የትምህርቱ ርዕስ | በክርስቶስ ነን ?

“በክርስቶስ ኢየሱስም ላሉት ምእመናን ፤” ኤፌ. 1 ፡ 1 ።

ክርስቶስ ኢየሱስ እውነተኛው የወይን ግንድ ነው ። የወይን ግንድ ስስ የሚመስል በቀላሉ ግን የማይበጠስ ነው ። ክርስቶስ ኢየሱስም ትሑት ነው ፣ ነገር ግን ሞት በፊቱ የሰገደለት ነው ። የወይን ግንድ በተገረዘ ጊዜ ብዙ ያፈራል ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም በመስቀል መከራው ብዙዎችን ገንዘብ አድርጓል ። የወይን ግንድ ማረፊያ ይፈልጋል ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም በሰዎች አድሮ ይሠራል ። የወይን ግንድ ጥላ ይሆናል ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም ብዙዎችን ከቃጠሎ ያሳርፋል ። የወይን ግንድ ፍሬውን ከላይ ወደ ታች ይሰጣል ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም ሰማያዊ ጸጋውን አፍስሷል ። የወይን ግንድ ልምላሜው ይማርካል ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም ብዙዎችን በፍቅር ይቀበላል ። የወይን ግንድ መልክ የለሽ ሲሆን ቅጠሉ ማራኪ ፍሬው ጣፋጭ ነው ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም ስለ እኛ ደም ግባቱን አጥቶ ምእመናንን ውብ ፣ አገልጋዮቹን ጣፋጭ ፍሬ ያደረገ ነው ። የወይን ግንድ መንገድ ከሰጡት ርቆ ይሄዳል ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም ፍቅሩ ለሁሉ ይበቃል ። የወይን ግንድ በፍሬው ይከበራል ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም በአማኞቹ ደግነት ሲመሰገን ይኖራል ። የወይን ግንድ መልኩ አፈር ፣ ቅጠሉ አረንጓዴ ፣ ፍሬው ቀይና ነጭ ነው ። መልኩ አፈር የመሰለው ግንድ ሰው መሆኑን ፣ አረንጓዴው ቅጠል በእርሱ ደስ የተሰኙ ምእመናን ፣ ቀይና ነጭ ፍሬው መሥዋዕትነትና ቅድስና ያለበት የምእመናን ሕይወት ነው ። የወይን ግንድ ባይንከባከቡትም ለመድረቅ አይቸኩልም ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም የጠሉትን ቶሎ አይቀየምም ። የወይን ግንድ የለም ሲባል ይኖራል ፣ ክርስቶስ ኢየሱስም ገደልነው ሲሉ ተነሥቷል ።

“እውነተኛ የወይን ግንድ እኔ ነኝ ፤ ገበሬውም አባቴ ነው” ይላል ። ዮሐ. 15 ፡ 1 ። ገበሬን እንንቅ ይሆናል ፣ እግዚአብሔር አብ ግን ገበሬ ተብሏል ። አናጢን መቀበል ያቅተን ይሆናል ፣ ክርስቶስ ኢየሱስ ግን የመረጠው ሙያ ነው ። ውኃን ከቀለብ አንቆጥረው ይሆናል ፣ መንፈስ ቅዱስ ግን የሕይወት ውኃ ተብሏል ። አህያ እያልን እንሳደባለን ፣ ክርስቶስ ኢየሱስ ግን ንጉሠ ሰላም ሁኖ የገባው በአህያ ውርንጫ ተቀምጦ ነው ። ገበሬ ወይንን ቢተክለው እንጂ አይፈጥረውም ፤ መትከልም መውለድ ነው ። ተካይ ገበሬ የልጅ ልጁ ፍሬው ነው ። እግዚአብሔር አብም ወልድን ቢወልደው እንጂ አይፈጥረውም ። ገበሬ ስለ ተክሉ ይናገራል ፣ እግዚአብሔር አብም የምወደውና የምመለክበትን ልጄን ስሙት ብሏል ። ገበሬ ፍሬውን ይለቅማል ፣ እግዚአብሔር አብም የልጁ የደሙ ፍሬዎችን ይሰበስባል ። ገበሬ በፍሬው ይመሰገናል ። እግዚአብሔር አብም በምእመናን አንደበት “የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አባት እግዚአብሔር ይመስገን” ይባላል ። ገበሬው አብ ፣ ግንዱ ክርስቶስ ፣ ውኃው መንፈስ ቅዱስ ፣ ቅርንጫፍ ምእመናን ፣ ፍሬው ሥነ ምግባር ነው ። ወይን የዕለተ ሠሉስ/የማክሰኞ ተፈጥሮ ነው ፣ ሰው የዕለተ ዓርብ የስድስተኛው ቀን ተፈጥሮ ነው ። ወይኑ በዕድሜ ሰውን ይበልጣል ። ሰው ግን የወይኑ ጌታ ሁኗል ። ይህ ምሥጢር ግሩም ነው ። እግዚአብሔር አብ ግን ዘመን ሳይቆጠርለት አባት የተባለው ዘመን የማይቆጠርለት ልጅ ስላለው ነው ። ዘላለማዊ አባትነት ዘላለማዊ ልጅ ይፈልጋል ። ልጅ በሌለበት አባት መባል የለምና ። አብም ያለ ወልድ የኖረበት ቅጽበት የለም ። ከአባቱ ጋር በዘመን እኩል የሆነው ልጅ ምስጋና ይገባዋል ።

ቅርንጫፍ ምእመናን ከወይኑ ግንድ ጋር መጣበቅ አለባቸው ። ቅርንጫፉ በወይኑ ላይ አለ ። ወይን ብዙ ቅርንጫፎች እንዳሉት ክርስቶስም ብዙ ልጆች አሉት ። ቅርንጫፍ በራሱ ሕይወትም ፍሬም የለውም ፣ ምእመንም ያለ ክርስቶስ ሕይወትም ቅድስናም የለውም ። ከፍሬ ሕይወት ይቀድማል ። ከሥነ መግባርም በፊት ሃይማኖት ያስፈልጋል ። እውነተኛው የወይን ግንድ እውነተኛ የወይን ቅርንጫፍ ያሰኘናል ። አቡሀ ለሐሰት የተባለውን የሰይጣንን ምክር የሰማው አዳም ሐሰተኛ የወይን ግንድ ሆነ ። የጸጋ ልጅነትን ከእግዚአብሔር የተቀበለው አዳም ስቶ ሁላችንን ሐሳውያን አደረገን ። የባሕርይ ልጅ በሆነው በክርስቶስ እውነተኛነትን ጻድቃን መባልን አተረፍን ።

በዚህ ዓለም ላይ እስረኞች አመክሮ እንዲታሰብላቸው ጨዋ ይሆናሉ ። ፈላስፎች ራሳቸውን አምላክ አድርገዋልና መቅደሳቸው እንዳይሰደብ ሥነ ምግባርን ይለማመዳሉ ። ወታደር ቅጣትን በመፍራት ዲሲፕሊን ውስጥ ይገባል ። ራስን በማስለመድም ሥጋቸውን የገሩ ሕዝቦች አሉ ። የክርስቲያን ሥነ ምግባር ግን ከዚህ ሁሉ የተለየና ከእውነተኛው የወይን ግንድ ከክርስቶስ በሚመጣ ሕይወት የሚገኝ ፍሬ ነው ። ትልቁ ጥያቄ ቅርንጫፍ በግንዱ ላይ እንዳለ እኛስ በክርስቶስ ኢየሱስ ነን ወይ? የሚለው ነው ። የኤፌሶን ምእመናን በክርስቶስ ኢየሱስ ያሉ ፣ በሰማያዊ ስፍራ የተቀመጡ ነበሩ ።

አንተን አብን ሳትታይ የምትወደደውን ፣ አንተን ወልድን ታይተህ የማትጠገበውን ፣ አንተን መንፈስ ቅዱስን አብና ወልድን ለማየት ዓይን የሆንከንን ለማመስገን ስለበቃን ደስ ይለናል ። ለዘላለሙ አሜን ።

የኤፌሶን ትርጓሜ /4

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 26 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም