መግቢያ » ትረካ » ቀራጩ ማቴዎስ » ቀራጩ ማቴዎስ /2/

የትምህርቱ ርዕስ | ቀራጩ ማቴዎስ /2/

/ማቴ. 9፡9-13/
ማቴዎስም ሁሉን ይዞ ሳይሆን ሁሉን ጥሎ ተከተለው ። ሁሉን ይዘው የሚከተሉ በቤተ ክርስቲያን ለሚነሣ ሁከት ምክንያት ናቸው ። ሁሉን ጥለው የሚከተሉ ግን ዓለምን የናቁ ሰላማውያን ናቸው ። ማቴዎስ ሁሉን ትቶ ተከተለ ። ማቴዎስ ሕይወትን ለዋጭ ፣ አድራሻን ቀያሪ የሆነውን መለኮታዊ ጥሪ ሲሰማ ያ የብሉይ ኪዳን ነቢይ ኤልሳዕ ትዝ አለው ። ኤልሳዕ በእርሻ ላይ ሳለ በነቢዩ ኤልያስ በኩል ጥሪ የደረሰው ገበሬ ነው ። እርሱም ከአሥራ ሁለት ጥማድ በሬ ሁለቱን አርዶ ፣ የቁም ተዝካሩን አውጥቶ ፣ ዓለምን ተሰናብቶ እግዚአብሔርን ተከተለ ። 1ነገሥ. 19፡19-21 ። ማቴዎስም ታላቅ ግብዣ አድርጎ ዓለምን ተሰናብቶ ፣ ጌታውን አመስግኖ ለመከተል ፈለገ ። ሲፋታ የሚደግስ የለም ፣ ማቴዎስ ግን ከዓለም ሲፋታ ደገሰ ። ቅድም የምድራዊ መንግሥት ሠራተኛ ነበር ፣ አሁን የሰማያዊ መንግሥት ሠራተኛ ሆነ ። የቀራጭነት ልምድ ለደቀ መዝሙርነት አይረዳም ፤ ጌታ ግን ከአዲስ ይጀምራል ። ሥራውን ብቻ ሳይሆን ዜግነትም ፣ ንጉሥም ቀየረ ። የእግዚአብሔር ጥሪና እውነተኛ ንስሐ ታሪክን ይለውጣል ። በመንግሥቱ የጋበዘውን ጌታ በቤቱ መጋበዝ ፈለገ ። ተጠልቶና ተንቆ ነበርና በቤቱ ቢጤዎቹ እንጂ ደህና የሚባሉ ሰዎች አይገቡም ነበር ። የቀራጮች ማኅበረተኛ ነበር ። ከዚያ ለመውጣት አቅምም ዕድልም አልነበረውም ። ጌታ ግን አዲስ መንገድን አሳየው ። ድኅነተ ነፍስ ብቻ ሳይሆን አእምሮን የማይቆረቁር ተልእኮ ተቀበለ ።

ማቴዎስም ጌታንና ደቀ መዛሙርቱን ብቻ ሳይሆን የከተማዋን ኃጢአተኞችና ቀራጮች ሰበሰበ ። እኔን እንዳዳነ ያድናቸው ብሎ ነው ። የክርስቶስ ማዳኑ ለማቴዎስ ብቻ አልነበረም ። ክርስቶስ ለሁሉ ቢሰጡት የማይቀንስ ሀብት ነው ። ቀራጮች በነፍሴ ለምጻም ነኝ በሚል ሒሳብ ራሳቸውን ያገለሉ ፣ ሰውም ያገለላቸው ፣ ከሌላ ቀራጭ ጋር ካልሆነ ዕድርና እቁብ የሚጠጡ አልነበሩም ።በእያንዳንዱ እንቅስቃሴአቸው ፍርሃት ባይርቃቸውም ክርስቶስን ግን ልበ ሙሉ ሁነው ቀረቡት ። በአንድ መንገድ ከሌላው አይሁዳዊ ጋር የማይሄዱ በአንድ ገበታ ከክርስቶስ ጋር ታደሙ ። ንጽሕናው የሚያሸማቅቅ ፣ ቅድስናው የሚገፈትር አልነበረም ። የእርሱ ንጽሕና የሚያነጻ ፣ ቅድስናውም የሚቀደስ ነው ። አንዳንድ ሰዎች የሚመኙት ቅድስና አለ ፣ እነርሱ በተሳፈሩበት መጓጓዣ ጋኔን የሚጮህ ፣ አጠገባቸው ያለው ሰው ተቃጠልሁ ብሎ የሚሮጥበትን ቅድስና ይፈልጋሉ ። እውነተኛ ቅድስና ግን ኃጢአተኞችን የሚያቅፍ ነው ። የሚያስበረግግና የሚያሸማቅቅ ፣ ኃጢአተኞችን ተስፋ የለሽ የሚያደርግ ቅድስና ከእግዚአብሔር አይደለም ። ኃጢአተኞች ከክርስቶስ ጋር ሲሆኑ ሰላም ተሰማቸው እንጂ ራሳቸው አንሶባቸው አልተረበሹም ። የትላንቱን ለመጣል ጉልበት አገኙ እንጂ እኔ አልድንም ብለው አልፈሩም ። ነገ በብሩህ ታያቸው እንጂ የእኔ ኃጢአት ንስሐ የለው ብለው አልሰጉም ።
እንደ እኔ የታመሙ መኖራቸውን ማሰብ ያጽናና ይሆናል ። መድኃኒቱን ሳገኝ እንደ እኔ የታመሙትን መፈለግ ደግሞ ግዴታ ነው ። ማቴዎስ እንደ እርሱ የታመሙትን ፣ በሰው መካከል እየኖሩ ሰው አልባ የሆኑትን ፣ በአድማ ተገልለው ብቸኛ የሆኑትን ፣ ኃጢአተኞችና ቀራጮች ጠራ ። ጌታችንም እነርሱን ከማቅረብ ውጭ የሚያቀራርብ አሳብ አላመጣም ፣ ከመውደድም ውጭ የማረጋጋት መልእክት አላስተላለፈም ። አጠገቡ ስፍራ ስላገኙ ፣ አብረው ማዕድ ስለቆረሱ “ለካ የሚወደን አለ” ብለው አረፉ ። የሺህዎችን ጥላቻ በአንዱ ፍቅር ሻሩ ። የብዙዎችን ስድብ በእርሱ ማቅረብ ዘነጉ ። የፍቅር ኃይል ከጥላቻ ኃይል በላይ ነው ።
ወግ አጥባቂዎቹ ፈሪሳውያን ይህን ሲያዩ ተበሳጩ ። እነርሱ ኃጢአትን ይወዳሉ ፣ ኃጢአተኛን ግን ይጠላሉ ። ያሉበትን ኃጢአት ላለማሳየት ኃጢአተኞችን ሲያወግዙ መዋል ስልታቸው ነው ። በጣም የሚሰድቡት የኃጢአት ዓይነት እነርሱ የወደቁበት ገደል ነው ። “እኔ የምኖረው ይህን ስህተት ለማጥፋት ነው” በማለት የተሳሳቱት ላይ ሰይፍ ይዘው ይወጣሉ ። እቤታቸው ሲገቡ ግን ያን ስህተት ይፈጽሙታል ። ልዩነታቸው ቀራጮችና ኃጢአተኞች በግልጽ መውደቃቸው ፈሪሳውያን ግን በድብቅ መውደቃቸው ነው ። ፈሪሳውያን ማለት ሐኪም ቤት ከፍተው በሽተኛ አይምጣብኝ የሚሉ መምህራን ናቸው ። መቼም “ትልቁ ድሀ ትንሹን ድሀ አይወደውም” እንዲሉ ትልቁ ኃጢአተኛ ትንሹን ኃጢአተኛ አይወደውም ። ፈሪሳውያንም መመጻደቅ ከሳሽ ያደርጋልና ክስ ጀመሩ ። የክስ ዓላማም የክርስቶስን ወገኖችን ለሁለት መክፈል ነው ። ጥርጣሬን እየፈጠሩ እኛን ብቻ እመኑን ቢሉም እነርሱም አንድ ቀን የዘሩትን ያጭዳሉ ።
“ፈሪሳውያንም አይተው ደቀ መዛሙርቱን፡- መምህራችሁ ከቀራጮችና ከኃጢአተኞች ጋር አብሮ ስለ ምን ይበላል ? አሉአቸው ።” ፈሪሳውያን ያልገባቸው ነገር ጌታ ከቀራጭ ጋር አብሮ መብላት ሳይሆን ከማቴዎስ ጋር አብሮ ሊኖር ነው ። እርሱ ስም ያላቸውን ለመመልመል የመጣ አይደለም ። የኃጢአተኞች ወዳጅ ሁኖ ለኃጢአተኛው ዓለም ንጽሕናን ለማልበስ የመጣ ነው ። ከማቴዎስ በቀር ደቀ መዛሙርቱ እንደ ፈሪሳውያን ሲያስቡ የኖሩ ናቸው ። ይልቁንም ቀናተኛው ስምዖን በመካከላቸው አለ ። “ቀራጭን መግደል ነው” ብሎ የሚያምን ሰው ነበር ። ክርስቶስ የመረጠውን ግን ማን ይገፋዋል ? ይህ ጥያቄ በውስጡ ብዙ ነገሮች አሉት ። “መምህራችሁ” አሉ ። መምህራችን አይደለም ማለታቸው ነው ። ኃጢአተኞችን በገፉበት መጠን ክርስቶስንም ገፉት ። ክርስቶስን አያርፉበትም ፣ ባረፉበት ሰዎች ደግሞ ይበሳጫሉ ። ክርስቶስ መልስ ሁኖ ያላሳረፋቸው ጥያቄ ሁኖ ያብሰለስላቸዋል ። ፈሪሳውያን ጥያቄውንም በቀጥታ ወደ ክርስቶስ አላቀረቡም ። ምን እንደሚመልስላቸው ያውቁታል ። ጥያቄውን ግን ወደ አዳዲስ ደቀ መዛሙርት አቀረቡ ። ደቀ መዛሙርቱም  ክርስቶስ የተቀበለውን ስለመቀበል ብቻ የሚያውቁ ነበሩ ። ለዚህ ጥያቄ መልስ ለመስጠት ገና በእምነት አላደጉም ። ጌታ ግን የጠራቸው ወገኖች ሲከሰሱ አንደበታቸው ነው ። ስለዚህ ለቀራጮችና ለኃጢአተኞች ተሟገተላቸው፡-
“ኢየሱስም ሰምቶ፡- ሕመምተኞች እንጂ ባለ ጤናዎች ባለ መድኃኒት አያስፈልጋቸውም ፤ ነገር ግን ሄዳችሁ፡- ምሕረትን እወዳለሁ መሥዋዕትንም አይደለም ያለው ምን እንደ ሆነ ተማሩ ፤ ኃጢአተኞችን ወደ ንስሐ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁምና አላቸው ።”  የምንባለውን እርሱ ይሰማል። ሰዎች የሚሉንን እርሱ አይለንም ። እርሱ ኃጢአተኞችን ይመለከት የነበረው እንደ ታካሚዎቹ ነው ። ሐኪም በሽተኛው እንዲህ ያለ ሕመም ስለ ተያዘ አይቀየመውም ። እንዲድንለት ብቻ ጥረት ያደርጋል ። ትልቁ የነፍስ ሐኪም ክርስቶስም ኃጢአተኞችን ስለ ማዳን ያስባል እንጂ በበሽታቸው አይሸሻቸውም ። በእርሱ ዘንድም እውነተኛው በሽታ ኃጢአት ነው ። በሽተኞችን በማከም እንጂ በመሸሽ በሽታን ከምድር ማጥፋት አይቻልም ። ጤነኛ ነን ብለው ለሚያስቡ ፈሪሳውያን እርሱ አያስፈልጋቸውም ። ክርስቶስ የመጣውና የሚያስፈልገው ኃጢአተኛ እንደሆኑ ለተሰማቸው ብቻ ነው ። እርሱ ምሕረትን እንጂ መሥዋዕትን የሚወድ አይደለም ። መሥዋዕት ሰው የሚያቀርበው ነው ፣ ምሕረት ግን ሰው የሚሰጠው ነው ። ሰው መሥዋዕት በማቅረብ ደስ እንደሚለው እርሱ ደግሞ ምሕረትን በመስጠት ደስ ይለዋል ። የመሥዋዕት ዓላማውም ምሕረት ለመቀበል ነው ። ፈሪሳውያን በመሥዋዕት ምሕረት ይለምናሉ ፣ ሌላው ምሕረት ሲያገኝ ግን ደስተኛ አይደሉም ። የግብዞች ትልቁ ችግር የእግዚአብሔርን ምሕረት ለግል ኃጢአታቸው መጽናኛ ማድረጋቸው ነው ። ምሕረቱ ለዓለምና ለዘላለም ነው ። ምሕረቱ ለሰፈር አይደለም ፣ ለዓለም ነው ። ምሕረቱ ለዛሬ አይደለም ፤ ምሕረቱ ለዘላለም ነው ።
ያ ቀንም ደስታን ለማጨለም በመጡ ፈሪሳውያን ያልተሸነፈ ብርሃን የበራበት ዕለተ ብርሃን ነበር ። አንዴ እርሱ ይቅር ካለ ማንም መክሰስ አይችልም ። ማቴዎስም ከጌታ ጋር ኑሮውን ጀመረ ። ያላሰበው ቦታ ዋለ ። ቀድሞ ስለ ኃጢአተኝነቱ ብቻ ያስብ ነበር ። አሁን ግን ስለ አዳኙ ታላቅነት ማሰብ ጀመረ ። ክርስቲያን መሆን ማለትም ኃጢአትን ማሰብ አይደለም ፣ እርሱማ ዓለማውያንም ያስቡታል ። መሐሪ ጌታ እንዳለ ማመን እርሱ ክርስትና ነው ። ስለሚጠሉን ማሰብ ሳይሆን ስለሚወደን ጌታ ማሰብ እርሱ ሃይማኖት ነው።
ማቴዎስ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ከጌታ ጋር በዋለበት እየዋለ ፣ ባደረበት እያደረ ቆየ ። የትንሣኤውም ምስክር ሁኖ ከሐዋርያት ጋር ወደ ዓለም ወጣ ። እነዚያ ይጠሉት የነበሩትን አይሁድ ለመካስ ፣ እርሱ ደግሞ በፍቅር ለመመለስ አሰበ ። ስለዚህም ወንጌሉን በሚገባቸው በአራማይክ ቋንቋ ጻፈላቸው ። ክርስቶስ የዳዊት ልጅ መሆኑን በመግለጥ ልባቸውን ወደ ንጉሣዊ ክብር ከፍ አደረገው ። ከሁሉ ቀድሞም በ41 ዓ.ም. ወንጌሉን ጻፈ ። የመጀመሪያው የአዲስ ኪዳን መጽሐፍም የማቴዎስ ወንጌል ነው ። ማቴዎስ ስለ ራሱ ሲጽፍ ጌታ ታሪኩን እንደለወጠለት ገለጸ እንጂ በይገባኛል ስሜት አልጻፈም ። ስለ ራሱ ጥሪ የጻፈውም ዘጠነኛው ምዕራፍ ላይ ነው ። በአሥረኛው ምዕራፍም ከሐዋርያት ዝርዝር ውስጥ ራሱን ሲገልጽ “ቀራጩ ማቴዎስ” አለ ። ትሑት ነበር ።
ማቴዎስ አሁንም ስመ ብዙ ሆነ ። ሲጠራ ደቀ መዝሙር ፣ ሲላክ ሐዋርያ ፣ ወንጌሉን ሲጽፍ ወንጌላዊ ተባለ ። በሰማዕትነትም ገድሉን ስለፈጸመ ሰማዕት ይባላል ። ማርቆስና ሉቃስም ወንጌላቱን የጻፉት ለሮማ ግዛትና ሰዎች ነውና ከቀራጭነት ወንበር ላይ ተነሥቶ የመነነ መሆኑን ጠቅሰው ስሙን ግን ሌዊና የእልፍዮስ ልጅ በማለት ሕይወቱን ከአደጋ ሰውረዋል ። ማቴዎስ ያላሉት ሕይወቱን ለመከለል ፣ የሮማን መንግሥት የከዳ እንዳይባል ነው ። ጽሑፍ የሌላውን ሕይወት ከአደጋ የመከለል ግዴታ አለበት ። ማር. 2፡14፤ ሉቃ. 5፡27። ማቴዎስ የስሙ ትርጉም “የእግዚአብሔር ስጦታ” ማለት ነው ።
ቀራጭን ሐዋርያ ፣ ገንዘብ ሰብሳቢን ነፍስ ሰብሳቢ የሚያደርግ ጌታ የእኛንም ሕይወት ሊለውጥ ይቻለዋል ።
ተፈጸመ
ሰኔ 21 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ 
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም