የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ሰባቱ ሀብታት

“የእግዚአብሔር መንፈስ ፥ የጥበብና የማስተዋል መንፈስ ፥ የምክርና የኃይል መንፈስ፥ የእውቀትና እግዚአብሔርን የመፍራት መንፈስ ያርፍበታል ። እግዚአብሔርን በመፍራት ደስታውን ያያል ። ዓይኑም እንደምታይ አይፈርድም፥ ጆሮውም እንደምትሰማ አይበይንም” ኢሳ. 11፡2-3
ስለ መሢሑ ከተነገሩ ትንቢቶች አንዱ ነው ። እነዚህ ሀብታትም ሰባት ሀብታት ናቸው ። ጥበብ ፣ ማስተዋል ፣ ምክር ፣ ኃይል ፣ እውቀት ፣ እግዚአብሔርን መፍራት ፣ በማየትና በመስማት አለመፍረድ ናቸው ። እነዚህ ሀብታት ጥንድ ፣ ጥንድ በመሆን ተቀምጠዋል ። ጥበብና ማስተዋል ፣ ምክርና ኃይል ፣ እውቀትና እግዚአብሔርን መፍራት በጥንድ ሲቀመጡ ፤ እንዳየና እንደ ሰማ አለመፍረዱ ለብቻው ተቀምጧል ። ጥበብ ያማረ ፍጻሜ ወይም ሥራን በውበት መደምደም ነው ። ጥበብ የሌለው ነገር ሁሉ የባከነ ነው ። ማስተማርም ፣ መምራትም ፣ መሥራትም ፣ መዳኘትም በጥበብ ሊሆን ይገባዋል ። እውቀትን የገፉ ሰዎች ጥበብን መግፋት አይችሉም ። ጥበብ ልብን የመማረክ አቅም አለው ። ጥበብ ደረቅ ንግግሮችንና ተግባራትን ያስቀራል ። የማይገባ ዋጋ እንዳንከፍል ከሚያግዘን ነገር አንዱ ጥበብ ነው ። ጥበብ ማለት ብልጠት ማለት አይደለም ። እውነትን በፍቅር የማሰረጽ አቅም ነው ።
ማስተዋል ከመናገር ከማድረግ በፊት ውጤቱን መገምገም ነው ። ማስተዋል ከትላንት ጉዳቶችና ከዕድሜ ልምድ የሚገኝ ሲሆን በዋናነትም የመንፈስ ቅዱስ ሀብት ነው ። ማስተዋል ነገሮችን ሁለት ጊዜ የማየት ዓይን ይሰጣል ።ማስተዋል ዛሬን ሳይሆን ነገን ፣ ራስን ሳይሆን ሰዎችን በቸር የሚያይ ነው ። በማስተዋል ውስጥ ፍጥነትና ቁጥብነት ተዋድደው ይሄዳሉ ። ማስተዋል አደጋን ባያስቀር እንኳ አደጋን የመቀነስ ትልቅ አስተዋጽዖ አለው ። ማስተዋል ጊዜያዊ ደስታን የሚንቅ ፣ ሰማይን አሻግሮ የሚመለከት ነው ።
ምክር ትልቅ የመንፈስ ቅዱስ ሀብት ነው ። ማንም ሰው መምከር አይችልም ። እንኳን መምከር ለመመከርም አቅም ያስፈልጋል ። ምክር በፍቅር ከረጠበ ልብ ውስጥ የሚወጣ የእውነት ወንዝ ነው ። ምክር ትልቅ ምጽዋት ነው ። ነገሥታትና ባለጠጎች ሳይቀር የሚፈልጉት ስጦታ ምክር ነው ። ምክር ሕይወትን ቀላል የማድረግ አቅም አለው ። ምክርን ሲሰሙት ሳይሆን ሲኖሩት ትልቅ ጥቅም ያስገኛል ። ምክር ከአደጋ በፊት የሚያስጠነቅቅ ሲሆን ከአደጋ በኋላም የመነሣት ጉልበት የሚሆን ነው ። ምክር የሌለው ሕይወት የሚማረው ዋጋ እየከፈለ ነው ። ምክር የመንፈስ ቅዱስ በመሆኑ ነጻ ስጦታ ነው ። ነገር ግን ርካሽ አይደለም ። እግዚአብሔር የምክር ጸጋን ይሰጣል ።
ኃይል ሌላውን ለመጣል ሳይሆን ራስን ለማሸነፍ የሚሰጠን ትልቅ በረከት ነው። የታመመውን ለመፈወስ ፣ የወደቀውን ለማንሣት የሚሰጥ ሀብት ቢኖር ኃይል ነው ። ኃይል የማይፈልግ ዓለምና ሰው የለም ። ሕይወት የኃይል ጥገኛ ናት ። ቀኑን በድል ለመፈጸም ብቻ ሳይሆን በዚህች ቅጽበትም በተስፋ ሙላት ለመሆን ኃይል ያስፈልጋል ። ሰው ኃይሉን ሲጨርስ የመኖር ፍላጎቱ እያነሰ ይመጣል ። ለትካዜም ይዳረጋል ። እግዚአብሔር ግን የኃይልን መንፈስ ይሰጣል ።
እውቀት ብርሃን ነው ። የሚያውቅ ሰው ከባዶነት ስቃይ የተፈወሰ ነው ። እውቀት ከስህተት ውሳኔ ይጋርዳል ። ያመኑበትን እንዳያፍሩበት ይረዳል ። ሰው ያመነበትን በድፍረት የሚይዘው ስለሚያምነው ነገር የሚያውቅ ከሆነ ብቻ ነው ። እውቀት የነፍስ ቀለብ ነው ። አእምሮ ያለ እውቀት እየዛገ ይመጣል ። ታዳሽ አእምሮ የምናገኘው በእውቀት ነው ። እውቀትን ማናዳብር ከሆነ መዘንጋት ውስጥ እየገባን እንመጣለን ። እግዚአብሔር የእውቀትን መንፈስ ይሰጣል ።
እግዚአብሔርን መፍራት ትልቅ ሀብት ነው ። እግዚአብሔርን የሚፈራ የሚያስፈሩት ነገሮች ሁሉ ይወድቁለታል ። እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው እግዚአብሔር በዙፋኑ ሁኖ ሁልጊዜ ይታየዋል ። መውጣት መግባቱን የሚቆጣጠሩ የማይከደኑ ዓይኖች እንዳሉ ያውቃል ። እግዚአብሔርን መፍራት በብርሃንም በጨለማም እንድንቀደስ ያደርጋል ። እግዚአብሔርን መፍራት ምንም ባናተርፍ ኅሊናን ለማትረፍ ይረዳል ። እግዚአብሔርን መፍራት የእውቀት ጉልላት ነው ።
እንዳዩና እንደ ሰሙ አለመፍረድ ትልቅ ሀብት ነው ። ብዙ ሰው የዓይኑና የጆሮው ጥገኛ ነው ። ባየውና በሰማው ለመፍረድ ይቸኩላል ። የእግዚአብሔር መንፈስ ግን ከምናየውና ከምንሰማው ጀርባ ያለውን ድካም በማየት ያዝናል ። ይራራል ። ሰው ያንን ያደረገው ክፉ ስለሆነ ሳይሆን መልካሙን መለየት ስላልቻለ ነው በማለት በቅንነት ያያል ።
ሀብታቱ በጥንድ ተጠቅሰዋል ። “የእግዚአብሔር መንፈስ ፥ የጥበብና የማስተዋል መንፈስ ፥ የምክርና የኃይል መንፈስ ፥ የእውቀትና እግዚአብሔርን የመፍራት መንፈስ ያርፍበታል ።” ጥበብና ማስተዋል በአንድ ላይ ተጠቅሰዋል ። ጥበብ ካለ ማስተዋል አለ ፤ ማስተዋል ጉድለቱን ሲያይ ጥበብ ደግሞ ይሞላዋል ። ምክርና ኃይልም በአንድ ላይ ተጠቅሰዋል ። ምክር ባለበት ድል አለና ። እውቀትና እግዚአብሔርን መፍራት በአንድ ላይ ተጠቅሰዋል ። እወቀት ኃይል ሲሆን ፈሪሀ እግዚአብሔር መሪ ነውና ። ከሁሉ በላይ ሰባተኛው ሀብት እንዳዩና እንደ ሰሙ አለመፍረድ ነው ። እኔ ያየሁትንና የሰማሁትን ክርስቶስ ቢያይና ቢሰማ ምን ያደርግ ነበር ? ማለት ይህ ያለ መፍረድ ሀብት ነው ። እነዚህን ሀብታት ይጨምርልን ።
ጌታ ሆይ ዛሬም እንደ ጥንቱ ፍቅር ነህ ። ዓመታት አያደክሙህም ። ውበትህም እንዳበራ ይኖራል ። በእነዚህ ሀብታት ውስጥ ራሳችንን ስናየው የጎደለን ይህ ነውና ሀብታቱን አፍስስልን ። የተዘባረቀውን ሕይወታችንን አስተካክልልን ። የዚህን ዓለም ሸለቆ እንድንወጣው እባክህን ጸጋን በሙላት ልቀቅልን ። ያንተ የሆነው በጎ ነገር ሁሉ አይለፈን ። በተባረከው ተስፋህ ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 11
ግንቦት 10 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ ተጻፈ በአዲስ አበባ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ