መግቢያ » ትረካ » በተዘጋው የሚመጣ » በተዘጋው የሚመጣ /4/

የትምህርቱ ርዕስ | በተዘጋው የሚመጣ /4/

 “ያም ቀን እርሱም ከሳምንቱ ፊተኛው በመሸ ጊዜ ፥ ደቀ መዛሙርቱ ተሰብስበው በነበሩበት ፥ አይሁድን ስለ ፈሩ ደጆቹ ተዘግተው ሳሉ ፥ ኢየሱስ መጣ ፤ በመካከላቸውም ቆሞ፡- ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው ።” /ዮሐ. 20፡19 ።/
ሦስት ዓይነት መሰባሰቦች እንዳሉ እናያለን ። ደቀ መዛሙርት በምሴተ ሐሙስ ፣ በሰንበት ፣ በእሁድ ምሽት የተሰባሰቡት መሰባሰብ ልዩ ልዩ ፍቺ አለው ። በምሴተ ሐሙስ ክርስቶስ መምህረ ፍቅር ወትሕትና ሁኖ ኪዳን ያደረጉበት ነው ። ሰንበት ሕግን በማክበር አንድ ላይ የሆኑበት ነው ። እሁድ ምሽት በፍርሃት ብርድ ተመትተው እንዲሞቃቸው የተጠጋጉበት ነው ። ከመከራ ሰዓቶች በፊት አስደናቂ ኅብረቶች ይታያሉ ። የክርስቶስን ፍቅር የሚካፈሉበት ፣ ትሕትናን እንደ ልብስ የሚታጠቁበት ውብ ጊዜዎች ያልፋሉ ። ይህን ኅብረት አንዳንድ ጊዜ መከራ ያፈርሰዋል ። መከራው የክርስቶስ ፣ ፈተናው ግን የደቀ መዛሙርቱ ነበረ ። እርሱ መከራ ለተቀበለ እነርሱ ተናወጡ ። እኛ ለተጎዳን ሰዎች መራቃቸውና መለወጣቸው ይገርመን ይሆናል ። በጌታችን የሆነውም ይህ ነው ። ሰንበት የሰበሰባቸው ሕግን መተላለፍ ስለማይችሉ ነው ። ሰንበትን የተላለፈ ታላቅ ቅጣት ይገጥመው ነበር ። የሕግ ቅንዓት የሚሰበስበው ኅብረት አለ ። ይቀጣ ፣  ይወገዝ ፣ ይወገድ ፣ ይወገር የሚሉ አንቀጾች አንድ የሚያደርጉአቸው ፣ በሌሎች ለመፍረድ የሚሰባሰብ ሸንጎ አለ ። ይህ ኅብረት ሰንበት ሲያልፍና መውጣት ሲቻል ይበተናል ። ጉዳያቸው ያሰባሰባቸው ጉዳያቸው ሲሞላ ይለያያሉ ። ድንበር ላይ የሚሰባሰቡ ድንበሩ ሲከፈት ይለያያሉ ። ሌላውን ለማጥፋት የሚሰባሰቡ በመጨረሻ ይጠፋሉ ። የእሑድ ስብስብም ፍርሃት የወለደው ስብስብ ነበር ። ብርድ ሲያንቀጠቅጠን እርስ በርስ እንጠጋጋለን ። የጋራ ችግርና ፍርሃት አንድ የሚያደርጋቸው ሰዎች አሉ ። እውነተኛ ኅብረት ግን በክርስቶስ ፍቅር ተማርኮ ፣ በክርስቶስ ትሕትና ለመኖር የሚፈልግ ነው ።

ለክርስቶስ ብዙ የሚጋደሉ ፣ እስከ ሞት ድረስም አብረውት የሚቆሙ የሚመስላቸው ደቀ መዛሙርት ስሜታቸውና እውነታቸው ተለያየ ። የተሰማን ሁሉ ቢሆን ጠቃሚም ጎጂም ነው ። ስሜት የእርግጠኛ ጉዳትና የአጠራጣሪ ጥቅም መገኛ ነው ። ብናገኝ ወርቅ የምናለብሳቸው የሚመስለን ሰዎች አሉ ። ስናገኝ ትዝ አይሉንም ። ስንሾም አማካሪ የምናደርጋቸው የሚመስሉን ሰዎች አሉ ። ስንሾም እንደ ተቀናቃኝ እናያቸዋለን ። ጊዜውን ስንቀበል በቅን እንደምንፈርድ እናስባለን ። ጊዜን ስንቀበል ግን ቅንቅን እንሆናለን ። ወዳጃችን ቢነካ ከፊት ለፊቱ ቆመን፡- “እኔን በመጀመሪያ ግደሉኝ” የምንል ይመስለናል ። ወዳጃችን ሲነካ ግን፡- “ይህ ዓለም ለደጎች አይሆንም” እያልን ሹልክ እንላለን ። ስለራሳችን ያለን ከፍ ያለ ግምትና ስለ ሰዎች ያለን ዝቅ ያለ ግምት በትንሣኤው መነጽር መስተካከል አለበት ። ስንት ዘመን ተፈትነን ቀለን ተገኘን ? ጎረቤታችን ተርቦ መቼ አካፈልነው ? የምንወደው ሰው ታሞ መቼ ጠየቅነው ? የሥራ ባልደረባችን ታስሮ መቼ ጎበኘነው ? በልጅነታችን በጣም ይወደን የነበረውን ያንን ሽማግሌ መቼ አሁን ፍቅር ሰጠነው ? እርሳስ የገዙልንን መቼ አስታወስናቸው ? ቃለ እግዚአብሔርን ያስተማሩንን መምህራን መቼ እግዚአብሔር ይስጥልኝ አልናቸው ? መስቀሉ ዛሬም አለ ። ትንሣኤም ዛሬ አለ ። መስቀል መሆንና መስቀል መሸከም ግን ልዩነት አለው። ለሌሎች መከራ መሆንና የሌሎችን መከራ መካፈል ልዩነት አለው ።
ብዙ ብናበላ ብዙ የሚደርስልን ወገን የምናገኝ ይመስለናል ። ይህ ፍጹም የተሳሳተ ግምት ነው ። ዓርብ ሲመጣ የበሉ አይገኙም ። እንዲሁ ደግ እንሁን እንጂ ለዓርብ/ለመከራ ቀን እያልን ገንዘባችንን አንጨርስ ። ዓርብ ሲመጣ እስከ መስቀል የሚጓዙ ወዳጆች ብቅ ይላሉ ። እነዚህ የማይፎክሩት እመቤታችንና ዮሐንስ ወንጌላዊን የሚመስሉ ናቸው ። በሩቅ የሚከተሉ ከኅሊና ክስና ከልብ ፍቅር ጋር የሚታገሉ ጴጥሮሶች አሉ ። ገበያ ከተገኘ የማይሸጥ የለም ብለው እንደ ይሁዳ የሚሸጡንም አሉ ። “መሸጥ የለመደ እናቱን ያስማማል” እንዲሉ ። ሰንበት የበለጠ ቁጭ ያደርጋል ። የሮጠም የበረረም የግድ መቀመጡ አይቀርም ። መቀመጥና ማረፍ ግን ልዩነት አለው ። መቀመጥ በሕግ ፣ ማረፍ ግን በክርስቶስ ነው ። ዓርብ ምሽት የገባው ሰንበት ቁጭ ባያደርጋቸው ኖሮ ደቀ መዛሙርቱ ኢየሩሳሌምን ለቀው ፣ ድንበርም ጥሰው ደማስቆ ይገኙ ነበር ። እስከ መጨረሻው እንዳንቀል እግዚአብሔር ሰንበትን ያመጣል ። እሑድ ጠዋት ጉዞ እንዳይጀምሩ መግደላዊት ማርያምን ላከባቸው ። ክህደትን ያልጀመረ የለም ፤ ያልጨረሰ እንጂ ። የሕይወት ሰንበት ሲመጣ ማለት በእስር ቤት ፣ በአልጋ ፣ በማጣት ፣ በብቸኝነት ስናሳልፍ ጨርሰን እንዳንጠፋ መጠበቂያ ነው ። እግዚአብሔር ምሽትን እያመጣ ሰውን ባይሰበስበው ኑሮ ስንቱ እቤቱ ሳይገባ ያረጅ ነበር ። ብቻ ዕድሜአችን ሲገፋ ዓለምን ለማትረፍ ክርስቶስን መካድ ከንቱ መሆኑን እንረዳለን ።
ቅዱሳን ሐዋርያት አይሁድን በጣም ፈርተው ነበረ ። አይሁድ እነርሱን እንዳይፈልጉም ክርስቶስ ቤዛ ሁኖላቸዋል ። ጨካኞች እኛን የማይፈልጉን ለእኛ ቤዛ የሆኑ ሰዎች ስላሉ ነው ። ያለ ቤዛ መኖር ይቅርና መዋል አይቻልም ። ተክሉ ተቆርጦ ሲቀቀል እኛን ለማጥገብ ነው ። ለማኖር መሞት አለበት ። በጉ ታርዶ ሲበላ ይህም እኛ እንድንኖር ዛሬ የሞተ እንስሳ አለ ማለት ነው ። ከበደል በኋላ ሕይወት ያለ ቤዛነት አይቀጥልም ። ደቀ መዛሙርቱ የፈሩት የሚያስፈራ ነገርን ሳይሆን የሚያስፈራራቸውን የአእምሮ ሥዕል ነው ። ራሱ ፍርሃት እንጂ ሌላ አስፈራሪ አልመጣባቸውም ። ፍርሃት ቁልፍ ይወዳልና የውጭውን በር ቆለፉት ። ፍርሃት ቁልፍ አይጠግብምና የሳሎኑን በር ከረቸሙት ። ፍርሃት ልክ የለውምና ወደ ሰገነቱ የሚያወጣውን የደረጃውን በር ቀረቀሩት ። ፍርሃት እስከዚህ አይልምና የሰገነቱን በር ዘጉት ። ይህ ሁሉ ሁኖ በፍርሃት ይናጣሉ ። የተዘጋው ደጅ ሳይሆን ደጆች ናቸው ። ከኤማሁስ የተመለሱ ሉቃስና ቀለዮጳ የሆነውን ሁሉ ተናገሩ ። ችግር ለየራስ ነውና የኤማሁስ መንገደኞች ተስፋ መቍረጥ ፣ ሐዋርያትን ደግሞ ፍርሃት ይዋጋቸው ነበር ። ተመስጠው ያንን የኤማሁስ ገጠመኝ ሲሰሙ ጌታችን በመካከላቸው ቆመ ። በር አልተንኳኳም ። በሩን ቢያንኳኳ ልባቸው የሚከዳቸው ፣ ደማቸው የሚፈላባቸው ብዙዎች ነበሩ ። ጌታ ግን አቅማቸውን አየ ። አዘነላቸው ። ያሉበት አቅም የበር ማንኳኳትን እንኳ የማይቋቋም እንደሆነ ተረዳላቸው ። የስልክ ጥሪ የሚረብሻቸው ፣ የደወሉለት ሰው ስልክ ካላነሣ የሚጨንቃቸው ፣ መረሳት የሚያስፈራቸው ፣ ለአትርሱኝ ሰው የሚበጠብጡ ብዙ ናቸው ። ጌታ ለእነዚህ ሁሉ ደንባሮች “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ይላል ።
ቅዱሳን ሐዋርያት የተነሣውን ጌታ በዓይናቸው አዩ ። እኛ ደግሞ በዓይናቸው ያዩት የመሰከሩልንን እናምነዋለን ። አይተው አመኑ ፣ አምነን እናያለን ። ከፊት ለፊት ያለውን ያመኑ ነቢያት ተባሉ ። ከኋላ ያለውን ያመኑ ሐዋርያት ተባሉ ። ነቢዩ ኢሳይያስ፡- “እነሆ ድንግል ትፀንሳለች” ብሎ ስለ አማኑኤል ተናገረ ፣ አመነ ። ሐዋርያት ክርስቶስ ከሞት እንደ ተነሣ አመኑ ። ከሞት ከተነሣ ሰው ጋር ግንኙነት አድርገን ብናውቅ ብዙ ነገሮች ይገቡን ነበር ። ከሞት የተነሣ ወዳጅ ስስት ነው ። ክርስቶስ ከሞት የተነሣ ወዳጃችን ነው ። እናቶቻችን፡- “የሞት ትራፊዬን አትንኩብኝ” ይላሉ  ። አዎ እርሱ ተነሥቷል እኛም እንነሣለን ። ከሞት በፊት የሚያውቁትን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት በኋላም አውቀውታልና እኛም በሰማይ እንተዋወቃለን ። በትንሣኤ አካል እንከን የለም ። ዛሬ ዓይኑ የታወረ ፣ እግሩ የሚያነክስ በትንሣኤ አካል ሙሉ ነው ። የማይታየው አብን ወልድ እንደ ተረከው ክርስቶስም ወደ ረቂቅ ግዛቱ ሲገባ ሐዋርያት ተረኩት ። እንዲተረክልን እንሰወር ።
ተፈጸመ
የመስቀሉ ገጽ 9/መ
ግንቦት 19 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም