የትምህርቱ ርዕስ | ብቻ ንቁ

“ንቁ ፥ በሃይማኖት ቁሙ ፥  ጎልምሱ ጠንክሩ ። በእናንተ ዘንድ ሁሉ በፍቅር ይሁን ።” 1ቆሮ. 16 ፡ 13-14 ። 
የስንብት ቃላት ልብን ያባባሉ ። ሰዎች በሰላምታ ተገናኝተው ፣ በስንብት ሲለያዩ ሆዳቸው ባር ባር ይለዋል ። አልጸና እያለ ይናወጥባቸዋል ። ስብሰባው በመግቢያ ንግግር ተጀምሮ ፣ በስንብት ሲጠቃለል በየተራ የገባው በጅምላ ይወጣል ። በመቅድም የተጀመረው መጽሐፍ በማጠቃለያ ሲሰናበት እፎይታ ይሰጣል ። በሃሌ ሉያ የተጀመረው ቅዳሴ “እትዉ በሰላም” ተብሎ ሲጠናቀቅ በረከትን ይዞ ሁሉም ወደ ቤቱና ወደ ሥራው ይፋጠናል ። በልቅሶ የተጀመረው ኀዘን ግብአተ መሬት ሲፈጸም “ከዚህ በኋላ ልቅሶ የለም” ተብሎ በመጽናናት ይጠናቀቃል ። መነሻ ያለው ሁሉ መድረሻ አለው ። የተጀመረ ነገር አንድ ዘመን ይፈጸማል ። ፍጥረት ሁሉ ወደ ፍጻሜ እየተጓዘ ነው ። በልደት የጀመረው የምድር ጉዞም በሞት ሊጠቃለል በእያንዳንዱ ቀን ወደምንጠላው ሞት እየሄድን ነው ። “ብንጠላው የምንጓዘው ወደ ሞት ነው” እንደ ተባለው ነው ። ስንብት ያባባል ፣ የተሰበሰበውን ይበትናል ። ጭብጥ አሳብ ይሰጣል ። በረከትን ያመጣል ። መጽናናት ይስገኛል ። ፍጻሜ ይሰጣል ። የሰውን መጨረሻ ያሳያል ። 
ኑዛዜ የስንብት ድምፅ ነው ። ሰውዬው ሊሞት ሲል ለቤተሰቡ ይናዘዛል ። ከሞተ በኋላም ኑዛዜው ይጸናል ። ዓለምና ፍላጎቷ ከኋላዬ ነው ብሎ በንስሐ የሚናዘዘው ተነሣሒም ኑዛዜው እንዲጸና ለተናዘዘበት ኃጢአት መሞት ያስፈልገዋል ። የመጨረሻ ቃላት የማይረሱና የአደራ ቃላት ናቸው ። ታላላቅ የሚባሉ ሰዎች በመጨረሻው ሰዓት የተናገሩት ሲወሳ ይኖራል ። የስንብት ቃል ብዙ ጊዜ እውነት ነው ። ሰው የሚዋሸው እኖራለሁ ብሎ ሲያስብ ነውና ። “ደህና እደር ልጄ” እና “ደህና ሁን ልጄ” ብለው የሞቱ ሰዎች ንግግራቸው ይመነዘራል ። “አባዬ ደህና እደር ያለኝ በሰማይ ስለምንገናኝ ነው ።” “እኔን ደግሞ ደህና ሁን ያለው በእግዚአብሔር አላምንም በፈቃዱ አልኖርምና አንገናኝም ማለቱ ነው” በማለት አንዱ ደስታን ሌላው ጸጸት ያተርፋል ። የመጨረሻ ቃላት አይረሱም ። 
ጌታችን በመስቀል ላይ የተናገራቸው ሰባቱ የመስቀል ጩኸቶች ሲታወሱ ይኖራሉ ። እነዚህን ቃላት የተናገረው በዕለተ ዓርብ ከስድስት እስከ ዘጠኝ ሰዓት ባለው ጊዜ ውስጥ ነው ። የተናገረውም ባማረ መድረክ ፣ በተዋበ አትሮኖንስ ፣ በከበረ ልብስ ፣ በድምፅ ማጉያ ፣ ውኃ እየተቀዳለት ፣ እየተጨበጨበለት ፣ … አይደለም ። በጨለማው ሰዓት ፣ በመስቀል ተንጠልጥሎ ፣ እጆቹና እግሮቹ በምስማር ተቸንክረው ፣ በደም ማዕበል ተጥለቅልቆ ፣ ዕርቃኑን ሁኖ ፣ በታላቅ የጣር ድምፅ ፣ ተጠማሁ እያለ ውኃ ተከልክሎ ፣ ጠላቶቹ እየዛቱበትና ጥርሳቸውን እየነከሱበት ነው ። እነዚህ የሕይወት ቃላት ሀብተ መስቀል ሁነው ይኖራሉ ፣ አይረሱም ። በውስጣቸውም ይቅርታ ፣ ስጦታ ፣ ፍቅር ፣ የኃጢአት ዋጋ ፣ አምላክ ከሰው የሚፈልገው ፣ የድኅነት ጉዞ መጠናቀቅ ፣ ተስፋ አለ ። 
ሐዋርያው ጳውሎስ አንደኛ ቆሮንቶስን ሲጽፍ የመሰናበቻ ንግግሩ፡- “ንቁ ፥ በሃይማኖት ቁሙ ፥  ጎልምሱ ጠንክሩ ። በእናንተ ዘንድ ሁሉ በፍቅር ይሁን” የሚል ነው ። 1ቆሮ. 16 ፡ 13-14 ። 
“ንቁ” ይላል ። ተራቁተው የተኙትን ብቻ ሳይሆን ለብሰው ያሸለቡትንም ፣ በአልጋ የተኙትን ብቻ ሳይሆን በወንበር ያንጎላጁትንም ንቁ ይላል ። ዓይናቸውን የጨፈኑትን ብቻ ሳይሆን ገልጠው የተኙትንም ንቁ ይላል ። የማያዩትን ብቻ ሳይሆን እያዩ የማያዩትን ፣ አዚም ውስጥ የገቡትንም ንቁ ይላል ። የሞት ታናሽ ወንድም የሆነው እንቅልፍ የወሰዳቸውን ብቻ ሳይሆን ሳይነቁ የሚጓዙትንም ንቁ ይላል ። ጠቢቡ ሰሎሞን ሲተኛ ዓይኑን ገልጦ ፣ ሲነቃ ዓይኑን ጨፍኖ ነው ይባላል ። ስለዚህ ነቃ ብለው ሲሸሹት ፣ ተኛ ብለው ሲጠጉት ይኖር ነበር ። መተኛቱና መንቃቱ ያልለየ በጣም አስቸጋሪ ነው ። እኛም የሰሎሞን ዘር እንዳለብን አለብንና መተኛታችንም መንቃታችንም የማይታወቅ ወገን እየሆንን ነው ። ተኝተዋል ሲባል ዘራፍ የአክሱም ፣ የላሊበላ ሠሪዎች ነን እንላለን ። ነቅተዋል ሲባል ሰው ዘልዝለን እንሰቅላለን ። ሐዋርያው፡- “ንቁ” ይላል ። መንቃት ለራስ እንጂ እነ እገሌ ነቅተዋል እንዲባል አይደለም ። ጌታ ገብቶናል ፣ ኢየሱስን አውቀናል የሚሉ ሰዎች እኛ በርቶልናል ፣ እነ እገሌ አልበራላቸውም ይላሉ ። መንቃት በንግግር አይደለም ፣ የተኛም እየቃዠ ያወራልና ። በእንቅልፍ ልብ ተነሥቶ የሚሰብክም አይታጣም ። ንቃት መናገር መቻል ሳይሆን በትክክል መከወን ነው ። መከወንም ብቻ ሳይሆን ነቅቶ ማድረግም ነው ። ከእንቅልፋቸው ሳይነቁ ከአራት ኪሎ ሰአሊተ ምሕረት የሚጓዙ ፣ በር ከፍተው በጠፍ ጨረቃ የሚወጡ አሉ ። ሲነቁ ራሳቸውን ርቀው ያገኙታል ። መሄድም መንቃት አይደለም ። ንቃት ወዴት እንደሚሄዱ ማወቅ ነው ። በእንቅልፍ ልባቸው የቤቱን ልብስ አውጥተው የሚያጥቡ አሉ ፣ ሥራቸው ግን የሚያስመሰግን ሳይሆን የሚያሳዝን ነው ። አልነቁምና ።
አጠገብ የተኛ ሰው ካለ እንቅልፍ ያመጣል ። እንቅልፍ ይጋባልና ሾፌር አጠገብ የሚቀመጥ ንቁ መሆን አለበት ። መንቃት ብቻ ሳይሆን እያጫወተና እያየለትም መሄድ አለበት ። አጠገብ የተኙ ሰዎች ካሉ መቀስቀስ ያስፈልጋል ፣ ቀጥሎ እኛም እንተኛለንና ። መሪ ይዞ መተኛት ተሳፋሪውንም ራስንም ይዞ ገደል መግባት ነው ። መዝሙረኛው፡- “ለሞትም እንዳልተኛ ዓይኖቼን አብራ” ያለው ለዚህ ነው ። መዝ. 12 ፡ 3 ። ቤት በእሳት እየነደደ ያለው እንቅልፍ ፣ ሌባ ቤት ውስጥ እየገባ ያለው አዚም አይጣል ነው ። ለዚህ ነው ዘማሪው ለሞት መንቃት እንጂ መተኛትን ተጸይፎ ዓይኖቼን አብራ ያለው ። አንዳንድ ሰዎች ተኝተሃል ሲባሉ እየሰማሁ ነው ይላሉ ። በንቃትና በእንቅልፍ መካከል ያሉ ሰዎችም ንቁ ተብለዋል ። ወታደር ሸሸ አይባልም አፈገፈገ ነው ። ተኛሁ ለማለት ያፈሩ እየሰማሁ ነው ይላሉ ። መንቂያው ሰዓት ሲደርስ በጣም የሚተኙ ሰዎች አሉ ። መነሻው ዘመን ላይ ትኩስ እንቅልፍ የያዛቸው የሕይወት ባቡር ጥሏቸው ይሄዳል ። 
ምድራችን ባልተማሩና ተምረው በደነቆሩ ተኚዎች ተጨንቃለች ። የተማሩት ጦርነት ሲፈጥሩ ፣ ያልተማሩት ይጨርሳሉ ። መንቃት ያስፈልጋል ። ሁልጊዜ ገዳይ መሆን የለም ፣ ገዳይም ሟች ይሆናልና መንቃት ይገባል ። ዘረኝነት እየወረረን ፣ የትላንቱን በአብሮነት እያስረሳን ነውና መንቃት ያስፈልጋል ። በብሶት ንግግር ያልደላንን እኛን የሚቆሰቁሱንን ነቅተን መሸሽ ይገባል ። ምስጋና እንጂ ብሶት እግዚአብሔርን አያሳይም ። የፈረድነው ነገር ሁሉ በቤታችን ገብቷል ፣ በአገራችን ሞልቷል ። በሃይማኖት ፣ በበሽታ ፣ በኃጢአት ፈረድን ፤ ሁሉንም ተከናንበን ቁጭ አልን ። ዛሬም የምንፈርድባቸው ነገሮች ነገ ዙፋን ይዘው እንዳይገዙን ፍርድን ትተን ትምህርትን ማስፋፋት ይገባናል ። ልጆቻችንን ችላ ብለን ብር የምናሯሩጥ ብር ሲገባ ልጆቹ ይወጣሉና ፣ ሕንፃው ሲደመደም ትዳሩ ይፈርሳልና መንቃት ያስፈልጋል ። የጋራ ሞትን እንደ ሕይወት የቆጠሩ መንፈሳዊ ስብስቦች መንቃት ያስፈልጋቸዋል ። ዛሬ ብሉኝ ብሉኝ የሚለው ቃለ እግዚአብሔር ነገ ላይገኝ ይችላልና ነቅተን መሰብሰብ ይገባናል ። “አጥብቀው ያሰሩትን ዘቅዝቀው ይሸከሙታል” እያሉ የሚወዱአቸውን የሚያጣጥሉ ፣ የሚያፈቅሯቸውን ሰዎች ችላ የሚሉ “የዋህ ካመረረ ፣ በግ ከበረረ” አይመለስምና መንቃት ይገባቸዋል ። ሰው ከፋ እያሉ የሚያወሩ ደጎቹን ግን አክብረው ያልያዙ የሰው ድሀ መሆን ይመጣልና መንቃት ይገባቸዋል ። 
“አገሬ ኢትዮጵያ ጠንክረሽ ተማሪ ፣ ሁልጊዜ አይገኙም ዕድልና መሪ” ይባላል ። ሁለቱ ገጥመው ከተገኙ ትልቅ ስጦታ ነው ። ሴትዬዋ፡- “አልጋው ሲገኝ ባሉ አይገኝ” እንዳለችው አንዱ ሲገባ አንዱ ይወጣልና ዕድልና መሪ በቤት ፣ በቤተ ክርስቲያን ፣ በአገር ሲገኝ መንቃትና መጠንከር ይገባል ። 
ብቻ ንቁ ።
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 25 ቀን 2012 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም