መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ሰማያዊ ወግ » ሰማያዊ ወግ /5

የትምህርቱ ርዕስ | ሰማያዊ ወግ /5

የምእመን ድምፅ

ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ !

ነገን እያሰብኩ ዛሬን አበላሻለሁ ፣ ዛሬ ከሌለ ነገ እንደማይኖር እረሳለሁ ። ሰው መሆኔን እንዴት ላድርገው ? ሌላውን የመከርኩበት ምክር የእኔን ጭንቀት አይመክረውም ። የተናገርኩትን የምኖርበት የፈተና ሰዓት ሲመጣ ቀልሎ ከመገኘት አድነኝ ። ተድላዬ እግዚአብሔር ሆይ ! ከዚህ ማንነት እንዴት እወጣለሁ ? ሰው ከሰው ጋር እልህ ይጋባል ። እልህ ጣዖት አምልኮ ነው ። እኔ ግን ከራሴ ጋር እልህ እጋባለሁ ። ራሴንም በኃጢአት ጦር እወጋለሁ ። ነፍሴ የራሴ እስከማትመስለኝ ትቻታለሁ ። አንተ ግን ረጅሙን የክፋት ጉዞ ሳደርግ ፣ ቀጠሮዎቼን ታግሠህ ፣ በመንገዴ ሁሉ ሞት እንዳይቀድመኝ ሰስተህ ዛሬን አሳይተኸኛል ። ጠላቱን የሚወድድ ፣ የሚያሳዝነውን የሚያፈቅር እንዳንተ ያለ ማንም የለም ። ብጠጋህ ለጥቅሜ ነው ። ከማስፈልግህ ይልቅ አንተ ታስፈልገኛለህ ። እኔ ግን ያላንተ ለመኖር ሳስብ ያለ አየር ለመቆየት እያቀድሁ ነው ። አቤቱ ሆይ ! ዕፀ በለስ መምረሩን በልቼ ሳይሆን ተሰብኬ እንዳውቅ እርዳኝ ። ሞትን ሞቶ ከማወቅ እባክህ አድነኝ ።

ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ !

ያልተሰበሰቡ አሳቦቼ ፣ ዝርው የሆኑ ኀሊዮቶቼ ፣ ገደብ ያጡት ምኞቶቼ ዛሬን እንዳልኖር ያደርጉኛል ። ኑሮዬ በአሮጌው ጨርቅ ላይ አዲስ እራፊ መጣፍ ነው ። የመጣሁበትን መንገድ መልሼ እደግመዋለሁ ። ይህን ተራራ መዞር አይበቃኝም ወይ ? እላለሁ ። ያልታየኸው ነገር ግን በየዕለቱ በሥራህ የምትታየው ፤ አየሁህ የማትባለው ፣ አላየሁህም የማትባለው ፣ ድንቅ እግዚአብሔር ሆይ ብርታትህን እፈልጋለሁ ። የከበሩ አሳቦችን በውስጤ አኑር ፣ ዓለምን በከንቱነት ልኳ እንዳያት እርዳኝ ። የምጨነቀው ለሰባና ለሰማንያ ዓመት ሳይሆን ለዘላለም በምድር ላይ የሚኖር ሰው ዓይነት ነው ። ተደራጅቶ የመጣብኝን አሳብ ሁሉ በማይመከተው ክንድህ አርቀው ።

የመድኅን ክርስቶስ ቃል ይህ ነው !

ልጄ ወዳጄ ሆይ !

ቅዱስ መንፈስ በጸጸት ራሳቸውን ለሚጎዱ ፣ ከክርስቶስ ደም የተነሣ ያለውን ስርየት እያሳየ ዕረፍትን ይሰጣቸው ዘንድ ወደ ዓለም መጥቷል ። ራስን ብቻ መስማት ፣ በራስ አለማወቅ ተጠልፎ መውደቅን ያመጣል ። የአባቶችህን ምሳሌነት ተከተል ። ብርታታቸው ስንፍናህን ይውቀሰው ፣ ድካማቸው ተስፋህን ያድሰው ። ለስላሳ ጣዕም እንዳለው ዜማ ፣ በእርጋታ እንደሚፈስስ ውኃ ፣ በጥበብ እንደሚሳብ መረብ ፣ በትሕትና ጎንበስ ቀና እንደሚል ዛፍ ፣ በተመሥጦ እንደሚጠፋ ፈላስፋ ፣ ለነጽሮተ ሥሉሥ ቅዱስ እንደበቃ መናኝ በጸሎትና በቃሌ ወደ እኔ ልስብህ እፈልጋለሁ ። አንተ ግን የአምላክን ቀጠሮ በፍጡር ቀጠሮ ትሽራለህ ። ቆይ አይቼ ልምጣ ብለህ እዚያው ትከርማለህ ። ወደ ክፋት ግዛት እየገባህ ታስረህ ትጨነቃለህ ። የልደቴን ደስታ እያሰብህ ስጦታ ትለዋወጣለህ ፣ የሞቴን ዋጋ እየዘነጋህ ራስህን ለእኔ ለመስጠት ትሰስታለህ ። ከወሬ ሰዓትህ ቀንሰህ አትሰማኝም ። የምኞትህን ያህል እኔን አትወደኝም ። በድንኳንህ እልልታ እንዲሰማ ብዙ ጊዜ መጣሁ ። አንተ ግን የምትገዛውን ደስታ ፈለግህ እንጂ የምትገዛለትን ሐሤት አልፈለግህምና ተጎዳህ ።

ልጄ ወዳጄ ሆይ !

ያልገበሩ የአካልህ ግዛቶች ለእኔ እንዲገብሩ ሰዓቱ አሁን ነው ። ስንቶች ወዳጆችህ በየቀኑ በሞት እየተጠሩ ነው ። ሞት ዙሪያህን ሲዞርህ እንዴት አልነቃህም ? እኔ ስመጣ በዓላማህ ማማ ላይ እንዳገኝህ በርታ ። የምትበረታውም በጸሎት ፣ በቅዱስ ቃሌና በአባቶች ምክር ነው ። አንተ ተላላ ሆይ ! ገና በማኅፀን ሳሉ የሚሞቱ ጽንሶችን ፣ በተወለዱ በመጀመሪያው ቀን የሚያንቀላፉትን ጨቅላዎች ቍጠርና ብዙ ዘመን እንደ ቀረህ አታስብ ። ለዓይንህ የሞሉትን ሰዎች የምወስደው እንድትማር እንጂ እንድትማረር አይደለም ። ቅና ንስሐ ግባ ። ራስህን ከማሳደድ ወጥተህ ራስህን በእኔ አግኘው ። የሁልጊዜው አፍቃሪህ ፣ በተራራው በሸለቆው የማልለይህ አባትህ እግዚአብሔር እኔ ነኝ ።

ቀንህ በእኔ ይብራ !

ሰማያዊ ወግ / 5

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 14 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም