የትምህርቱ ርዕስ | ሰው ማለት

 “በርታ ሰው ሁን” 2ነገሥ. 2፡3
ንጉሥ ዳዊት ልጁ ሰሎሞንን የመከረው የመጨረሻው ምክር ነው ። ሰው መሆን ጥልቅ ምሥጢር ያለው ፣ በዚህ ዓለም ላይ የመገኘታችንን ዓላማ የሚያሟላ ነው ። በዘመናት የተነሡ የእግዚአብሔር ሰዎች ሰው ፈልገዋል ። በየዘመናቱ የጮኹ ፈላስፎችም ሰው በመፈለግ ቃትተዋል ። የፈለጉት ሰው መልኩና ቅርጹ ሰው የሆነ ሳይሆን ልቡ ሰው የሆነ ነው ። በጎነትን የለበሰ ፣ ፍቅርን የደረበ ፣ ፍትሕን የተዋበ ሰው ፈልገዋል ። “ሰው ማለት ሰው የሆነ ነው ሰው የጠፋ ዕለት” ተብሏል ። በማይጨው ጦርነት ኢትዮጵያ ድል ሲርቃት ፣ ንጉሡ አገር ለቀው ለአቤቱታ ሲጓዙ ገበሬው ያለሁት መሪ እኔ ነኝ አገሬን አላስደፍርም ። ነጻነቴን ሰጥቼም በክብር ልኖር አልችልም በማለት ራሱን ሹሞ ተዋጋ ። የሚደንቀው ጨዋነቱ ንጉሡ ሲመጡ የነጻነቱ ዓርማ አድርጎ ተቀበላቸው እንጂ እኔ ልንገሥ በማለት አልተጣላም ። ሰው በጠፋ ቀን ሰው ሁነው የተገኙ አያሌ ኢትዮጵያውያን አሉ ። ደጃች በላይ ዘለቀ ፣ ራስ አበበ አረጋይ ፣ የአድዋው ድል ሳይበቃቸው በሽምግልናቸው የተዋጉ ደጃች ባልቻ … እነዚህ ሁሉ ሰው የጠፋ ቀን ሰው ሁነው የተገኙ ናቸው ። ዛሬ በቋንቋችን የምናወራው ፣ ስማችን የጣልያን ያልሆነው ፣ ነጻ ባንዲራ የያዝነው በእነዚህ ሰው ሁነው በተገኙት አርበኞች ነው ። የተዋጉት ለአገር ፣ ለሃይማኖት ፣ ለነጻነት ነው ። እነዚህ ሦስት ነገሮች ከሌሉ የሰውነት ክብር ዝቅ ይላል ።
ንጉሥ ዳዊት፡- “በርታ ሰው ሁን” ብሎ ሲናገር ጌታችን ደግሞ “ከሰዎች ተጠበቁ” በማለት ተናግሯል ። ማቴ. 10፡17 ። የአዲስ ኪዳንን መጻሕፍት ብቻ በማገላበጥ በሰውነት ወግ ስላልተገኙና የእንስሳትና የአራዊት ስያሜ ስለተሰጣቸው ሰዎች እናያለን ።
  1-  እፉኝት፡- እናንተ የእፉኝት ልጆች፥ ከሚመጣው ቍጣ እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ?” ማቴ. 3፡7 ። ይህንን ቃል የተናገረው መጥምቁ ዮሐንስ ነው ። ስለ እፉኝት እባብ የሚተረክ አለ፡- እፉኝት የተባለ የእባብ ዘር በዘመኑ አንድ ጊዜ ብቻ ከሴቷ ጋር ሩካቤ ባደረገ ጊዜ ይሞታል ። ሴቷ እፉኝትም የፀነሰቻቸው ሆዷን ቀደው ሲወጡ ትሞታለች ይባላል ። እፉኝት ስትፀንስ ባሏን ትገድላለች ፣ ስትወልድ ልጆችዋ ይገድሏታል ማለት ነው ። መጥምቁ ዮሐንስ የእፉኝት ልጆች በማለት ከሰውነት ክብር የወረዱትን ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያንን ገሥጾአል ። እፉኝት ዘር የሰጣትን ትገድላለች ፣ ክፉዎችም ለአገር ለትውልድ የሚተርፍ ነገር የሰጡትን ሰዎች ይገድላሉ ። ማወቅ ዕዳ እስኪመስል በአገራችን ስንት ሊቃውንት ተፈጁ ። ጮሌ እንጂ እውነተኛ መኖር ያልቻለባት ፣ እሳት የላሱ ደንቆሮዎች ያደከሟት አገር ናት ። ሥርዓት ሲለወጥ አብረው የሚለወጡ ፣ መገልበጥ የማይሰለቻቸው ፣ ከታቦትም ከዳጎንም ኅብረት ያላቸው አያሌ ናቸው ።እነዚህ እንደ እፉኝት ፣ ዘር የሚሰጡትን በመግደል የሰለጠኑ ናቸው ። ዘር የሰጣትን የገደለች እፉኝት የምትወልዳቸው ይገድሏታል ። መልካም ያደረጉትን ፣ አገር ያቀኑትን በማጥፋት የተሰማሩ ፍጻሜአቸው በወለዱአቸው መሞት ነው ። “አብዮት ልጇን በላች” እየተባለ ሲነገር የነበረው እፉኝትነት ሰልጥኖ ስለነበር ነው።
 ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ለክብርና ለሥልጣን ሲጋደሉ ብዙ ነቢያትንና አባቶችን አስገደሉ ። በዘርፋፋው ቀሚሳቸው ውስጥ ጦርና ጎራዴ ነበር ። የቻሉትን ራሳቸው ፣ ያልቻሉትን ለሮማውያን አሳልፈው በመስጠት አገርን አመከኑ ። መጨረሻ ግን በወደዷቸው ሮማውያን ተደመሰሱ ። በነጠላ የሚገድልልን ጠላት መጨረሻ ላይ በጅምላ ይገድለናል ። ዛሬም ያስተማሩንን ፣ ያገለገሉንን ፣ ያጽናኑንን መግደል ቋሚ ሥራ ሁኗል ። በመግደል ስብከት የፀነስናቸው ሲወለዱ እኛን መግደላቸው እርግጥ ነው። ክፋትን በማስተማር የምንወልዳቸው ከእኛ የባሱ ክፉዎች ይሆናሉ ። ሌላውን በመግደል የኖረ ማንም የለም ። ገዳዮች ለጊዜው ይንጎማለላሉ ፣ ቀጥሎ በወለዱአቸው ልጆች ይወገዳሉ ። የዓለም ታሪክ የምንለው በአመዛኙ የእፉኝት ታሪክ ነው ።
    2-  ድንጋዮች፡- ከነዚህ ድንጋዮች ለአብርሃም ልጆች ሊያስነሣለት እግዚአብሔር ይችላል።” ማቴ. 3፡9 ። ድንጋዮች በማለት መጥምቁ ዮሐንስ የገለጣቸው አሕዛብ ናቸው ። ልጆቻቸውን ለጣዖታት ሲሠዉ ምንም የማይሰማቸው ፣ ርኅራኄ የራቃቸው ድንጋዮች ነበሩ ። የማይርሱ ፣ በፍቅር የማይማረኩ ፣ ውለታን የማያስቡ ፣ ብዙ አማልክትና ብዙ ትዳርን የተለማመዱ ድንጋዮች ነበሩ ። ድንጋይ የኒውክለር መነሻ ናት ፣ አቤል የሞተው በድንጋይ ነው ። ድንጋይ ገዳይነት ነው ። ሰው መሆን ያቃታቸው ድንጋይ ይሆናሉ ። ለገዛ ልጆቻቸው ሳይቀር ኃላፊነት የማይሰማቸው ፣ ወልደው የሚክዱ ፣ በየስፍራው በመውለዳቸው ክብር የሚሰማቸው እነዚህ ድንጋይ ናቸው ።ልጆቻቸውን ለዘመናዊነትና ለኃጢአት ሲሠዉ ቅር የማይላቸው ፣ ገንዘብ ያምጣ እንጂ ልጅ ቢሸጥ መልካም ነው ብለው የሚያስቡ ከሰውነት ወደ ድንጋይ ዝቅ ያሉ ናቸው ። በቀላሉ የማይነኩ የድንጋይ ልብ ያላቸው ፣ ፍቅር የማይስባቸው ፣ በአንድ የማይረጉ ፣ ለአሚናቸው የማይታመኑ ድንጋይ ተብለዋል ። ጌታ ግን ከእነዚህ ድንጋዮች ልጆችን ያስነሣል ። በነቢዩ ሕዝቅኤልም፡- የድንጋዩንም ልብ ከሥጋችሁ አወጣለሁ የሥጋንም ልብ እሰጣችኋለሁ” በማለት ተስፋ ሰጥቶ ነበር። ሕዝ. 36፡26 ።
  3- ውሾች፡- በእግራቸው እንዳይረግጡት ተመልሰውም እንዳይነክሱአችሁ፥ የተቀደሰውን ለውሾች አትስጡ ፥ ዕንቁዎቻችሁንም በእሪያዎች ፊት አትጣሉ ።” ማቴ. 7፡6 ። ውሾችና እሪያዎች የተባሉት መናፍቃን ወይም የስህተት ትምህርት የሚያስተምሩ ናቸው ። የተቀደሰና ዕንቁ የተባለው የእግዚአብሔር ቃል ነው ። ውዱን ቃል እንዲሁ ማባከን እንዲረገጥና መልሰው እንዲሰድቡን የሚያደርግ ነው ። ውሻ የተፋውን መልሶ ይልሳል ። የኑፋቄ ትምህርት የለከፈው ሰውም ወጣሁ ሲል ተመልሶ ይያዛል ። የኑፋቄ ትምህርት በቀላሉ ከነፍስ ውስጥ አይወጣም ። ኑፋቄ የእግዚአብሔርን ስም የሚጠራ ነገር ግን እግዚአብሔር የለሽ ሰውን የሚፈጥር ነው ። እርያም ታጥቦ መልሶ ጭቃ ላይ ይንከባለላል።የመናፍቃን ንስሐም እንደማይረጋ ከአርዮስ ታይቷል ። ከስህተት ትምህርት መጠበቅ ያለብን ዋጋ ስለሚያስከፍል ነው ። ኑፋቄ ዘመንን በሚመስል ነገር የሚጨርስ ነው ። ኑፋቄ እኔ ልክ ነኝ ለማለት እነ እገሌ ተሳስተዋል እያለ የሚያዜም ነው ። ራስን ለማየት ጊዜ ያሳጣል ። ዘወትርም እንዲህ ተብሏል እንዲህ ብለን መልስ እንስጥ የሚል የሙግት ዓለም ነው ። መቃወምና መንቀፍ ፣ ራስን ግን መቆለል ዓይነተኛ ባሕርይው ነው ።
“በርታ ሰው ሁን” የሚለውን የንጉሥ ዳዊትን የመጨረሻ ምክር መስማት በእውነት ተገቢ ነው ። ሰው በመጨረሻ ሰዓት የሚናገረው ሐቁን ብቻ ሳይሆን የዘመኑን የተጨመቀ ምክርም ነው ። በርትቶ ሰው ያልሆነ እፉኝት ሁኖ መጀመሪያ ገዳይ ከዚያም ሟች ይሆናል ። ድንጋይ ሁኖ የማይርስ ፣ ለገንዘብ እንጂ ለፍቅር ግድ የሌለው ፣ ማንም ቢወድቅ የማያዝን ይሆናል ። ውሻ ሁኖ የተፋውን ይልሳል ፣ ወጣሁ ሲል ይያዛል ። በማይረጋ ንስሐ ይኖራል ።
“በርታ ሰው ሁን ።” ዛሬም ሰው እየጠፋ ነው ። እውነት የሚናገር ደግ ሰው እያጣን ነው ። መተማመን ጎድሎንም ፊትና ኋላ መሄድ የማንችል እየተጠባበቅን የምንጓዝ የጅብ መንገደኞች ሁነናል ። ሰው በጠፋበት ዘመን ሰው መሆን ያስፈልገናል እንጂ “ሰው የለም” እያልን ማዘን ምን ይጠቅመናል ? ሰው የለም ማለት ክብር የለውም ፤ ሰው ሆኖ መገኘት ግን ለዛሬ ደስታ ፣ ለነገ ታሪክ ነው ።
የዓለማትና የዘመናት ፣ የዳርቻዎችና የአድማሳት ፈጣሪ ፣ መቻልህ አጋዥ ፣ መሥራትህ አማካሪ የሌለው ፣ እኔ ነኝ ብለህ ያሳረፍከን ፣ በስምህም ነጻ ያወጣኸን ቡሩክ የዓለም ተስፋ ተመስገን ። እባክህን ሰው መሆንን አድለን ።አንተ የመረጥከው ዓይነት ሰው አድርገህ ሥራን ። ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 26
ግንቦት 26 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም