መግቢያ » ትረካ » በተዘጋው የሚመጣ » በተዘጋው የሚመጣ /3/

የትምህርቱ ርዕስ | በተዘጋው የሚመጣ /3/

 “ያም ቀን እርሱም ከሳምንቱ ፊተኛው በመሸ ጊዜ ፥ ደቀ መዛሙርቱ ተሰብስበው በነበሩበት ፥ አይሁድን ስለ ፈሩ ደጆቹ ተዘግተው ሳሉ ፥ ኢየሱስ መጣ፤ በመካከላቸውም ቆሞ፡- ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው ።”/ዮሐ. 20፡19 ።/
እርሱ አስቀድሞ፡- “ያከበሩኝን አከብራለሁ” ብሏል ። /1ሳሙ. 2፡30 ።/ ቅዱሳን ሴቶች ማልደው ወደ መቃብሩ ስለገሰገሱ እርሱም ማልዶ የምሥራቹን አሰማቸው ። “ለገቢህ ተንገብገብለት” ይባላል ። ገቢህ የተባለው ስትጠራው አቤት ለሚልህ ፣ ስትጮህ ለሚደርስልህ ፣ እሳት ውስጥ ስትገባ እሳት ገብቶ ለሚያወጣህ ፣ ሲከፋህ አብሮ ለሚከፋ ፣ ስትታመም ለሚያገላብጥህ ለእርሱ ተንገብገብለት ፣ ኑርለት ፣ አልቅስለት ፣ ራራለት ፣ ሁለመናህን ስጠው ማለት ነው ።  ጌታም ለገቢዎቹ ይንገበገባል  ። እግዚአብሔር ማለዳ የገቡትንና ሠርክ የገቡትን በፍቅር ቢቀበልም ማለዳ መግባት ቢያንስ የቀኑ ሐሩርና የት ልሄድ የሚለው ሥቃይ ፣ ሥራ ፈትነት የሚያመጣውን የልብ ውዝዋዜ እንዲቀር ያደርጋል ። ደግሞም ከነትጥቁ የተማረከና ትጥቁን አራግፎ የተማረከ እኩል አይደለም ። በማለዳ የገቡ ቆስለው የተማረኩ አይደሉም ፣ ትጥቃቸውን ወይም ጉልበታቸውን አባክነው የመጡም አይደሉም ። እኩል በክርስቶስ ብንድንም እኩል አንሸለምም ። ማልደው የገቡ ክብራቸው ከፍ ይላል ። ቅዱሳን ሴቶችና መግደላዊት ማርያም ማልደው ቢሄዱ ትንሣኤን ሰሙ ። ማልደው ወደ እግዚአብሔር በጸሎት የሚገሰግሱ የሚያቆምና የሚያጸና መንፈስን ያገኛሉ ።

ቀኑን ብቻ ሳይሆን ቀኑን የሚያውል ቃል እግዚአብሔር ሰጥቶናል ። ያንን  የሚያገኙ ማልደው ቃለ እግዚአብሔርን የሚያነቡ ናቸው ። ቀኑን ያለ ኃይል መዋል ከባድ ነው ። ከእንቅልፍ እንደ ነቃን እንቅልፍ ሲሰማን ፣ ተኝተን አድረን ድካም መልሶ ሲጫጫነን ፣ ተስፋችን ተሟጦ ፊታችን ሲጨማደድ ፣ የትዳር ጓደኞቻችንንና ልጆቻችንን በጠዋቱ በቍጣ ስናስደነብር ይህ ኃይልን ያለ መሞላት ችግር ነው ። ሰው ሁሉ ማልዶ ተነሥቶ ውኃ መኖሩን ያረጋግጣል ፣ ለቁርስ የሚሆኑ ነገሮች በቤት እንዳሉ ይፈትሻል ፣ ቆሞ ያደረው መኪናው ዘይት አፍስሶ እንደሆነ ያጣራል  ። ሰው ግን ስለ መኪናውና ስለ ቁርሱ የሚያስበውን ያህል ስለ ነፍሱ አያስብም ። የሥጋ ጥጋቦቻችን ሁሉ እርካታ ያልሰጡን የነፍስ ጠኔ ስላለብን ነው ።
እነ ጴጥሮስ የመነሣቱን ዜና በመግደላዊት ማርያም ሰሙ ፣ ሮጠው ወደ መቃብሩ በመገስገስ አረጋገጡ ። ነገር ግን ዝምታን መርጠው ዋሉ ። እስቀድመው የሰሙት ወንዶች ቢሆኑ ኑሮ ሰብአዊ ኩራታቸው የምሥራቹን ታግሠው እንዲውሉ ያደርጋቸው ነበር ። ደስታቸውን ሊያጋሩ ሁልጊዜም ፈቃደኛ ለሆኑ ሴቶች ጌታ ትንሣኤውን ገለጠ ። እርሱ ለማን ምን መንገር እንዳለበት ያውቃል ።
መግደላዊት ማርያም ከመቃብሩ ባዶ መሆን ፣ ከመላእክት ምስክርነት በላይ ራሱን ጌታን አግኝታ ትንሣኤውን አረጋግጣለች ። ያ ቀን የዓርብ ዕለት ተቃራኒ ነበር ። ዓርብ ከማለዳው እስከ ምሽት የኀዘን ቀን ነበር ። እሑድ ደግሞ ከማለዳው እስከ ምሽት የምሥራች ነበር ። የዓርብን መከራ ያመኑ የእሑድን ደስታና ክብር ማመን አልቻሉም ። ጭንቅን የሚቀበል ደስታን የማይቀበል ፣ የሰይጣንን ሀልወት የሚያምን የእግዚአብሔርን መኖር የሚክድ ፣ በአዳም መኰነኑን የሚቀበል በክርስቶስ መዳኑን ችላ የሚል ፣ የምድርን አታካችነት የሚናገር የሰማይን ደስታ የማይቋደስ አእምሮ የሚደንቅ ነው ። ክፉ ነገር አገሩ እዚህ ነውና ይፈጥናል ። መልካም ነገር ደግሞ ይዘገያል ። በሰዎች ተጎዳሁ እያለ በክርስቶስ የማይጠቀም ፣ በምድር ተገፋሁ እያለ የሰማይን ምሰሶ የማይጨብጥ ፣ አጋንንት ተሰለፉብኝ እያለ የመላእክትን ተራዳኢነት የማይቀበል ፣ የሚጠሉትን እየተከተለ ለወዳጆቹ ጀርባው የሚሰጥ ፣ ቀሙኝ ብሎ እያለቀሰ ሲሰጡት የሚጠራጠር ፣ የክፋት ዜና መረረኝ እያለ የልማት ዜናን የማይወድ … የሚደንቅ ፍጡር ነው ። ሰው ሊጸልየው ከሚገባ ጸሎት አንዱ፡- “መከራዬን አስረሳኝ” ብሎ ነው ። አስተዳደጋቸው አኗኗራቸውን የሚዋጋባቸው ብዙ ናቸው ። የማጣት ዘመናቸው ዛሬ ወርቅ እንዳይለምዱና እንዲያግበሰብሱ ያደረጋቸው አያሌ ናቸው ። አንድ ወንድ ጎዳኝ ብለው ሺህ ወንድ የሚበቀሉ ፣ አንድ ሴት አታለለችኝ ብለው ሺህ ሴት የሚጠራጠሩ ብዙ ናቸው ። የዛሬው ኑሮ የሚበጠበጠው የትላንቱን መርሳት ባለ መቻላችን ነው ። ዓርብን ስላልረሱ እሑድን ሲተክዙ ዋሉ ። እግዚአብሔር ሲክስ ከተጎዳነው በላይ ነው ።
የትላንቱን መዘባበቻ መሆን ፣ የትላንቱን ከፀጉር የበዙ ጠላቶች ማስተናገድ ፣ የትላንቱን በአደባባይ መራቆት ፣ የትላንቱን የወደዱትን ማጣት ፣ የትላንቱን የአስገባሪዎች ክፋት ፣ የአስጨናቂዎችን ዘንግ ፣ የጫንቃውን በትር ፣ የጀርባውን ሰንበር መርሳት የዛሬን ትንሣኤ ለመቀበል አስፈላጊ ነው ። ደርግ አሥራ ሰባት ዓመት ጃንሆይን አልረሳም ፣ ሲራገም ነበር ። ሬሳ መደብደብ ጀግና አያሰኝም ። ያንን በደል ማውራት ጥቅም የለውም ። መካስ ግን ጥቅም አለው ። ደርግንም እስካሁን እንራገማለን ። አካሉ ሂዶ መንፈሱ አልሄድ ብሎን እንጨነቃለን ። የትላንቱን ተምረንበት መርሳት ያስፈልጋል ። ዛሬ ላይ ትላንትን መኖር አለማወቅ ነው ። እገሌ ጎዳን ከማለት እኔስ ምን ጠቀምኩኝ ? ማለት እውነተኛ ጥቄ ነው ። ሁለት ነገሮች ለሕክምና አስቸጋሪ ናቸው፡- ራስን አለመቀበልና ትላንትን አለመርሳት ። ክረምትና በጋ ፣ ደስታና ኀዘን የሕይወት ዑደት እንጂ አደጋ አይደሉም ።
ደቀ መዛሙርቱ የጌታን መነሣት ጠብቀዋል ። ሲነሣ ግን ማመን አቃታቸው ። ትልቅ ደስታ ማመን ይከለክላል ። ይህ ቅዱስ አለማመን ነው ። እየጠበቁም አለማመን አለ ። እየጠበቁ አይሁድ ክርስቶስን ሰቀሉ ። እግዚአብሔርን የማንቀበለው በእኛ ሥዕል ስለምንጠብቀው ነው ። እግዚአብሔር በእግዚአብሔር ብቻ የታወቀ ፣ እግዚአብሔር በራሱ መንገድ የሚሠራ አምላክ ነው ። ሲሆንና ሲፈጸም ለመቀበል አቅም የሚጠይቅ ደስታ አለ ። ደስታንም ለመሸከም አቅም ያስፈልጋል ። በዓለም ላይ እውነትን ለመሸከም አቅም ስለሚያስፈልግ መመጠን ያስፈልጋል ። የጋኑን በገንቦ እየገለበጡ ማፍሰስ ብክነት ነው ። እንዲህ ያለ የትንሣኤ ደስታ የዘመናትን ትካዜ ጠራርጎ የሚወስድ የብርሃን ጎርፍ ነው ። እሑድ ምሽት ላይ ደቀ መዛሙርቱ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋው እንዳልተሰረቀ አረጋግጠዋል ። በሥፍራው ማለት በመቃብሩ እናገኘዋለን ብለው ጠብቀው ስላጡት በስፍራቸው ሁነው ጠበቁት ። በስፍራው የተሰወረብንን ነገር በስፍራችን ሁነን መጠበቅ ግድ ነው ። መፈላለግ ያጠፋፋልና ።
የክርስቶስን መነሣት በግማሽ ልብ ቢቀበሉም ጠላቶቹ እስካላለቁ ደስታችን ሙሉ አይሆንም ብለው ያሰቡ ይመስላል ። በዚህም የነቢዩን ጸሎት ዘነጉ፡- “በጠላቶቼ ፊት ለፊት ራሴን በዘይት ቀባህ ” ይላል ። ጠላቶቼ እያዩ ፣ አለ እንጂ ጠላቶቼ ሬሳ ላይ ራሴን በዘይት ቀባህ አይልም ። የምንለምነው የጠላቶችን ሬሳ እንጂ የእግዚአብሔርን ዘይት አይደለም ። ሙት ግን ይዞ ይሞታልና ቅባቱ ይሻለናል ። የጠላት ድርብ ሞቱ የእኛን መቀባት ማየቱ ነው ። ጠላት ቅባታችንን ሊያጥብ ፣ ጸጋችንን ሊያራቁት ይነሣል ። እግዚአብሔር ግን በክብር ላይ ክብር ይጨምራል ። ሞት አንድ ጊዜ ነው ። ጠላት ደጋግሞ የሚሞተው ግን ቀበርሁት ያለው አደባባዩን ሲሞላው ነው ። ክርስቶስ ሲሰቀል ደቀ መዛሙርቱ በሕሊና ሙተው ነበር ። ክርስቶስ ሲነሣ ጠላቶቹ በሕሊና ሞቱ ።
አቤቱ ቅዱስ ዘይትህ አይለፈን ።
ይቀጥላል
የመስቀሉ ገጽ/ሐ
ግንቦት 17 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቀን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም