መግቢያ » ከመጻሕፍት » ወዳጄ ሆይ » ሰላማዊ ኢየሱስ ክርስቶስ

የትምህርቱ ርዕስ | ሰላማዊ ኢየሱስ ክርስቶስ

 

ወዳጄ ሆይ !

መጻሕፍት የአእምሮ ምግብ ናቸው ። ሆድን አጥግቦ አእምሮን ባዶ ማድረግ የመንፈስ ረሀብ ያመጣል ። ውስጣቸው እየሞተ ያሉ ሰዎች ማሳያው ማንበብ ማቆማቸው ነው ። መጻሕፍት ስትገዛ የምትከፍለው ገንዘብ ለወረቀቱ እንጂ ለአሳቡ አይደለም ። በምድር እጅግ ደግ የሚባሉት እውቀታቸውን ሳይሰስቱ የሚሰጡ ጸሐፍት ናቸው ። የኪስ ምጽዋት የሚሰጡትን እያከበርህ የነፍስ ምጽዋት የሚሰጡትን ደራስያን አትናቅ ። ጌጥ ለመግዛት የማይከራከር መጽሐፍ ለመግዛት የሚከራከር ደካማ ትውልድ ነው ። ከሳንሱር ሕጎች በላይ የሚያሳዝነው የማይጽፉ ሰዎች የሚጽፉትን መተቸታቸው ነው ። የአሳብ ክብር በሌለበት የአገር ዕድገት አይታሰብም ። የራስህንና የሰዎችን ዋጋ የሚያሳውቁህ ደገኛ መጻሕፍት ናቸው ። 

ወዳጄ ሆይ !

በታላቅ ስቃይ ውስጥ ላሉ ወገኖች እግዚአብሔር የሚሰጣቸው ዕረፍት ሞት ይባላል ። ሞት የሰው ልጆች ሁሉ የሚከፍሉት ዕዳ ነው ። የሞትን ዕዳ እናት ለልጅዋ መክፈል አትችልም ። እርሱ ሞቶ አንተ አትቀርምና በጠላትህም ሞት ደስ አይበልህ ። ክርስትና በውስጣችን ትኩስ በነበረበት ዘመን ከባሕር ዳርቻ መዝናኛ ይልቅ የሰማይ ወደብ ይናፍቀን ነበር ። እግዚአብሔር የልብ ሀብት በመሆኑ ዕረፍት ፣ ተስፋ በመሆኑም ናፍቆት ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

ቁምነገረኛ ሰው በሕይወቱ መጻሕፍትን ያነባል ፣ በሞቱ እርሱ ራሱ ሲነበብ ይኖራል ። ሞት ስጋት የሚሆንብን ስላልተዘጋጀን ነው ። የክርስቶስ ምጽአት ለመቃረቡ ማሳያው ምጽአቱን ክርስቲያኖች ሲረሱ ነው ። አካልና ጥላ እንደማይለያዩ ሰውና ሞትም አብረው ይኖራሉ ። እግዚአብሔርን ስንከተል በጎነት ይከተለናል ። ከምትወደው ጋር ሺህ ዓመት ብትኖር እንኳ ከትልቅ መጽሐፍ ገና አንድ ገጽ ማንበብህ ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

እስከ ሽምግልና የሚከተልህ ወጣትነት ነው ። መርዛም ነገርን ማስወገድ ከተሠራበት በላይ ወጪ ያስወጣል ። ክፉዎች ቢሞቱም ክፋታቸው ሲያዋራን ይኖራል ። እጅግ ስስ መሆንህን ለማወቅ ከፈለግህ ማወቂያው የሰው ጠባይ ሲከብድህ ነው ። መወለድን ከተቀበልህ መሞትንም መቀበል አለብህ ። 

ወዳጄ ሆይ !

ካልሞትህ በቀር አትቁም ። መሮጥ ካልቻልህ መንፏቀቅም ጉዞ ነው ። ለበጎ ነገር ምቹ ጊዜ አትፈልግ ፣ ሰዓቱ አሁን ነው ። በዛሬው ዘመን ሰዎች በቃላቸው እብለት ፣ በሰውነታቸው ክፋት ተለማምደዋልና አንተ ግን በቃልህ እውነተኛ ፣ በኑሮህ ደገኛ ሁን ። ጥላቻ ከሚመርዝህ ፍቅር ቢያስጠቃህ ይሻላል ። ጠላትህ ከነጠቀህ ይልቅ በችግርህ ሰዓት ወዳጅህ አለመድረሱ ቆይቶ ይቆጫል ። በየትኛውም አገር የሚፈጸም ወንጀል ፍትሕን ዝቅ አድርጓልና ሊወገዝ ይገባዋል ። መጀመር መጨረስ ባይሆንም ለመጨረስ ግን አንድ ደረጃ መቀነስ ነው ። ለመብት መታገል መልካም ነው ፣ እውነተኛ ነጻነት ለማግኘት ግን ማደግ ወሳኝ ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

አንተ የምትጠላውን ሰው እግዚአብሔር እንደሚወደው አስብ ። ውድቀትህ የእግዚአብሔርን ጸጋ የምታይበት አደባባይ ነው ። ለበዛው ስህተታችን ጸጋው ባይበዛልን እንደ ሰዶም በሆንን ገሞራንም በመሰልን ነበር ። ብርሃን ጨለማን ይገፋል እንጂ እስከወዲያኛው አያርቀውም ፣ የአሁን ጸሎትህ ቢሰማም ሌላ ጥያቄ እንደሚመጣ እወቅ ። ጥላቻን በጥላቻ ለማጥፋት ስንነሣ በመተላለቅ እግዚአብሔር የሰጠንን ዕድሜ እናሳጥራለን ። ያለማወቃቸውን የሚያውቁ አላዋቂዎች ምሁራን ናቸው ። አላዋቂነታቸውን እንደ እውቀት የሚያዩ ሁሉንም ወንጀል የሚፈጽሙ ናቸው ። እውቀት በዓለም ላይ ያለኸው አንተ ብቻ አይደለህም በማለት ሌላውን አክብር ትልሃለች ። ድንቁርና ደግሞ በዓለም ላይ ያለኸው አንተ ብቻ ነህ በማለት ከፍ ያሉትን አዋርድ ትልሃለች ። 

ወዳጄ ሆይ !

በፍቅር አውሬንም ማልመድ ይቻላል ። ዓለም የጋራ ቤታችን መሆኗን ተረድተን ተደማምጠን መኖር አለብን ። ይቅርታ እንቅልፍ እንቢ ሲለን የምንመርጠው ሐቅ ሳይሆን የሁልጊዜ ጠባያችን መሆን ይገባዋል ። ዲያብሎስ ይህ ሁሉ የሚደክመው ብቻውን ላለ መኰነን ነው ፣ አንተስ ብቻህን መጽደቅ ቅር ብሎህ ያውቃል  ምሽቱ የበራችውን ፀሐይ ቢሸኝም የተሰወሩ ከዋክብትን ይገልጣል ፣ ችግርህም የማታውቃቸውን ደጎች ያሳይሃል ። ሰው በአንድ ቀን ንግግርና ትውውቅ አይመዘንም ። ቀኖች እየገፉ ሲመጡ የተደበቁ አመሎች ብቅ ማለት ይጀምራሉ።

ሰላማዊ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ሰላምህን ስጠን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ኅዳር 15 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም