የትምህርቱ ርዕስ | በቸርነቱ ያዳነን

“ነገር ግን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለ ጠጋ ስለ ሆነ ፥ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን ፥ በጸጋ ድናችኋልና ፥” ኤፌ. 2፡3-4 ።

እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለጠጋ ተብሏል ። የዚህ ዓለም ባለጠጎች በቁሳዊ ነገር ባለጠጋ ሊሆኑ ይችላሉ ። በምሕረቱ ባለጠጋ የተባለ ግን እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ምሕረቱ ከፍቅሩ ጠባያት አንዱ መገለጫ ነው ። የምሕረቱም ገጸ በረከት ቸርነቱ ነው ። ፍቅሩ እንዲሁ መውደዱ ነው ። ፍቅሩ ዓለም የተፈጠረበትና ዓለም የዳነበት መነሻ ነው ። ምሕረቱ አዳምን በገነት የፈለገበት የንስሐ ድምፅና ሰው የሆነበት ግብር ነው ። ቸርነቱ ተስፋን መስጠቱና ድኅነትን ማግኘታችን ነው ። ፍቅር ፣ ምሕረትና ቸርነት ተናባቢ ናቸው ። የአብ ጸጋ ፣ የወልድ ፍቅር ፣ የመንፈስ ቅዱስ አንድነት ከሁላችን ጋር ይሁን የሚለውን ለዋውጠን መጠቀም እንችላለን ። ጸጋ ፣ ፍቅር ፣ አንድነት መለኮታዊ ግብራት ሲሆኑ እግዚአብሔር ለፍጥረቱ የሚያደርጋቸው በጎነት ናቸው ። እነዚህ ጸጋ ፣ ፍቅርና አንድነት የአንድ መለኮት የባሕርይ ግብር ናቸው ። ፍቅሩን ስናስብ የእግዚአብሔርን ዘላለማዊ ምክር እናስባለን ። ምሕረቱን ስናስብ የወደቀን የሚፈልግና ንስሐን የሚወድ አምላክ መሆኑን እንገነዘባለን ። የነቢያት የሐዋርያት አገልግሎትም ንስሐን ለሰዎች ማወጅ ነው ። ቸርነቱ ደግሞ አማኝ የተባልንበት ነው ።

ወደ ምሥጢረ ሥጋዌ ስናመጣው ፍቅሩ እግዚአብሔር ወልድን ከሰማይ ያወረደ ፣ “ፍቅር ሰሐቦ ለወልድ ኃያል እመንበሩ ፣ ወአብጽሖ እስከ ለሞት” የተባለበት ነው ። ምሕረቱ ደግሞ በመስቀል ላይ የዋለበት ቤዛነት ነው ። ቸርነቱ የድኅነት ጸጋን የተቀበልንበት ነው ። ምሥጢረ ሥጋዌ ሦስት ክፍሎች አሉት ። የመጀመሪያው ሰው የመሆኑ ምሥጢር ነው ፤ ሁለተኛው በመስቀል ላይ የፈጸመው የቤዛነት ሥራ ነው ። ሦስተኛው የዳነች አንዲት ቤተ ክርስቲያን ወይም ማኅበረ ምእመናን የተመሠረተችበት ነው ። ሰው መሆኑን ፣ ማዳኑንና መዳናችንን አስተባብረን ማየት ይገባል ። ድንሃል የሚለው ቋንቋ ቁንጽል ነው ። ለመዳን የተከፈለውን ዋጋ ማሰላሰል ፣ የመዳንንም ዓላማ ማለትም ቅድስናን ማሰብ ይገባናል ።

በአዳም በደለኞች ተብለን ፣ የበደል ዋጋ የሆነው ሞትም ደርሶብን እንኖር ነበር ። ያ ማለት ግን ጽድቅ መሥራት የማንችልበት የተበከለ ማንነት ተቀበልን ማለት ሳይሆን የአባት ዕዳ ለልጅ መትረፉ እርግጥ ስለሆነ ነው ። አቤል ጻድቅ ነበረ ። ኖኅም በቅድስና ተመላልሷል ። እነዚህ ሁሉ ግን ፍጹማን አልነበሩም ። አዳም ከመበደሉ በፊት የነበረውን ሐዲስ ተፈጥሮ አላገኙትም ። ከሰማዕትነት የሚቆጠረውን ሥጋን እንቢ ማለት ግን ፈጽመዋል ። የአዳም ኃጢአት ያዘጋውን ገነት የእነዚህ ሁሉ ጽድቅ ማስከፈት አልቻለም ። ስለዚህ በቀዳማዊ አዳም የተዘጋ በር በዳግማዊ አዳም በክርስቶስ ተከፈተ ። ይህም ስለሚገባን ሳይሆን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለጠጋ ስለሆነ ነው ። የትኛውም የሰውና የመላእክት በደል ከእግዚአብሔር ምሕረት በላይ አይደለም ። ምሕረቱ ግን አስፈቅዶ ያድናል እንጂ አስገድዶ አያጸድቅም ። ገነት ባልተከፈተበት ዘመን ፣ በመካነ ሲኦል ቅድሳን ቢኖሩም በረድኤተ እግዚአብሔር ተከልለው ይኖሩ ነበር እንጂ እንደ ሌሎቹ ኃጢአተኞች ቅጣትን አላገኙም ። ለዚህም በሉቃ. 16፡19-31 ያለውን ማንበብ ይቻላል ። ሙሴና ነቢያት በነበሩበት ዘመን አብርሃም በረድኤተ እግዚአብሔር ተከልሎ በዓለመ ነፍስ ይኖር ነበር ። የእግዚአብሔር ምሕረት ኃጥኡን ለንስሐ ማብቃት ብቻ ሳይሆን ጻድቁ ከክፉዎች ጋር እንዳይቀጣም ይከልል ነበር ።

የወደደን እግዚአብሔር ነው ። ፍቅሩም በመልኩ በአምሳሉ እኛን የፈጠረበት ፣ የማይሞተው አምላክ ሥጋ ለብሶ የሞተበት ነው ። በዚህ ዓለም ላይ ብዙ ፍቅሮች ቢኖሩም ይህ ፍቅር ትልቅ ነው ። ከዘላለም ሞት አይደለም ከሥጋ ሞት የሚያድን ፍቅር በዓለም ላይ የለም ። ትልቁ የእግዚአብሔር ፍቅር ግን በማዳን የበረታ ነው ። እርሱ የወደደን ያልበደለውን ማንነታችንን ብቻ ሳይሆን በደልና ኃጢአት ሙታን አሰኝቶን በነበረ ሰዓትም ወዶናል ። የሞት አጋፋሪ የሆኑት የሥጋ ፈቃድና የዓለም ምኞት እያንገላቱን ዛሬም ይወደናል ። ፍቅሩ ግን ባለንበት ኃጢአት እንድንጸና ፣ አይቶ እንዳላየ የሚያልፍ ሳይሆን ለንስሐ እንድንበቃ የሚተጋልን ነው ። በፍቅሩ ኃጢአተኞችን ቢወድድም ፣ በጻድቅነቱ ደግሞ ኃጢአትን ይጠላል ። በደልና ኃጢአት በዚህ ዓለም የሕሊና ሙት ወይም ሙታነ ሕሊና ሲያደርግ በሚመጣው ዓለም ደግሞ ዘላለማዊ ሙት ያደርጋል ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመሞቱ ተነሣ ተብሎ ተነግሮለታል ። ስለ እኛ ሞተ ፣ እኛን ይዞ ተነሣ ። ከክርስቶስ ጋር ሕይወትን አግኝተናል ። መንፈስ ቅዱስም አማኙን ከክርስቶስ ጋር የማዋሐድ ሥራ ይሠራል ። በክፉ ሥራችን ከገነት ብንወጣም ፣ በደግ ሥራችን የገነት ደጃፍን ማስከፈት አልቻልንም ። በክርስቶስ ቤዛነት ፣ በመስቀሉ ሥራ የገነት ደጅ ተከፈተ ። የዳንነው በጸጋው ነው ። በሥራችን ሞተን ፣ በሥራችን አልዳንም ። አዳም ለማስኰነን በቂ ነበረ ። ክርስቶስም ሊያጸድቀን ተቻለው ። በጸጋ ድናችኋል ማለትም በቸርነቱ ድናችኋል ማለት ነው ። ኦርቶዶክሳዊነት ቤተ ክርስቲያን ድኅነተ ዓለምን ትመሰክራለች ። በድናችኋል ስም ግን እምነትና ምግባርን ፣ ሃይማኖትና ምሥጢራትን አትለያይም ። ድናችኋል ኃጢአትን የምንጥልበት እንጂ ምግባርንና ምሥጢራትን እንዲሁም አገልጋይ ካህናትን የምንገፋበት አይደለም ። ድነሃል የሥጋ አርነት መስደጃ ፣ የራሱ ጉዳይ ተብሎ ሁሉን ነገር ማስጣያ አይደለም ። ሰው የዳነበትን መንገድና የዳነበትን ዓላማ በቅጡ መማርና ማወቅ አለበት ። ከነገረ ሥጋዌ የተነጠለ የድኅነት ትምህርት የማያድን ትምህርት ነው ። ይህን የምንለው የዛሬ ሁለት ሺህ ዓመት የተፈጸመውን መዳንና ሁለት ሺህ ዓመታት የተሰበከውን ወንጌል ሰበር ዜና አድርገው የሚያቀርቡና ለእናታቸው ምጥ የሚያስተምሩ ወገኖች ስለፈሉ ነው ። ክርስቶስ ያዳነን የዳነ ማንነት እንዲኖረን እንጂ እገሌ የዳነ ነው ፣ እገሌ ያልዳነ ነው የሚል ሰንጠረዥ እንድንሠራ አይደለም ።

ድኅነትን ስናስብ ፍቅሩን ፣ ምሕረቱንና ቸርነቱን የሚያዘክር ሕሊና ያብዛልን !

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /31

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 10 ቀን 2014 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም