መግቢያ » ከመጻሕፍት » ወዳጄ ሆይ » በአሳብ መለያየት መነጋገርን አይከለክልም ።

የትምህርቱ ርዕስ | በአሳብ መለያየት መነጋገርን አይከለክልም ።

 

ወዳጄ ሆይ !

ክርስቲያን ማለት ክርስቶስ በምድር ማለት ነው ። ስለዚህ በበረት ብትወለድም በድህነት ቤትህ አትፈር ። ብትሰደድም ግብጽን አስታውስ ። ለሚያንሱህ ታዛዥ በመሆንህ ቢከፋህ በባሪያ እጅ መጠመቁን አስብ ። ያለ ስህተትህ ብትከሰስ ኃጢአት ሳይኖርበት እንደ ኃጢአተኛ የተቀጣውን መድኅን አስብ ። ሳምራዊቷን ሴት ፍለጋ በቀትር ፣ ኒቆዲሞስን ለማገልገል በእኩለ ሌሊት ትጋ ። ከቀራጮች ጋር ለመብላት ፣ ኃጢአተኞችን ለማቀፍ ዝግጁ ሁን ። ከሞት ስትነሣ ፣ ማጣትህ በማግኘት ፣ መሰደድህ በሥልጣን ሲተካ የካዱህን ጴጥሮሶች ፍለጋ ውጣ ። 

ወዳጄ ሆይ !

ያለ እግዚአብሔር መቍጠር ሲቆጥሩ መኖር ነው ። ያለ እግዚአብሔር ማሰብ መዋተት ነው ። የክርስቶስ ሰላም ገንዘብ የማይገዛው ፣ ዕረፍቱም ያማረ ቤተ መንግሥት የማይሰጠው ነው ። እግዚአብሔር ያብጀው ብለህ ስትቀመጥ እርሱ ይሠራዋል ። እግዚአብሔር ያውቃል ብለህ ስታምን በእውቀቱ ያጸድቅሃል ። ያለማቋረጥ የምትጸልየው ያለ ማቋረጥ ለመቀበል አይደለም ። 

ወዳጄ ሆይ !

ልብ ብርሃን የምትሆነው በአራት ነገሮች ነው ። የመጀመሪያው የፍቅር ፊት ስታይ ፣ ሁለተኛ መልካም ወሬ ስትሰማ ፣ ሦስተኛ ስትጸልይ ፣ አራተኛ እግዚአብሔር አዋቂ ነው ብላ ስታምን ነው ። ነፍስ ካልተረጋጋች ሥጋ ሲንቀጠቀጥ ይኖራል ። የቀኑን ትግል አንተ ትግል ትለዋለህ ፣ እግዚአብሔር ግን የጸሎት ርእስ ይለዋል ። እግዚአብሔር እንኳን በአፍህ በልብህ የተመካኸውንም ያፈርሳል ። ትምክሕት ሲሰማህ “ሁሉ ባንተ ነው ጌታዬ” በማለት ክብርን ለአምላክህ ስጥ ። በአፍህ ምስጋና ሲሞላ በልብህ ደስታ ይሞላል ። በእጅህ ስትጎርስ በልብህ አመስግን ፤ ያን ጊዜ ሆድህና መንፈስህ እኩል ይጠግባሉ ።

 

ወዳጄ ሆይ !

አምነህ እየተኛህ አምነህ መውጣትን አትፍራ ። ስትበላ ድሀ አደጎችን ፣ ስትጠጣ በበረሃ የሚኖሩትን ፣ ስትለብስ የተራቆቱትን ፣ ወደ ቤትህ ስትገባ ጎዳና የወደቁትን ፣ ስትተኛ ዕረፍት ያጡ በሽተኞችን ፣ ስትሠራ ሥራ ያጡትን ፣ ስትራመድ እግር አልባዎችን ፣ … አስብ ። ሁሉን መርዳት ባትችልም አንዱን መደገፍ የዓለምን ሥቃይ መቀነስ ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

በፈተናህ ሰዎችን ተጠያቂ ከማድረግ እግዚአብሔር ያስተማረህን ማስታወስ ያጽናናል ። ሰዎች ካደረሱብህ ጉዳት የደረሰልህ መድኃኔ ዓለም ይበልጣል ። ትንሽዋን ጎጆህን እንደ ቤተ መንግሥት ካልቆጠርካት ቤተ መንግሥት ቢሰጥህም እንደ አማረ እስር ቤት ይሆንብሃል ። በቅናት ያደገ እኔን ብቻ ይድላኝ ይላል ። በምቀኝነት ያደገ አብረን እንጥፋ ይላል ። በዝቅተኛነት ስሜት ያደገ ጌጥ የማይጠግብ ይሆናል ። 

ወዳጄ ሆይ !

ተሳዳቢን ዝም የምታሰኘው ስድቡን ስትዝናናበት ነው ። የሚቀኑብህን የወለደው ያለህ ነገር ነው ። ቅናት ከፍ ያለበት ሰው በበሽተኛም ይቀናል ። ለምታስለቅስህ ዓለም ስቀህ ጠብቃት ። ይህ ከንቱ ዓለም እንደ ውሻ ሲሮጡለት ይከተላልና ደፍረህ ፈተናን ተጋፈጥ ። ካልደፈረሰ አይጠራም ስትል መጀመሪያ ያንተ ቤት እንዲደፈርስ መፍቀድ አለብህ ። በሌላው ሞት “እግዚአብሔር ሰጠ ፣ እግዚአብሔር ነሣ” ትላለህ ፣ ባንተ ጉዳይ ግን “እኔ አገኘሁ ፣ እግዚአብሔር ወሰደ” ባይ ነህ ። 

ወዳጄ ሆይ !

ትምህርት ሰብእናን ካልገነባ መቅረት አለበት ። ማለዳ ስትነሣ ምንም የለኝም አትበል ፤ ገና ያልተነካ የ24 ሰዓት ሀብት አለህ ። ቤትህ ሲቃጠል እየጮኽ ፣ በሲጋራ እሳት አንተ ባለቤቱ ስትቃጠል ግን ዝም ትላለህ ። ያለ ራእይ የሚኖር ብዙ ነው ፣ ያለ ራእይ የተፈጠረ ግን አንድም የለም ። አንተ ባለቤቱ ካልታየህ ሰዎች ስላዩልህ አትራመድም ። ትዳር ማለት አብሮ መወለድና አብሮ መሞት ሳይሆን አብሮ መጓዝ ነውና ተስማማ ። በአሳብ መለያየት መነጋገርን አይከለክልም ። 

መድኅን ክርስቶስ ሆይ የተለያዩትን አንድ አድርግ ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ኅዳር 18 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም