መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ባለ መታወክ አመሰግንሃለሁ

የትምህርቱ ርዕስ | ባለ መታወክ አመሰግንሃለሁ

ሸክም የከበዳቸውን ሸክም ተቀብለህ ፣ እርሱም ሳያንስህ እነርሱን በትከሻህ ላይ አሳፍረህ ፣ በምሕረት ጣቶችህ ፀጉራቸውን እየደባበስህ ኮረብታውን የምታወጣ እግዚአብሔር እንዴት ድንቅ ነህ ! የመድረስ ምኞት ይዞት መንገድ የቀረውን ፣ ልቡ እንደ ናፈቀ የራበውን ያላገኘውን ፣ ሰፊ ቀን ሲጠብቅ ጠባብ ዘመን የገጠመውን ፣ ይሆናል እያለ እንዳይሆን የሆነበትን ፣ ጽድቁን ትቶ በቅጡ መኰነንን የሻተውን ፣ ተወርሶ ድሀ ፣ ተከድቶ ብቸኛ የሆነውን ፣ የእርሱስ ቍስል አይድንም የተባለውን ፣ በጓዳ መክረህ ፣ በቤተ ውበትህ አስውበህ ፣ ሌላ ሰው አድርገህ የምታቆም አማኑኤል እንዴት ዕፁብ ነህ ! የገዛ እናቱ ረሳችውን ፣ የገዛ መምህሩ ያስካደውን ፣ የገዛ አባቱ የካደውን ፣ የገዛ ሰውነቱ የከዳውን ፣ የገዛ ገንዘቡ ጠላት ያመረተበትን ፣ የገዛ ደግነቱ ያስደፈረውን ፣ የገዛ ጥንቃቄው ከአደጋ የጣለውን ያንን ሰው መራራውን የምታጣፍጥለት ኤሎሄ እንዴት ግሩም ነህ !

ኤልሻዳይ ሆይ የጽድቅ ተማሪ አድርገኝ ። እንደ ተመላላሽ ተማሪ ሳይሆን እንደ አዳሪ ደቀ መዝሙር በቀንም በሌሊትም ከፊትህ አትለየኝ ። የመጀመሪያው ቀን ትውስታ አይጠፋምና በመጀመሪያ ቀን ሰውን በፍቅር መቀበልን አድለኝ ። ሰውን እስካውቀው ብዬ ከመኮፈስ በክርስቶስ አውቀዋለሁ ብዬ ትሑት መሆንን ስጠኝ ። ተገቢያቸው ስለሆነ ሳይሆን ስላንተ ፍቅር ለሰዎች ሁሉ የቸርነት ልብ ስጠኝ ። ጉዞው አቀበት ሁኖ ቢታክት ፣ እንቅፋቱ በዝቶ እግሮች ቢቆስሉ ፣ ዓይኖች ቀኑን ማየት አቅቷቸው ዕንባ ቢያረግዙ ፣ ልብ በኀዘን ቢሞላ ፣ የፈሩት ቢደርስ ፣ የጠሉት ለመውረስ ቢቃረብ ፣ እጆች ዘርን ለመዝራት ተስፋ ቢቆርጡ ፣ ጎረቤቶች ፍርሃት ፣ ዘመዶች ጥቅም ተኮር ቢሆኑ ፣ ጓደኞች ተንሸራተው የማያበቁ የተልባ ስፍር ቢሆኑ ፣ ሰማይ ቢከዳ ፣ ምድር ቢናወጥ ፣ የዘሩት ባይበቅል ፣ የሄዱበት በሩ ዝግ ቢሆን ፣ ጉባዔው ቢበተን ፣ ሰልፉ ጀግንነት ቢያጣ ፣ መሪ መንገድ ቢጠፋው ፣ ጋባዥ ለማኝ ቢሆን ፣ ጸሎተኛ ወሬ ቢተነትን ፣ ሰላም ባዩ ቢያኮርፍ ፣ ምስኪኑ ቀን ወጣልኝ ብሎ ቢገፋ ፣ ገበሬው በሞፈር ካልጻፍሁ ብሎ ቢደነፋ ፣ ምሁር ጭቃ ቢያላቁጥ ፣ ጠቢብ ቢደነቁር ፣ ፍረጃ ቢበዛ ፣ ሰውን ሰው ከማለት እገሌ ለማለት አፍ ቢፈታ ፣ ቅዱሳን ቢረክሱ ፣ ካህን እያጠፋ ሌቦች ቢያፍሩ ፣ ትንሽ ነው ያሉት ትልቅ ቢሆን ፣ ትልቁ ቢያንስ ፣ … አንተ ግን አንተ ነህ ። ባለ መታወክ አመሰግንሃለሁ ። አሜን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 27 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም