መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የዕለት መና » በነፍስ ለዛላችሁ

የትምህርቱ ርዕስ | በነፍስ ለዛላችሁ

“በነፍሳችሁ ዝላችሁ እንዳትደክሙ፥ ከኃጢአተኞች በደረሰበት እንዲህ ባለ መቃወም የጸናውን አስቡ።” ዕብ. 12፡3 ።
“አንቺው ጠሪ አንቺው ቀሪ” ይባላል ። እኛ ያሳመናቸው እያመኑ እኛ ማመን ሲያቅተን ፣ እኛ ጸሎት ያስለመድናቸው እየጸለዩ እኛ መጸለይ ሲከብደን ፣ እኛ ፍቅርን ያስተማርናቸው እያፈቀሩ እኛ ጠብ ሲናፍቀን ፣ እኛ አሥራት ማውጣት ያለማመድናቸው እያወጡ እኛ ንፍገት ሲጫጫነን ፣ እኛ መዝሙር መልካም ነው ያልናቸው እየዘመሩ እኛ አሸሼ ገዳሜ ሲያምረን ፣ እኛ ታገሡ ያልናቸው ሲረጋጉ ፣ እኛ ማበድ ሲጀማምረን ፣ እኛ የስብከት አትሮኖንስ ለቀንላቸው ሲሰብኩ እኛ ፖለቲካ ሲያምረን ፣ … እኛው ጠሪ እኛው ቀሪ መሆናችን ነው ። ወደ እግዚአብሔር ቤት ያመጣናቸው ሰዎች ስላሉ ብቻ ቤተ ክርስቲያን መሄድ ፣ እልህ ስላለብን ብቻ መስበክ ፣ አልጠፉም ላለመባል መዘመር ዝለትን የበለጠ እያፋፋመው ይመጣል ።
“በሰም የተጣበቀ ጥርስ ቢስቁበት አያደምቅ ፣ ቢበሉበት አያደቅ” ይባላል ። ጥርሱ ሲታይ የሚቆርጥ ፣ የሚያደቅ ፣ የሚመነጭቅ ፣ የሚቦጭቅ ይመስላል ።በርቀት ላለ ማስፈራሪያ ነው ። ቢቀርቡት ግን እንደ ነገሩ የተያያዘ ነው ። ለሳቅም ለማኘክም የማይሆን ነው ። ደስታንም መከራንም የማይችል ነው ። ሲስቅም ተጨንቆ ፣ ሲያኝክም ፈርቶ ነው ። የተጣበቀው በደካማው በሰም ነውና ። ሐሰተኛ ሳቆች ፣ የፉከራ ድምፆች ፣ ጌታን የያዘ ምን ይሆናል ? የሚሉ መግደርደሮች ፣ በትንሽ ፈተና የሚደነብሩ ማንነቶች እያንዣበቡን ይመስላል ። ለሳቅም ለኀዘንም ስሜት አልባ መሆን ከባድ ነው ። ይህ የነፍስ ዝለት ይባላል ። ስለ ባል ስለ ሚስት ብቻ አማኝ መምሰል በሰም የተጣበቀ ጥርስ ነው ። ስለ አባቶች ቊጣና ተግሣጽ ብቻ ወደ እግዚአብሔር ቤት መገስገስ ይህ በሰም የተጣበቀ ጥርስ ነው ። ተቃዋሚዎች ስላሉ ብቻ ለአገልግሎት ተፍ ተፍ ማለት ይህ በሰም የተጣበቀ ጥርስ ነው ። እውነተኛ መከፋትን ደብቆ የሌለንን ደስታ ማውራት ይህ በሰም የተጣበቀ ጥርስ ነው ። መግደርደር የበዛበት ኑሮ ፣ ለመስጠትም ለመቀበልም የማይመች ሐሰተኛ አኗኗር በሰም የተቀባ ጥርስ ነው ።
ዝለት በአንድ ጊዜ የሚመጣ አይደለም ። ዝለት የብዙ ድካሞች ጥርቅም ነው ። አንድ ነገርን ያለ ታዳሽ ኃይል የያዙ ሰዎች ዝለት ውስጥ ይገባሉ ። በነፍስ ዝለት የተያዘ ሰው ራሱን እየፈራ የሚኖር ሰው ነው ። የያዘውን ኃላፊነት በሙሉ ድንገት የሚጥለው እየመሰለው የሚበረግግ ነው ። ዝለት በድንገት ፀሐይ ስትጨልም የሚፈጠር ስሜት ነው ። ዝለት የያዝነውንና የያዘንን መልቀቅ ነው ። እግር ድንገት ሽብርክ ሲል ፣ እጅም ዛል ብሎ የያዘውን ሁሉ ሲዘረግፍ ዝለት ይባላል ። ድንገት እንደ ብራቅ ብልጭ ብሎ መናገር ፣ እንኳን ዝናብ እሳት ለምን አይዘንብም ብሎ ደፋር መሆን ፣ ለሰው ሁሉ ያለንን በጎ አመለካከት መጣል ፣ የሠራነውን ሁሉ ተግተን ስናፈርስ ፣ ቀትሩ ሲጨልምብን ፣ ሁሉም ነገር ድግግሞሽ ሲሆንብን ይህ የነፍስ ዝለት ነው ። ጠዋት ስንነሣ ተኝቶ ያደረ ሰው ሳይሆን ሲሠራ ያደረ ሰው ያህል ስብርብር ስንል ፣ ደስ ብሎን እናደርገው የነበረውን እንደ ተጋዘ እስረኛ በግዳጅ ስንፈጽም ፣ ሊመጣ የሚችለውን ማንኛውንም አደጋ መድፈር ስንጀምር ይህ የነፍስ ዝለት ነው ። ዝለት ውስጥ ስንሆን በጣም ልንመገብ አሊያም መመገብ ሊያስጠላን ይችላል ። የሚሆነው ባለፈው የሆነው ፣ የሚደረገው ሲደረግ የነበረ ይሆንብንና ድግግሞሽ እንጂ አዲስ ነገር የለም የሚል ስሜት ውስጥ እንገባለን ።
የዕብራውያን መልእክት ፀሐፊ የዝለት መነሻዎችን ይጠቅስልናል ። የቀደሙትን የቅዱሳን ሕይወት ማሰብና ማሰላሰል አለመቻል ዝለት ውስጥ ይከተናል ። ቅዱሳን በተጋድሎ ብቻ ሳይሆን በብዙ ፈተና ወስጥም ያለፉ ናቸው ። ዳዊት በእኔና በሞት መካከል አንድ እርምጃ ብቻ ቀረ እስኪል ተስፋ ቆርጧል ፣ ነቢዩ ኤልያስም ግደለኝ ብሎ ለምኗል ፣ ነቢዩ ዮናስም ከእግዚአብሔር ፊት ኮብልሏል ። የቅዱሳንን ሕይወት ስናስብ እንደገና እንበረታለን ። ገድለ ቅዱሳን እንዳንዝልና ከዛልንም እንድንበረታ ያደርገናል ። እንግዲህ እነዚህን የሚያህሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን” ይላል ። ዕብ. 11፡1 ። ምስክርነታቸው ሃይማኖት የሚፈጸም ሩጫ መሆኑን የሚናገር ነው ። ካዩት ፣ ከሰሙት ፣ ከቀመሱት ፣ ከተሸለሙት ቅዱሳን ይመሰክሩልናል ። እንደ እኛ ያምኑ የነበሩ ፣ በእምነት ግን ብዙ የተጋደሉ እንዳሉ መስማት ከነፍስ ዝለት ያነቃል ። ለልጆች በትምህርት ቤት ስለ አገር ጀግኖች የሚነገራቸው ጎበዝ እንዲሆኑም ነው ። ክርስትና በብዙ ዋጋ የቆመ መሆኑን እንድናውቅና በክብር እንድንይዘው ገድለ ቅዱሳን በጣም ያግዘናል ። “የሰማዕታት ደም የቤተ ክርስቲያን ዘር ነው” ይባላል ።
ወደ ነፍስ ዝለት የሚያደርሰን ሌላው ነገር “ሸክም” ነው ይለናል ። ሸክም ኃጢአት አይደለም ወደ ኃጢአት የሚያደርስ ዋዜማ ነው ። አጉል ባልንጀርነት ፣ የማይገቡ ፊልሞችና ንባቦች ፣ ከንቱ ጨዋታዎች  እነዚህ ሁሉ ለክርስትናችን ሸክም ናቸው ። ሰይጣን በሸክም ካዳከመ በኋላ በኃጢአት ይጥለናል ። ሌላው የዝለት መነሻ ኃጢአት ነው ። ኃጢአት ዛሬ በስሙ ልንጠራው ያልቻልነው ብዙ የዳቦ ስም ያበጀንለት ነው ። ዘመናዊነት ምንድነው ስንል ኃጢአትን የማቆንጀት ባሕል ነው ። የነፍስን ዝለት የሚያመጣው ሌላው ነገር ክርስቶስን አለመመልከት ነው ። አገልጋዮችንም መመልከት ዝለት ያመጣል ። ከአገልጋዮች ጋር ያለን ግንኙነት ከአገልግሎታቸው ጋር እንጂ ከኑሮአቸው ጋር መሆን የለበትም ። ድንበራችንን ካላወቅን እየሳትን እንመጣለን ። መመልከት ያለብን የጥሪውን ባለቤት ነው ። ሰርግ ቤት የሄደ ሰው የሚያየው የሰርግ ወረቀቱን ያመጣለትን ሰው ሳይሆን የጠራውን ሙሽራ ነው ። ፈረንሳዮች፡- “ወደ ቤተ ክርስቲያን በቀረብህ ቊጥር ከአምላክ ትርቃለህ” ይላሉ ። ወደ አስተዳደሩ ፣ ወደ አገልጋዮቹ የግል ሰብእና እየቀረብን ከመጣን እግዚአብሔርን ልናጣ እንችላለን ። ምክንያቱም በቤተ ክርስቲያን የተፈቀደልን መንፈሳዊነታችንን ማጠናከር ነውና ።
መሮጥ አለመቻል የነፍስ ዝለትን ያመጣል ። ወደ ክርስትና ስንመጣ በጀመርነው ትንፋሽ እየሮጥን ካልሆነ ዝለት ይመጣል ። ለመሄድ የተሠራ መኪና ሲቆም መዛግ ይጀምራል ። ሰማይን ወደብ አድርጎ የጀመረ ክርስትናም ካልሮጠ ፣ በትናንሽ ነገር ከቆመ ዝለት ይገጥመዋል ። ሩጫው በግራና ቀኝ ደጋፊ ሳይሆን ተሳዳቢ ያለው ነውና በሰማይ ያደሩትን ቅዱሳን እያሰብን በትዕግሥት መሮጥ ይገባናል ። ሊያባሩ ያልቻሉ መከራና ፈተናዎችም ወደ ነፍስ ዝለት ያደርሱናል ። ሰንሰለታማ የሆኑ ችግሮች ድንገት እንድንሰለች ያደርጉናል ። የዚህን ጊዜ የተሰቀለውን ጌታችንን ማሰብ ያስፈልገናል ። ሌላው የዝለት መነሻ ዘወትር የሚጥለን የግል ድካማችን ነው  ። የሚያበሳጩን ከጎናችን ያሉ ብቻ ሳይሆኑ በውስጣችን ያለው ኃጢአትም ነው ። ከኃጢአት ጋርም ነጻ ትግል ለማድረግ ብናስብም መልሰን እንሸነፋለን ። ሐዋርያው እንደገለጠው እስከ ደም ጠብታ ከኃጢአት ጋር መታገል ያስፈልገናል ። ተራ ትግል ሳይሆን ብርቱ ጦርነት መሆኑን ማሰብ ከነፍስ ዝለት ይታደጋል ።
የነፍስ ዝለት ሲሰማን ልናደርገው የሚገባን ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብና ማጥናት ቀዳሚው ነው ። ሸክም የሆኑብንን ነገሮች ቆርጠን መጣል ወሳኝ ነው ። ይበልጥ ክፉ ባልንጀርነቶችን መበጠስ ያስፈልገናል ። በኃጢአታችንም ንስሐ ገብተን ከእግዚአብሔርና ከራሳችን ጋር ሰላም መፍጠር ግድ ይለናል ።ዘወትርም የጠራንን ጌታ እንጂ ማንንም ማየት አይገባንም ። ገና በፈተና ላይ ያሉት ሰዎች ሳይሆን በሰማይ ያደሩትን ፣ ተጋድሎአቸውን የፈጸሙትን ቅዱሳን ማየት ይገባናል ። ሩጫው መልካም ቢሆንም ደጋፊ ሳይሆን ተቃዋሚ ያለበት መሆኑን በማሰብ በትዕግሥት መሮጥ ይገባናል ። ሯጩ የሚሮጠው የሚሸልመው ዳኛ እስካለበት ድረስ ነው ። እውነተኛው ዳኛ ፣ በጽዮን የነገሠው ክርስቶስ ጋ እስክንደርስ መሮጥ አለብን ። ያለነውም ጦር ሜዳ እንጂ ኳስ ሜዳ አለመሆኑን ማሰብ ያስፈልገናል ። ከነፍስ ዝለት ክርስቶስ ያተርፈናል ።
በላይ በሰማይ በዙፋንህ ላይ ፣ በታች በምድር በትንሿ ልቤ ላይ ላለኸው ፣ ሰጠ እንጂ አጣ ለማትባለው ለአንተ ለአምላኬ ክብርና ምስጋና አቀርባለሁ ። ሰማይን ወደብ አድርጌ እንድሮጥ ፣ አንተን ብቻ እያየሁ እንድበረታ ጸጋህ ያግዘኝ ። ያደከሙኝን ነገሮች አድክማቸው ። የበረቱብኝን ድል ንሣቸው ። በዘላለም ክብርህ አሜን ።
የዕለቱ መና 30
ግንቦት 30 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም