መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ሰው እንዳንተ ነው

የትምህርቱ ርዕስ | ሰው እንዳንተ ነው

ዛሬ ላይ ቁሞ ትላንትን በትዝታ ፣ ነገን በስጋት የሚኖር ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። ዛሬን ለመኖር የማይደፍር ፣ በሰንጣቃ ዓለት እንዳለ በትላንትናና በነገ መካከል የሚተክዝ ነው ። ሰው ማለት እንደ አንተ ነው ። እውነቴን ነው ፣ የቅዱሳን አምላክ ምስክሬ ነው ፤ የተሰማህን ያ ሰው ተሰምቶታል ፣ ያመመህ ሕመም እዚያ ሰውዬ ጋ እየጀመረ ነው ። ሰው ማለት እንደ አንተ ነውና ኅሊናው ሳይወቀስ አይቀርም ። ክፋት ሲያበዛ ፣ በበደል ላይ በደል ሲጨምር ፣ ዝምታህን ሰብሮ ክፉ ሊያናግርህ ሲሻ ውስጡ እየተሰቃየ ነው ፣ ባንተ ስህተት ውስጥ ለመደበቅና እፎይታ ለማግኘት እየፈለገ ነው ። አንተም ብትሆን እየበደልካቸው ዝም ሲሉህ ያምሃልና ። በጣም ክፉ ስትሆን የሚተፋህ ፣ በጣም ደግ ስትሆን ሰስቶ የሚርቅህ ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። እንደ አንተም ስለሆነ መሸነፍን የማይፈልግ ይቅርታ ማለትን እንደ ተራራ የሚያይ ነው ። ሰው ማለት እንደ አንተ ነው ፣ ሲያጠፋ ትክክል የነበረ ትንሽ ቆይቶ ግን ኅሊናው የሚቆስልበት ነው ። ሰው እኮ እንደ አንተ ነው ፣ እየራበው በልቻለሁ የሚልህ ፣ ተበድሮ ድግስ የሚደግስልህ ባለ ይሉኝታ ነው ። ሰው ማለት እንደ አንተ ነው ። መልካሙን ቀን ፣ የትላንትን ጥሩ ጊዜ መመለስ ቢያቅተው እውቅና እንኳ ለመስጠት ረጋ ያላለ ነው ። አዎ ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። ቀስት ሁሉ ወደ እርሱ የተነጣጠረ የሚመስለው ፣ አማርኛ የሚቆረጥመው ፣ ፀጉር የሚሰነጥቀው ፣ “እንዲህ ያለው ምን ለማለት ፈልጎ ነው ?” የሚለው ሰው እንዳንተ ነው ። 
 
አንተ እርሱን ትፈራዋለህ ፣ እርሱ አንተን ይፈራሃል ፤ በግልጽ ያላወራችሁ መንጋ ፈሪዎች ናችሁ ። ምክንያቱም ሰው ማለት እንዳንተ ነውና ። በጠጅ ጀምሮ በቅራሪ የሚጨርስ ፣ በጉዳትህ በአንድ ዓይኑ እያለቀሰ በአንድ ዓይኑ የሚስቅ ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። ሬሳ አስቀምጦ የሚስቅ ፣ ሲደነግጥ “ጥርስ ባዳ ነው” የሚል ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። ትላንት ስንዴ ዘርቶ ስንዴ ያጭድ ነበር ፣ ዛሬ ገብስ ቀጥሎም እንክርዳድ በማጨዱ ግራ የተጋባ ፣ ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። ፊትህን እያየ ጀርባህን የሚያጠና ፣ ሳሎን አስቀምጠኸው ጓዳ የሚገባ ፣ ለነገ አስበኸው ማምሻ የማይገኝ ፣ ለዓመት ሰፍረኸው ለዕለት የሚያልቅ ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። በከመርከው ቊጥር የሚወርድ “የተልባ ስፍር” ሰው ማለት እንዳንተ ነው ፣ መንሸራተት የማይደክመው ።
አዎ አምላከ አበው ምስክሬ ነው ፣ ሰው ማለት ልክ እንዳንተ ነው ። ራስህን ፊት ለፊትህ ማየት ስላቃተህ እንጂ ያ ሰው ማለት አንተ ነህ ። አንተ ማለትም ያ ሰው ነህ ። ስልክህ ተጠልፎ ሲያስተጋባ የገዛ ድምፅህን መስማት እንደሚያስደነግጥህ ሁሉ ፣ የሰውዬውን ድምፅ ስትሰማ የደነገጥኸው ራስህን ስለሰማኸው ነው ። ሰውዬው ያደረገው አንተ የምታደርገውን ነው ። ዛሬ ባታደርገው ነገ የምታደርገውን ነው ። የጊዜ ጉዳይ እንጂ እነዚያ የወደቁትን ትወድቀዋለህ ፣ እነዚያ የወጡትን ትወጣዋለህ ። ምናልባት በዚያ ሰውዬና ባንተ መካከል ያለው ልዩነት እርሱ በመናገሩ አንተ ዝም በማለትህ ነው ። የሁለታችሁም ኅሊና ግን ያው አረም ያለበት ማሳ ነው ። ጠዋት ስትነሣ ያለው ማንነትህ ቀን ላይ እንደ ገጠመህ የቆሸሸ ሰውዬ ነው ። ሰውዬው ዋለበት አንተ አረፈድክበት እንጂ ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። የአንድ ቀን ውኃ ሲያጣ ራሱን መቀበል የሚያቅተው ማንነት የተሸከምህ ነህ ። በውስጥህ የሚበቅሉት ነገሮች ከደጅ የመጡ አይደሉም። ጊዜ የገለጣቸው አዳማዊነትህ ነው ። ሰው ማለት እንዳንተ ነው ራራ ። ሰው ማለት እንዳንተ ነውና አትደንብር ።
ከተወለድክበት ጊዜ ጀምሮ እየሞትህ ነው ። ጥርስህ ይሰበራል ፣ ድድህ ይደማል። ሲቆይ እግርህ ያነክሳል ፣ ጨጋራህ ያጓራል … ። አንተ አካሉ በሸተተው በሽተኛ ለመደነቅ መልአክ አይደለህም ። ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። እርሱ እንዳንተ ያስብ ነበር ። ዳሩ መሐል ሁኖ ነካው  ። ሩቅ ያዩት ሩቅ አይቀርምና ይኸው ሲይዘው ከበደው ። “እንዴት ያማርራል ?” ባለበት ነገር ይኸው የበለጠ እያለቀሰ ነው ። ሰው ሲታበይ እግዚአብሔር ይስቃል ። ጠዋት ጠግበሃል እንደገና ምግብ የሚያምርህ እስከማይመስልህ ተንገፍግፈሃል ። ሆድ ግን እጅግ ከሃዲ ነውና ይኸው ምሳ ላይ ርቦሃል ። ከበሽታ ብትድን ፣ ከድህነት ብታመልጥ ለመጨረሻ ጊዜ አይደለምና ተጠንቀቅ ። እዚያ ማዶ የምታየው ሰው እንዳንተ ነበረ ። ይህችን ከሃዲ ዓለም አትመናት ።   
አንተ ድራማውን በመቻልህ በድብቅ በማድረግህ ፣ እርሱ አላውቅበት ብሎ በግልጽ በማድረጉ እንጂ ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። አዎ ሰው ማለት እንዳንተ ነው ልቡን አስቀምጦ በአፉ የሚያወራህ ፣ እንዳላስቀይመው ብሎ የሚዋሽህ ፣ በአሳቡ ሂዶ በድኑን ያስታቀፈህ ሰው ማለት እንዳንተ ነው ። አንተን የሚፈትንህ የኃጢአት ስሜት እርሱንም ይፈትነዋል ። አንተ በወደቅህበት ብዙ ጊዜ ወድቋል። መዐርጉ ፣ ያለበት ሥልጣን ሳይረዳው ሰው በጣም ይደክማል ። ምክንያቱም ሰው እንዳንተ ነው ። ሰው እንዳንተ ነውና አትፍራው ። ሰው እንዳንተ ነውና አክብረው ። እግዚአብሔር ግን እንዳንተ አይደለምና ፍራው፡፡      
      
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም