“እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ የዋይታና የመራራ ልቅሶ ድምፅ በራማ ተሰማ ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች የሉምና ስለ ልጆችዋ መጽናናትን እንቢ አለች ።” ኤር. 31፡15 ።
አንድ ትልቅ አባት ነበሩ ። እውቀትም መንፈሳዊነትም የነበራቸው ነበሩና የበቁ አባት ተብለው ሲጠሩ እሰማለሁ ። ምክራቸው እጅግ አሳራፊ ፣ ከእግዚአብሔር የተሰጣቸው ጸጋም በትሕትና የተሽሞነሞነ ነውና ትልቅ ውበት አላብሶአቸው ነበር ። በዚያ በዘጠና ዓመታቸው ከዓመታት በፊት የተነጋገርነውን ሁሉ ያስታውሳሉ ። ጊዜው ከዛሬ 23 ዓመት በፊት ነው ። እኒህን አባት ሳልጠይቃቸው ረጅም ጊዜ ሆኖኝ ስለነበርሁ ወደ በአታቸው የምሄደው እያፈርሁ ነበር ። እርሳቸው በቀን ብዙ ሰው የሚያስተናግዱና መንገድ የሚመሩ ስለነበሩ ሰው አጥተዋል ፣ ብቻቸውን ናቸው ብዬ ሳይሆን ለእኔው ስለቀረብኝና የእግዚአብሔርን ሰው መራቅ ተገቢ ስላልሆነ ነው ። እንደ ሱነም ሴት በቤቴ እንዳልቀበላቸው ቤት የለኝም ። በቤታቸው ግን በልቤ እቀበላቸዋለሁ ። ታዲያ እያፈርሁ ጎንበስ ብዬ ጉልበት ሳምሁ ። እርሳቸውም እንደ ፀሐይ የሚያበራውን ፊታቸውን አሳዩኝና ባረኩኝ ። “የት ጠፋህ ?” አሉኝ ። እኔም “አገልግሎት በዝቶብኝ ነው” አልኳቸው ። በርግጥ አገልግሎት በዛልኝ ነው የሚባለው ብለው ሌላ መምህርም አርመውኛል ። ታዲያ አገልግሎት በዝቶ ነው የጠፋሁት ስላቸው ትክዝ ብለው ሰሙኝና ። “እግዚአብሔር የነገረኝ ነገር ነበር” አሉኝ ። እኔም ጆሮዬን ከልቤ ጋር አንቅቼ ልሰማቸው ፈለግሁ ። “ማስተማርህ መልካም ነው ። ይህ ሕዝብ ግን በትምህርት ብቻ አይለወጥም” ብሎኛል አሉኝ ። እኔም ደንግጬ ለመስማት ተዘጋጀሁ ። “ፌዘኛና አልምጥ ስለሆነ እውቀት ያለው ንጉሥ እያስተማረና እየቀጣ ካልመራው አይሰማም ብሎኛል” አሉኝ ። ይህ ነገር ከድካም አረፍ ስል ፣ ስንዴ ዘርተን ገለባ ስናጭድ ፣ ክርስትናን ሰብከን መተራረድን ስናተርፍ አስታውሰዋለሁ ። ያ እውቀት ኖሮት የሚያስተምር ፣ ሥልጣን ኑሮት ፍትሕ የሚሰጥ ንጉሥ ማን ይሆን እላለሁ ?
ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች ። ይህች ራሔል የያዕቆብ ሚስት ራሔል ከሆነች እርስዋ በወሊድ ምክንያት ሞተች እንጂ ልጆችዋ ዮሴፍና ብንያም አልሞቱባትም ። በርግጥ በግብጽ ምድር የታነቁት ሕፃናት ትውልዶቿ ናቸውና ከቀኑ በፊት አዝናለች ፣ የፍቅር አንጀቷ ስለ እነርሱ ተላውሷል ማለት ይሆናል ። ይህች ራሔል በግብጽ የባርነት ዘመን የነበረች ከሆነች ድርስ እርጉዝ ሁና ጡብ የሚሠራበትን ጭቃ ስትረግጥ ልጇ ፈትለክ ብሎ ከማኅፀኗ ወጣ ። በዚህ ጊዜ ደንግጣ ብትቆም አስገባሪው፡- “እርገጭው ምን ይለዋል ፣ የሰው ደም እንደውም ያጠነክረዋል” አላት ። በዚህ ጊዜ “በዚህ ሰማይ የእስራኤል አምላክ የለምን!” ብላ እንባዋን ወደ ላይ ረጨችው ። የራሔልም እንባ መንበረ ጸባዖትን አራሰው ። እግዚአብሔርም ለፍትሕ ተነሣ ፣ እስራኤልም ከግብጽ ባርነት ነጻ ወጣ በማለት ታሪክና ትውፊት አጣቅሰው ትምህርተ አይሁድን አስሰው አባቶች ይነግሩናል ።
ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች ። ይህች ራሔል የዘመናት አልቃሾችን ፣ በልጅ ሞት የሚተክዙትን ወክላ የቆመች ናት ። እንባዋ የዘመናትን የልጆች ሞት ሲገልጥ ይኖራል ። በባቢሎን ምርኮም የእስራኤል ሕፃናት እንደ ጎመን ሲቀረደዱ ፣ እንደ ዛፍ ሲቆረጡ ይህች ራሔል ታወሰች ። ኤር. 31፡15 ። ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች ተባለ ። ሄሮድስም የቤተ ልሔም ሕፃናትን ሲፈጃቸው ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች በማለት ቅዱስ ማቴዎስ ያነሣታል ። ማቴ. 2፡17 ። ቅዱስ ማቴዎስ ያነሣት የመጀመሪያው መራራ ኀዘን መሆኑን ስለመግለጥ ነው ። ሁለተኛ ታሪክ መደገሙን ለማንሣት ነው ። ክፉ ታሪክ ሲደገም ሰው ካለፈው አለመማሩን ያሳያልና ያሳምማል ። ካለፈው ትርፍ እንዳልተገኘ ተገንዝቦ አሁንም ትርፍ የሌለው ነገር መሥራቱ ያሳዝናል ።
ራሔል ዛሬም ያሉትን ፣ በመላው ዓለም ስለ ልጆቻቸው የሚያለቅሱትን አባቶች እናቶች ትወክላለች ። በአገራችን ራሔል ጠፍታም ፣ ልቅሶዋም ነጥፎ አያውቅም ። የዘመናት አልቃሽ ሁና ዛሬም ትጮኻለች ። የዋይታና የልቅሶ ድምፅ በአርያም እየተሰማ ነው ። ባለፉት አርባ ዓመታት እንኳ ስንት ወጣት ረገፈ ። ቀይ ሽብርና ነጭ ሽብር እየተባባለ ስንቱ እንደ ወጣ ቀረ ። ሬሣው የሚያነሣው ጠፍቶ በአደባባይ ዋለ ። እርጉዞች ተገደሉ ፣ ብዙ ወጣቶች የት እንደ ደረሱ ሳይታወቅ ደብዛቸው ጠፋ ። በመቀጠል ለ17 ዓመታት በዘለቀ ጦርነት በሰሜኑ የአገራችን ክፍል ብዙ ወጣት ረግፎ ቀረ ። ይህም ምንም ትርፍ የሌለው የወንድማማቾች እልቂት ነበር ። በ1990 ዓ.ም. “የክፍለ ዘመኑ ኋላ ቀር ጦርነት” ተብሎ በተሰየመው በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል በተደረገ ጦርነት ትውልድ እንደ ወጣ ቀረ ። እነዚያ ወጣቶች እንዳጎደሉ የሚያውቀው ዛሬም ያ ቤተሰባቸው ብቻ ነው ። የእኛ የኢትዮጵያውያን ጸጋችን መርሳት ነውና ረስተናቸዋል ። ላለፉት አርባ ዓመታት ጥቁር ልብስ ያላወለቁ ፣ በኀዘን ምክንያት በሽተኛ የሆኑ ፣ አቅላቸውን ስተው ያበዱ ፣ አጉል ነዋሪ ሁነው የቀሩ ብዙ ራሔሎች አሉ ። በዚህ የደም ገንቦ ላይ እንጨምርበታለን ተብሎ አይታሰብም ነበር ። አሁንም እያትረፈረፍነው ነው ። አዎ ጣፋጩ ትረካችን “ኢትዮጵያ ማንንም ወርራ አታውቅም” የሚል ነው። ኢትዮጵያውያን ግን ሲተላለቁ የሚኖሩ ናቸው ። እስከ ሰባት ቤት ደም ከሚቃቡት ጀምሮ ያለ ምክንያት እስከሚፈጁት ወገኖች ድረስ የደም ጥምቀት በአገራችን የተለመደ ሁኗል ። ያለፈው ሳይካስ ሌላ ዕዳ እያመጣን ፣ የወለድናቸው ለአንድ ቀን እንኳ የሰላም ድምፅ እንዳይሰሙ አድርገን እያሸማቀቅናቸው ነው ።
ራሔል ኢትዮጵያ ስለ ልጆችዋ አለቀሰች ። በጠፍ ጨረቃ ፣ በውድቅት ሌሊት በራቸው ተንኳኩቶ ስለታረዱት ፣ በጎሣቸው ምክንያት ስለተፈጁት ምስኪኖች ልቅሶ በአርያም ተሰማ ። እግዚአብሔር ፍርድ ሲሰጥ ሰምተን እንዳልሰማን የሆነውን ፣ እኔን ካልነኩኝ ብለን ያለፍነውን ሁሉ የብይኑ በትር ያገኘናል ። ሁሉም ነገር ካለቀ በኋላ ወሬ ማሯሯጥ ጥቅም የለውም ። ንጹሕ ነኝ ብሎ ማሰብም ከንቱ ነው ። ማንን ነው የምንቀየመው ? ብለን ስንጠይቅ ገዳይም ሟችም ሁሉም ኢትዮጵያዊ ነው ።
“የገደለው ባልሽ የሞተው ወንድምሽ ፣
ኀዘንሽ ቅጥ አጣ ከቤትሽ አልወጣ ፤”
ሌላም ግጥም ትዝ ይለናል፡-
“አንጀቴ ተቆርጦ ከሆዴ ከወጣ ፣
እንግዲህ ሐኪሙ ምን ሊቀጥል መጣ ?”
አዎ ሁለት ነገሮች ያስፈልጋሉ ። የእኛ አባት መገለጥ ቀላል አይደለም ። ፍርድና ትምህርት ያስፈልጋሉ ። ከተመከርንበት የሕንዱ የነጻነት ታጋይ የነበሩት ማኅተማ ጋንዲ እንዲህ ብለው ነበር፡- “በምድር ላይ ብቻህን ብትቀር እንኳ ከግፈኞች ጋር አትተባበር ።”
እግዚአብሔር የመጽናናትን መንፈስ ይላክልን ። ላዘኑት የሚያረጋጋ መልአክ ይላክልን ። ልብ ይስጠን ።
“ጎዳናው ሳይጠበን አመል እያጋፋን ፣
አካሄዱ ቀርቶ አቋቋሙ ጠፋን ፤”
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 28 ቀን 2012 ዓ.ም.