መግቢያ » ከመጻሕፍት » ረቡኒ » ረቢኒ /5

የትምህርቱ ርዕስ | ረቢኒ /5

 ትንሣኤ ላይ ሴቶችና መላእክት ይታወሳሉ ። የተዘነጉ ሲሆኑ ድርሻቸው ትልቅ ነው ። ጌታ ሲነሣ አብረው እንዲነሡ አደረገ ። መግደላዊት ማርያም በአካል ባላገኘውም ፍቅሩን አስታውሳለሁ ብላ ፣ ወደፊት ይህን አድርግልኝ ባልለውም ያደረገልኝ በቂ ነው በማለት ወደ መቃብሩ ገሰገሰች ። ክርስቶስ ግን ሞት ድንበሩ አይደለም ። ከሞትም የሚጀምር የትንሣኤ አምላክ ነው ። አካሉም ፍቅሩም ሕያው ነው ። ገና ሊሰጠንም ያኖረናል ። እርሱ በስጦታውና በፍቅሩ ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው ።
ምድር የከዳችውን ፣ መሬትን ያረክሳል ተብሎ ከፍ አድርገው መስቀል ላይ ያንጠለጠሉትን ዮሴፍ ዘአርማትያስ ፍልፍል መቃብሩን ለቀቀለት ። ጌታችን በዮሴፍ ቤት እንደ ተስተናገደ አልተጻፈም ፣ በመቃብሩ ውስጥ ግን ሦስት ቀን አደረ ። በእስራኤላውያን ባሕል መቃብር ትልቅ ዋጋ አለው ። ዛሬ በታወቀ የአይሁድ መቃብር ለመቀበር በሚሊየን የሚቆጠር ዶላር ለአንድ መቃብር ይከፈላል ። ዮሴፍ ዘአርማትያስ ይህን ለጌታ ተወለት ። በቁም ብዙ ጋባዦች ነበሩ ፣ ዛሬ አልተገኙም ። ማንም በማይገኝበት ቀን የተገኘ ፣ ማንም በማይሰጥበት ቀን የሰጠ ዮሴፍ ዘአርማትያስ ነው ። ክርስቶስን እንዲህ ሲወዳጀው ጠላት ይነሣብኛል ብሎ አልፈራም ። በሁሉ ቦታ ክርስቶስ ወዳጅ አለውና ከአይሁድ ሸንጎ ሰባ አባላት ካለው ፍርድ ቤት ዮሴፍና ኒቆዲሞስ የክርስቶስ ወዳጆች ነበሩ ። ዮሴፍ በአዲስ መቃብር ክርስቶስን ቀበረው ። እርሱ ማንም ባልተቀመጠበት ማኅፀን ያደረ ነው ፣ ማንም ባልተቀበረበት መቃብርም ተቀበረ ። በዚያ ማኅፀን ከዚያ በኋላ ፍጡር አልተቀመጠም ፣ በዚህ መቃብርም ፍጡር አላረፈም ። በእግዚአብሔር ዙፋን ፍጡር አይቀመጥም ። የቁምም የሞትም ወዳጅ መሆን የማይችሉ ምስኪኖች ናቸው ። ትምህርት በከንቱ አይሰጥም ። ኒቆዲሞስና ዮሴፍ በስውር ተምረው በግልጥ መሰከሩ ። የከበበ ሲበተን ተገኙ ። ብቻ ፈሪዎችንም እንደ አቅማቸው በድብቅ አስተምሩ ፣ አንድ ቀን ጎበዝ ሲፈራ እነርሱ ይደፍራሉ ።

ዮሴፍ መቃብሩን ለጌታው ለቀቀ ። ከዚያ በኋላ ወደ መቃብሩ አልተመለሰም ። መግደላዊት ማርያም ግን ሽቱ ይዛ በሦስተኛው ቀን ተመለሰች ። ወንዶች የመጨረሻው ሰዓት ላይ ቢገኙ አስታውሰው መሄድ አይሆንላቸውም ። ሴቶች ግን ሲያስቡ ይኖራሉ ። አካልን እንጂ ትዝታንም መቅበር ፣ ሥጋን እንጂ ሥራን መቅበር አይገባም ። በዚህ ዓለም ላይ ሁሉም ነገር ሲሞት ጥሩ ትዝታ ይኖራል ። የሞቱት ትዝታቸው ያዋራናል ።
የክርስቶስ ትንሣኤ መንግሥት ፈርሶ መንግሥት የጸናበት ነው ። የዲያብሎስ መንግሥት ፈርሶ የእግዚአብሔር መንግሥት በሰው ሥጋና ነፍስ የሰለጠነበት ነው ። መንግሥታት ሲዋጉ ያለውን ትርምስ መግደላዊት ማርያም አታውቅም ነበር ። በምናውቀው ነገር ውስጥ ብዙ የማናውቀው ነገር አለ ። በመንፈሳዊው ዓለም ውስጥ ስላለው ምሥጢር እውቀታችን አነስተኛ ነው ። አለማወቃችን ግን የመጠቀም ዕድላችንን አይነፍገንም ። ቴሌቪዥን እንዴት እንደሚሠራ ብዙዎቻችን እውቀቱ የለንም ። አለማወቃችን ግን እንዳንጠቀም አያደርገንም ።
ክርስቶስን መግደል ራስን በፈቃድ ለዲያብሎስ መንግሥት አሳልፎ መስጠት ነው ። ሰባት አጋንንት የወጡላት መግደላዊት ማርያም ግን ያንን ክፉ ኑሮ ስለምታውቅ እንደገና መቀለድ አልፈለገችም ። አዲሱን ሕይወት አክብራ ያዘች ። ፈርዖን ከለቀቀ በኋላ ተከታትሎ ለመያዝ ይመጣል ። በእምነት ካልተሻገርን ይይዘናል ። ከፊተኛው የኋላው ቀንበር ይከብዳል ። ያላዩ በእሳት ለመጫወት ይደፍራሉ ። ሰይጣን ክፉ ገዥ ነው ፣ የሚያመልኩትን እንኳ የሚያስጨንቅ ነው ። አዋርዶ የሚገዛ ክብር የለሽ ነው ።
ጌታችን ሲነሣ የተገነዘበትን ጨርቅ ትቶ ተነሥቷል ፣ ልብሱን ደግሞ በመስቀሉ ሥር ወታደሮች ዕጣ ተጣጥለው ወስደውታል ። በትንሣኤ የለበሰው ልብስ የብርሃን ልብስ ነው ። የብርሃን ልብስ የማይወልቅ ቀሚስ ነው ። እርሱ ብቻውን አልተነሣም ፣ ብዙ ሙታንን ይዞ ተነሣ ። ቤት ለቤት እየሄዱ ትንሣኤን እንዲሰብኩ ክርስቶስ አሥነሣቸው ። ሞትን ያዩ ቍጣን አይፈሩም ።
ወደ መግደላዊት ማርያም እንገሥግስ ። ትንሣኤ በር ዘግቶ ፣ ምሥጢሩ አላሳልፍም አለን ። የክርስቶስ ትንሣኤ ሆይ እባክህን መንገድ ልቀቅልን ። የማታልቅ ትንታኔ ሆይ ፣ ሞትን ያሸነፍህ የእግዚአብሔር ክንድ ሆይ በትንሽ ጭንቅላት ትልቅ ምሥጢርን ማሰስ አንችልምና ለማለፍ ፍቀድልን ።
ከሞታችሁ ከሦስት ቀንም በኋላ የሚወዳጃችሁ ወዳጅ ብታገኙ ደስ ይላችኋል ። መግደላዊት ማርያም ከሦስት ቀንም በኋላ ወዳጅ ነበረች ። ሽቱ ክቡር ነው ፣ ያለ ሰዓቱ ከሆነ ግን የሚጣል ነው ። ሰዓትን ማወቅ ከሽቱ በላይ ነው ። ብዙዎች ሽቱ ይዘዋል ፣ ሰዓቱ ግን አልፏል ። ፍቅራችሁን ለመግለጥ ፣ የተዘረጉላችሁን እጆች ዛሬ ለመሙላት ፣ ያሳደጉአችሁን ለማድነቅ ሰዓቱ አሁን ነው ። ተጠቀሙበት ። ለሽቱ እንጂ ለሰዓት ዋጋ ለምን አትሰጡም ?  ሴቶች ሞቶም እንዲህ የወደዱት ቢነሣ እንዴት ይወዱት ይሆን ? ሞቱን ያመኑ ሴቶች ትንሣኤውን ማመን አልቻሉም ። ሞት የሰው ሁሉ ዕጣ ነው ፣ መሞት ችሎታ አይጠይቅም ። ትንሣኤ ግን ችሎታ ይጠይቃል ። ሞትን አምኖ ትንሣኤን አለማመን ከባድ ነው  ። የሚገርመው እኛ ሞትንም ትንሣኤንም አለማመናችን ነው ። የምንሠራው ክፋት ሞት እንዳለብን የዘነጋን ያስመስልብናል ። ነገሮች ሲሞቱ እግዚአብሔር እንደሌለ ያህል የሚሰማን ትንሣኤን አለማመናችንን ያሳያል ። ክርስቶስ ሲቀበር የእነ መግደላዊት ማርያም ተስፋም አብሮ ተቀብሮ ነበር ። ሞት ፣ ድንጋይ ፣ ወታደሮች ይታሰቡአቸው ነበረ እንጂ ሕይወት ፣ መልአክ ፣ ብሥራት አልታሰባቸውም ነበር ። የእምነታችንን ያህል ሳይሆን የታማኝነቱን ያህል ስለ ሰጠን ለእግዚአብሔር ምስጋና ይገባዋል   ።
የሰው ኀዘን በትንሹ ይረጋጋል ። ቅዱስ ሥጋውን ሽቱ ከቀቡ በኋላ ለመጽናናት ፈልገዋል ። ከስንብት በላይ ትንሣኤ ያረጋጋል ። የእኛ ኀዘንም በትንሹ ይጽናናል ። ድሀው ሲያሳዝነን ፣ እጅ እግሩ የተቆረጠው ሰው ሲያራራን አሥር ሣንቲም ስንጥል እንረጋጋለን ። ኀዘናችን ሰውዬውን አንድ ቦታ አድርሶ ሳይሆን ድቃቂ ሣንቲም ጥሎ ይረጋጋል ። ወትሮም የምንሰጠው ሕሊናችንን ፀጥ ለማሰኘት እንጂ ለወደቀው ሰው አዝነን አይደለም ።
ታሪክ ያለመደው ፣ ምድራዊ ሥልጣንና ሀብት ያልቻለው አንድ ነገር ቢኖር የክርስቶስ ከሞት መነሣት ነው ። እነ ፈርዖን ፣ እነ ናቡከደነፆር ፣ እነ ዳርዮስ ፣ እነ እስክንድር ፣ እነቄሣር እንደ ሞቱ ቀርተዋል ። እነ ሶቅራጥስ ፣ እነ ፕላቶን ፣ እነ አርስቶትል ፣ እን ፊሎ በመቃብር እንደ ተዘጉ ይኖራሉ ። ታሪክ ያለመደውን ነገር እነ መግደላዊት ማርያም መቀበል ፣ ለነገሥታትና ለጠቢባን ያልተቻለውን አማን አማን ማለት ከበዳቸው ።
ድንጋዩን ማን ያንከባልልልናል ? ሲሉ ተንከባሎ አገኙት ። በዚህ አንዱ ጭንቀታቸው ቀለለ ። ክርስቶስ ተነሣ የሚለውን ብሥራት ለመቀበል ከበዳቸው ። ድንጋዩን ማን ያንከባልልልናል ለሚል ልብ ሞትም ተንከባሏል ብሎ መቀበል ከባድ ነው ። የክርስቶስ ሥጋ ተሰርቋል የሚል አሳብ አደረባቸው ። ክፉ ገዥዎች የሚፈሩትን ሰው ከገደሉት በኋላ መቃብሩ ተከታይ እንዳያፈራ ደብዛው እንዲጠፋ ያደርጋሉ ። ሴቶች እንዲህ የሆነ መሰላቸው ። ተሰርቋል የሚለው አሳብ በካህናት አለቆች በእነ መግደላዊት ማርያም አእምሮ ስፍራ አገኘ ። ሰይጣን አሳብ ይዘራል ፣ ሰው ሥጋ ያለብሰዋል ።
ሴቶች ባዶውን መቃብር እንዲጎበኙ በመላእክት አጋፋሪነት ተጠየቁ ። ባዶ መሆኑ አስደነገጣቸው ። ቅዱስ አካሉ ተኝቶ ሊያገኙት ፈልገዋል ። የመሰረቁ አሳብ ልባቸውን ገዛው ። መልአኩ ግን ተነሥቷል ብሎ አወጀላቸው ። መላእክትን እንዳይሞቱ አድርጎ የፈጠረው እርሱ በሥጋ ሞተ ። በሥጋ ሞተ ። በመለኮቱ ቢሞትማ አይነሣም ነበር ። የምንነሣው ከሞት ቀጥሎ ትንሣኤ ስላለ ሳይሆን አምላካችን የማይሞት ስለሆነ ነው ።
ትንሣኤ ማንንም የማሳቀቅ ዓላማ የለውም ፣ ዓላማው የወደቁትን መፈለግ ነው ። ስለዚህ ይህን ዜና አስቀድመው ለጴጥሮስ እንዲነግሩ ፣ ወደ ካደው ሰው ተላኩ ። ትንሣኤ የካደውን ጴጥሮስ ፣ አሳዳጁን ጳውሎስ ገንዘብ ያደረገ ነው ። ክርስቶስ ባይነሣ እነዚህን ሁለት ዕንቁዎችን ቤተ ክርስቲያን አታገኝም ነበር ። የትንሣኤው የምሥራች በመላእክት ፣ በሴቶች ቢሰበክም በሐዋርያት ቀጣይነት ያገኛል ።
መግደላዊት ማርያም መቃብሩ ባዶ መሆኑን ከተናገረች በኋላ  ጌታዬን ወስደውታል እያለች ትጨነቅ ነበር ። ክርስቶስ ተነሥቷል ብለው ከሰበኩ በኋላ ለሚጨነቁ ምሳሌ ናት ። ሰብካችሁ ለምትጨነቁም ክርስቶስ ተነሥቷል ። እንኳን ደስ አላችሁ ። በትንሣኤ የብርታት ድምፅ እንጂ የመፈራረድ ቋንቋ የለም ።
ይቀጥላል
የመስቀሉ ገጽ 8 ሠ
ሚያዝያ 24 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም