በልደቱ ካህናት ቀርተው እረኞች ተገኙ ፣ በሞቱም ወንበዴ ገብቶ ሊቃነ ካህናት ሐናና ቀያፋ ተኰነኑ ። የሚጠበቁት ቀርተው የማይጠበቁት ሲገኙ ይህ የወንጌል ጠባዩ ነው ።
መግደላዊት ማርያም ሰንበትን እቤቷ አሳለፈች ፣ ጌታም በመቃብር አሳለፈ ።ሰንበት የእግዚአብሔርን ቀን ለእግዚአብሔር የምንሰጥበት ነው ። የብሉይን ሰንበት አክብራ በማግሥቱ በአዲሱ ሰንበት ክርስቶስን አከበረች ። በሁለቱም ኪዳን የከበረች ሴት ሆነች ። ሚሊኒየም ላይ መገኘት ብዙዎች የሚመኙት ነው ፣ በሺህ ዓመት አንዴ ስለሚመጣ የሚያገኙት ጥቂቶች ናቸው ። ከዚያ በሚበልጥ ሁለቱ ኪዳናት አንዱ አንዱን ሲያከብርና ሲረካከብ መግደላዊት ማርያም ተገኘች ። የመጨረሻውን የብሉይ ኪዳን ፋሲካ አክብራ የዘላለሙን ፋሲካ ማክበር ጀመረች ። በሚቀጥለው ዓመት በእስራኤላዊነት ፋሲካን ብታስበው በክርስቲያንነት ግን አዲሱን ፋሲካ ታከብራለች ። የብሉይ ፋሲካ የሥጋ ነጻነት የአዲሱ ፋሲካ የነፍስ ነጻነት የተገኘበት ነው ።
ቀትር የጨለመው ፣ እኩለ ሌሊት የበራው በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነው ። ቀትር ፀሐይ አናት ላይ የምትወጣበት ፣ ሙሉ ቀን ተብሎ የሚጠራበት ፣ የብርሃን ድምቀትና ትኩሳት ያለበት ነው ። እኩለ ሌሊት ሰማዩ አጋም የሚመስልበት ፣ ጥቁር ግምጃ ለብሶ የሚያስጨንቅበት ነው ። ክርስቶስን በታሪካችን ስንሰቅል ሥልጣኔው አለማወቅ ፣ ብርና ወርቁም ዝገት ይሆናሉ ።ሥልጣኔም ገንዘብም እንደማያድን ይህ ዘመን ምስክር ነው ። ስለ ጨረቃ ላይ ሆቴል በሚወራበት ዘመን ገና እጃችሁን ታጠቡ መባል የሚገርም ነው ። ያለ እግዚአብሔር የሚጓዙ ሲከልሱ ይኖራሉ ። የደመቀውን ሥልጣኔ ማንም አያቆመውም ፣ በሰዓታት ዓለም ከዓለም እንጓዛለን ፣ ኢኮኖሚያችን ጣራ ነክቷል ፣ ዓለም አንድ መንደር ሁኗል የሚባለው ሁሉ እንደ ቀትር ይጨልማል ። ያለ ማስተዛዘኛ ሁሉም ነገር ድንገት ያበቃል ። ክርስቶስን ለሚያስሱም እኩለ ሌሊት ብርሃን ይሆናል ። ወደ ኋላ ለመመለስ ጉልበት ፣ ወደፊት ለመሄድ ወኔ ያጡ ፣ ሁሉም ነገር የከዳቸው ፣ አለመኖር የሚሰማቸው ፣ ወልደው መሐን የሆኑ ፣ አፍቅረው ስድብ የተሸከሙ ፣ የእኔ ነገር አብቅቷል ብለው ለራሳቸው የዕድር ጡሩንባ የሚነፉ ፣ የእርሱ ነገር አብቅቷል ተብሎ ሁሉ ተስፋ የቆረጠባቸው ፣ የትላንቱን እምነት አይደለም ወንድነት አጥተው ትጥቃቸው የላላባቸው ፣ የወረደባቸው በረዶ ያደነዘዛቸው ፣ ቢያፈጡ መልሶ ችግራቸው የሚያፈጥባቸው ለእነዚህ ጨለምተኞች የትንሣኤ ብርሃን ይበራላቸዋል ። ይህን ብርሃን የሮማ ክንድ ሊከለክለው አይችልም ። ዓርብ ዕለት የወጡ ወረኞች ቀኑ ጨለመባቸው ፣ እሑድ ዕለት የወጡ ምስክሮች ግን ጨለማው በራላቸው ። ወረኞችን ጨለማ ፣ ምስክሮችን ብርሃን ይከተላቸዋል ።
የመቶ አለቃው ሞቱን አይቶ አመነ ፣ ትንሣኤውን ያዩ ወታደሮች ግን አላመኑም ወይም እንዳመኑ አልተጻፈልንም ። እግዚአብሔርን በዝምታው የሚያከብሩት እንዴት የታደሉ ናቸው ? ለበደላችን ይህም ሲያንስ ነው እያሉ በእሳት ውስጥ የሚዘምሩ ቡሩካን ናቸው ። አድርግልን ሳይሆን ያደረግህልን እንዴት ድንቅ ነው ! የሚሉ አማንያን ናቸው ። ክርስቲያን ገና እንዲደረግለት አይኖርም ። የዘላለም ሕይወት ሆኖለታል ። የሰው ልጆች ልብሱን ሲገፉት ፀሐይ ዕርቃኑን አላሳይም ብላ ጨለመች ። ሰው ሲደፍር ፀሐይ አፈረች ። ዛሬም ሰው ለሰው መርዝ ሲበጠብጥ አትክልት ግን ንጹሕ አየር ይለግሳሉ ። ለመርዙ ማርከሻም ላም ወተት አለኝ ትላለች ። በግፍ የተገደለውን ጌታውን ከመቃብሩ አልለይም በማለት ውሻው ይጠብቀዋል ። ምነው ዛሬ የጌታችን ውሾቹ እንኳ በሆንን ።
ሰው በፍጥረቱ ክቡር ፣ በአኗኗሩ ግን ርካሽ መሆኑን ዕለተ ዓርብ ይናገራል ። ሲወለድ በበረት ከብቶች አውቀውት ሰዎች በር ዘጉበት ። ሲሰቀል ፀሐይ አዝናለት ያዳናቸው ጨከኑበት ። ለሰው የተደረገውን ግዑዛንም ይመሰክራሉ ። ጨካኙ የባቢሎን ንጉሥ ሰዓዳም ሁሴን ፣ የቀሬናው/የሊቢያው ጋዳፊ ሲያዙና ሲንገላቱ ልባችን አዝኗል ። የክፉዎች ሞት እንኳ ካሳዘነ የመድኃኔ ዓለም ሞት እንዴት ያሳዝናል ። መላእክት እስከ ዛሬ አመስግነው በማያውቁት አዲስ ቅኔ አመሰገኑ፡- የታረደው በግ ኃይልና ባለ ጠግነት ጥበብም ብርታትም ክብርም ምስጋናም በረከትም ሊቀበል ይገባዋል አሉ።” /ራእ. 5፡12 ።/ ትንሣኤ አዲስ ዝማሬን በሰማይ ያመጣ ነው ። ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን “ክርስቶስ ተነሣ” ብላ ማወጇ ተገቢና ከሰማይ የወረሰችው ነው ።

የማትችለው መግደላዊት ማርያምና መግደል የሚችሉት መላእክት ከጌታቸው ትዕግሥት ጋር ተባበሩ ። ጌታው የቻለውን ሎሌው አይቆጣውምና ። እግዚአብሔር ሎሌዎቹን ያከብራል ። ነቢዩ ኤልያስ ለእግዚአብሔር ቀንቶ ሰማይን ለጎመ ፣ ምድርን ገዘተ ። እግዚአብሔርም ከአሳቡ ጋር ተስማማ ። ያ ሕዝብ ግን አልመለስም ባለ ጊዜ እየራበው ከሚክደኝ እየበላ ይካደኝ ብሎ ኤልያስን ተገለጥላቸው አለው ። ቅዱስ ገብርኤልም ዘካርያስን ዱዳ ቢያደርግ እግዚአብሔር ተስማማ ። በሞቱ ግን መላእክትን ገረመመ ፣ እንዲታገሡም አስጠነቀቀ ። ልደቱና ሞቱ ይመሳሰላሉ ። የተወለደው ሊሞት ነውና ። በልደቱ ድንግልን እንዳያስደነግጥ መልአኩ ገብርኤል ታዘዘ ወይም በትዕግሥት አናገራት ። በሞቱ ዕለትም ገዳዮችን እንዳያጠፉ መላእክት ቅንዓታቸውን አብርዱ ተባሉ ። ልደቱና ትንሣኤውም ተመሳሳይ ናቸው ። በሁለቱም መላእክት ነበሩ ። በሁለቱም በዝግ በር ወጥቷል ። በሕቱም ድንግልና የተወለደ ፣ በሕቱም መቃብር ተነሣ ። ላብ ከሰውነት ሲወጣ ቆዳን እንደማይቀድ ፣ ብርሃን በመስተዋት ሲያልፍ መስተዋት እንደማይሰበር የአምላክ ልጅም ከድንግል ሲወለድ ማኅተመ ድንግልናዋን አልለወጠም ። በዝግ መቃብርም ሲወጣ የሮማውያንን ማኅተም አልቀደደም ።
መግደላዊት ማርያም በትንሣኤ ቀን “ረቡኒ” አለችው ። አዳኜ የሚለው ምስጋና ይገባው ነበረ ። እመቤታችን ግን በብሥራቱ ቀን፡- ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች ፥ መንፈሴም በአምላኬ በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች አለች ። ሉቃ. 1፡47 ። ልደትና ትንሣኤ ፣ ትንሣኤና ምጽአት ሲናበቡ ይኖራሉ ።
አቤቱ የትንሣኤህን ብርሃን በልባችን አብራ ።
ይቀጥላል
የመስቀሉ ገጽ 8ለ
ሚያዝያ 21 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ