መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ሰማያዊ ወግ » ሰማያዊ ወግ 11

የትምህርቱ ርዕስ | ሰማያዊ ወግ 11

ምእመኑ በጽድቅ ለሚሰማው ጌታ ተናገረ፡-

ጌታ ሆይ ! አንተ ካልሰጠኸው አንድ ቃል የሚጽፍ ፣ አንተ ካልረዳኸው የወደቀን የሚያነሣ ፣ አንተ ካልቀባኸው ተናግሮ የሚያጽናና ፣ አንተ ካልባረከው ሰባራን የሚጠግን ፣ አንተ ልቡን ካላረጠብከው ፍቅርን የሚሰጥ ፣ አንተ ካላረጋጋኸው የዘመንን ማዕበል የሚያሸንፍ ፣ አንተ ሁን ካላልከው ሰው መሆንን የሚያገኝ ማንም የለም ። ዓለም ተበጥብጣ ልትበጠብጠኝ ስትሻ ፣ ምን እንደሚፈልጉ የማያውቁ የሰው ልጆች አቅሌን ሊነሡኝ ሲነሣሡ ፣ የይሁዳ መሳም ጥርስ ሁኖ ሲያደማኝ ፣ የጴጥሮስ ክዳት የዓርቡን ሌሊት ሲያረዝምብኝ ፣ የቀድሞ ጉልበቴን ሳጣው ፣ መልኬን በፎቶ ስፈልገው ፣ ልቤን ማመን አቅቶኝ ስፈራው ፣ መሐላዬን ሳፈርስ ፣ ወስነው የመጡብኝን ወስኜ ማምለጥ ሲያቅተኝ ፣ በጥቅስ የምወደው ቃልህን ለመኖር ሲመርረኝ አንተ ግን ለእኔ መልካም ነህ !!

መሪውን ልምራህ ፣ ምሁሩን ላስተምርህ ስል ፣ የረዳኝን ሰው በችግሩ ስሳለቅ ፣ መልካሙን ሰው “ምስኪን” ብዬ ስጠራ ፣ አንተ ግን ከዚህ ማንነቴ ልታወጣኝ ትታገሠኛለህ ። በድጡ ላይ ስወድቅ ዝም ያሉኝ ፣ በማጡ ስነከር ከዚህ በኋላ አይወጣም ብለው ይስቁብኛል ። ነውሬን ክብሬ አድርጌ ስኖር ፣ ወደ ግብጽ ለመመለስም ከነዓን ለመድረስም አካፋይ መንገድ ላይ ስቆም አንተ ግን በርታ ትለኛለህ ። አንተን ለመውደድ ብዙ ውለታህን ለመቍጠር እነሣለሁ ፣ አንተ ግን ሳትቆጥር ወደኸኛል ። ለጥላቻ አቅም እንዳላስፈለገኝ ፣ ለፍቅር ግን አቅም ያሻኛል ። ዓለም ስም መስጠት ጠባይዋ ነው ። ሎቱ ስብሐት ላንተም ብዙ ስም ሰጥታሃለች ። በሬን ስዘጋ ጋኔን ጎታች ፣ ሰውን ስቀርብ ክብር የለሽ ትለኛለች ። ለሰው የኖርኩትን ላንተ ብኖር ቍጥሬ ከቅዱሳን አበው ነበር ። አማኑኤል ሆይ ከብርሃን በሚፈጥነው ረድኤትህ ድረስልኝ ።

የምሕረት አምላክም መለሰ፡-

ልጄ ሆይ !

ሳትታክት መለመን በእኔ ዘንድ እንደ ሰማዕትነት ይቆጠራል ፣ በሰው ዘንድ ጨቅጫቃ ያሰኛል ። ኃጢአት ሲስማማህ እንጂ ከቆረቆረህ የፈውስ ዋዜማ ላይ ነህ ። ማስተዋል መንገድን ያቀናል ፣ መጥኖ መናገር ያስከብራል ። መጨረሻውን ኃጢአት ያደረገ በደለኛ ይባላል ፣ መጨረሻውን ጽድቅ ያደረገ ኃጥእ ግን ጻድቅ ይሰኛል ። ችግሮች ወደ እኔ የምትጮህባቸው ርእሶች ናቸው ፣ ትልቁ ችግር ከእኔ መራቅ ነው ። ባልመጣው በረከት የመጡትን በረከቶች አትርሳቸው ። ላያልቅ የጀመረ ፈተና የለም ። እኔንም አልፎ ሊያጠፋህ የሚሻ ኃይለኛ አይገኝም ። ከሰዎች ላይ ጋኔን ከማውጣት ክፉ ምኞታቸውን ማውጣት ይከብዳል ። ሰው ከክፋቱ የበለጠ ጠላት የለውም ። ለውስጥ ሰዎች ሸካራ ለውጭ ሰዎች ግን ለስላሳ አትሁን ።

ልጄ ሆይ !

የሹመት ሞቱ ሺህ ነውና አትውደደው ። ስሜትህን መቆጣጠር አቅቶህም ሕዝብን የሚዋርድ ቃል አትናገር ። ያንተ ድርሻ መናገር ብቻ ነውና ለምን አልተቀበሉም ብለህ አትበሳጭ ። እኔ ለፈጠርኩት ዓለም ከእኔ በላይ አሳቢ አትሁን ። መሳትህ ለብዙዎች መሳት በር ይከፍታልና ለሚያዩህ ስትል በአቋምህ ጽና ። የሰውን አንደበት መቋቋም ከቻልህ ሌላው ፈተና ቀላል መሆኑን ተረዳ ። የሌላቸውን ጽድቅ ባንተ ላይ ይፈልጋሉና የሚሰድቡህን አትስማቸው ። የሚያምርህን ትተህ የሚያምርብህን ያዝ ። ሁሉ ከእኔ ነውና ሁሉን ለእኔ ክብር አድርግ ።

ልጄ ሆይ ! በተለዋዋጭ ዓለም ላይ ነህና በሚለዋወጡ ነገሮች አትደንግጥ ። እኔን ማየት ስትጀምር የሰዎችን ይሁንታ አታስስም ። የእኔ በር ክፍት ነውና የተዘጋውን የሰዎች በር አታንኳኳ ። በመሆን እንጂ በስልት መልካም አትምሰል ። ሁልጊዜ የምወድህ እኔ ኢየሱስ ክርስቶስ ነኝና ደስ ይበልህ ።

አሜን!!!

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ተፃፈ ሐምሌ 28 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም