የትምህርቱ ርዕስ | ብናውቅ

“ኢየሱስ መልሶ፦ የእግዚአብሔርን ስጦታና፡- ውኃ አጠጪኝ የሚልሽ ማን መሆኑንስ ብታውቂ ፥ አንቺ ትለምኚው ነበርሽ የሕይወትም ውኃ ይሰጥሽ ነበር አላት ።” ዮሐ. 4፡10 ።
አንድ ቀልድ ቢጤ ሲነገር እንሰማለን ። ለእግዚአብሔር ስለሚሰጡ ሦስት ዓይነት ሰዎች የሚገልጥ ነው ። አንደኛው ሰውዬ ክብ ሠራና፡- “ገንዘቤን ወደ ላይ እወረውራለሁ ፣ ክቡ ውስጥ የወደቀው የእኔ ከክበቡ ውጭ የወደቀው የእግዚአብሔር ነው” አለ ። ሁለተኛው ደግሞ መስመር አሰመረና፡- “እኔ ገንዘቤን ወደ ላይ እለቃለሁ ፣ ከመስመሩ ወዲህ የወደቀው የእኔ ፣ ወዲያ የወደቀው የእግዚአብሔር ነው” አለ ። ሦስተኛው ደግሞ “ገንዘቤን ወደ ላይ እበትናለሁ ፣ የወረደው የእኔ ፣ አየር ላይ የቀረው የእግዚአብሔር ነው” አለ ይባላል ።
እግዚአብሔርን ከሕይወታቸው ውጭ አድርገውት ነገር ግን ትንሽ ገንዘብ መጣል የሚፈልጉ ፣ በኑሮአቸው ክበብ ውስጥ ሊጋብዙት የማይሹ ብዙ ሰዎች አሉ ። እግዚአብሔር በመንበሩ ይኑር ፣ እኔም በምድር እኖራለሁ ፣ እኔን የሚያስደስተኝ ነገር እርሱን አያስከፋውም ፣ በአእምሮዬ እጠቀማለሁ እንጂ ጸሎትና ቤተ ክርስቲያን መሄድ አያስፈልገኝም ብለው የሚስቡ ሰዎች እየበዙ ነው ። እነዚህ ሰዎች እግዚአብሔር የለም ለማለት አይደፍሩም ፣ ማኅበረሰቡን ይፈራሉ ። ለቤተ ክርስቲያን ድጋፍ ለማድረግም በጣም ስስታም አይደሉም ። ነገር ግን እግዚአብሔርን ከሕይወታቸው ክበብ ውጭ አድርገው የሚኖሩ ናቸው ። እነዚህ ሰዎች ዝግ በመሆናቸው የሰውን ይሰማሉ እንጂ የራሳቸውን መናገር አይፈልጉም ። ድብቅነታቸውና ውሳኔ የሌለው ሕይወታቸው ውስጥ ውስጡን ቢከነክናቸውም ወደ ፍቅር ዓለም መጠቃለል አይፈልጉም ። ለማንም ሰው ጥርሳቸውን ይጋብዛሉ ፣ ልባቸውን መጋበዝ ግን ይቸገራሉ ። የጸዳ ኑሮ የላቸውም ። እያላቸውም አኗኗርን አያውቁበትም ። ራሳቸውን መደበቃቸው ትልቁ ኩራታቸው ነው ። እነዚህ ሰዎች የወደቁ ቀን ትንሣኤ የላቸውም ። የማይደሰቱበት ቤትና ትዳር አላቸው ። ገንዘባቸውንም ስለማይጠቀሙበት ተቆልሎ ሲያዩት ደስ ይላቸዋል ። በጥሩ ቃል ቢሸኙም የሰውን ጉዳይ ጉዳዬ ነው ብለው ማሰብ አይፈልጉም ።
መስጠት መርሕ በሆነባት ሕይወት ውስጥ ሁለተኛዎቹ ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር እኩል ለእኩል እየተካፈሉ የሚኖሩ ናቸው ። ሙሉ ሕይወታቸውን ለእግዚአብሔር አይሰጡም ። መጸለይም መጨነቅም ገንዘባቸው ነው ። ዓለማዊነትም መንፈሳዊነትም ያምራቸዋል ። ወንበራቸውን አስጠብቀው ወደ ቤተ ክርስቲያን ይመጣሉ ። በማንኛውም ሰዓት ደግሞ የሱስና የኃጢአት ወንበራቸው ላይ ይቀመጣሉ ። እነዚህ ሰዎች ራሳቸውን በመውቀስ ወደር የላቸውም ። ጸጸታቸው ግን ዕድሜ ስለሌለው መልሰው ባስለቀሳቸው ነገር ይያዛሉ ። ሲሰበኩ በቀላሉ ይነካሉ ። ሲገሠጹ ያለቅሳሉ ። መልሰው ግን የተፉትን ይልሳሉ ። ጭቃ ላይ ተቀምጠው ስለሚታጠቡ መልሰው ይቆሽሻሉ ። ሁልጊዜ ጀማሪ ናቸው ። ብዙ መሠረት አላቸው ፣ አንድ ጉልላት ግን የላቸውም ። የተሰማቸውን እንጂ እውነት የሆነውን ነገር የሚያደርጉ አይደሉም ። ከወገብ በላይ ታቦት ፣ ከወገብ በታች ጣዖት እንደሚባለው ናቸው ። አብረዋቸው ለሚኖሩ ሰዎች የሚያዳክሙ ናቸው ።
ሦስተኛዎቹ ሰዎች ሕይወታቸው ላይ የሚያፌዙ ናቸው ። እግዚአብሔር እንዳልበድል ከፈለገ ለምን በደልን ፈጠረ ይላሉ ። በሱስ ወንበር ላይ ተቀምጠው ስለ አዳም ትክክለኛነት ይሟገታሉ ። መጠጥ አትጠጡ ሲባሉ መጽሐፍ “ወይን ያስተፌስሕ” ይላል በማለት የማይገናኝ ጥቅስ ይጠቅሳሉ ። ሕይወት ከእግዚአብሔር የተቀበሉአትና በኋላም የሚያስረክቧት አደራ መሆኗን ይዘነጋሉ ። ስለ እውነት መስማት በፍጹም አይፈልጉም ። በከንቱ ጨዋታ እውነትን ይደልላሉ ። ሁሉ ዓለም እንደ ተሞኘና እነርሱ ብቻ እየኖሩ እንደሆነ ይሰማቸዋል ። ወጣትነት የመበደል መብት እንደሆነ ይናገራሉ ፣ ለንስሐ እርጅና ዘመን ላይ እንደሚደርስ ያስባሉ ። እርሱም ቢሆን ሐሰታቸውን እንጂ እውነታቸውን አይደለም ። ብዙ ሰው ስለሚስቅላቸው ልክ የሆኑ ይመስላቸዋል ። እነዚህ ሰዎች በድንገት በታላቅ ጭንቀት ውስጥ ይወድቃሉ ። አእምሮአቸው ይጣላቸዋል ፣ ራሳቸው የሚያመልጣቸው መስሎ ይሰማቸዋል ። እነዚህ ሰዎች ብዙ ጊዜ ሲሰበሩና በታላቅ ፈተና ውስጥ ሲገቡ እግዚአብሔርን ይፈልጋሉ ።
ሕይወት ከእግዚአብሔር የመቀበልና ለእግዚአብሔር የመስጠት ሂደት ናት ። ሕይወት ከሰዎች የመቀበልና ለሰዎች የመስጠት ባሕል ናት ። ለመስጠት ከሰሰትን አንቀበልም ። ፍቅርን ፣ ቸርነትን ፣ እውቀትን … መስጠት ካቆምን አይጨመርልንም ። ካልተጨመረልን የያዝነውን እንጨርሳለን ።  በመጨረሻም ባዶ እጃችንን እንቀራለን ። የዚህ ሁሉ ችግር አለማወቃችን ነው ። እግዚአብሔር ማን መሆኑን አላወቅንም ። በመለመኑ ውስጥ መስጠት ፣ በመጠየቁ ውስጥ መልስ ያለው መሆኑን አልተገነዘብንም ። እግዚአብሔር ሕይወታችንን የሚጠይቀን አበጃጅቶ መልሶ ሊሰጠን ነው ። ትንሹን ገንዘብ የሚጠይቀንም ትልቁን ጸጋ ሊሰፍርልን ነው ።
ሳምራዊቷ ሴት ጌታችን ውኃ ሲጠይቃት እርሷ ብዙ ጥያቄ አነሣች ። ውኃ የሚጠይቃት የውኃው ፈጣሪ መሆኑን አልተገነዘበችም ። የሕይወት ባለቤት የሆነው ጌታ ሕይወታችንን ሲጠይቀን ፣ የጊዜ ባለቤት ጊዜአችንን ሲለምነን ፣ የገንዘባችን ምንጩ አሥራት በኩራታችንን አምጡ ሲለን አልገባንምና እሺ አላልነውም ። እርሱ እኛነታችንን ሲጠይቀን እኛ ስለ ሕዝቡ መጎሳቆል እናወራለን ፣ እርሱ ገንዘባችንን ሲጠይቀን እኛ ታማኝ አገልጋይ የለም እንላለን ። በቀጥታ እየመለስን ሳይሆን አፍራሽ ጥያቄዎችን እያቀረብን ነው ። ጊዜያዊ መከታ ካገኘን እንጽናናለን እንጂ እኔን የሚመለከተኝ የቱ ነው አንልም ። የሚለምነን ሰው ስናይ አለው አይደለም ወይ ? እንላለን ። ራበኝ የሚለንን ዘሩ ምንድነው ? በማለት እንጠይቃለን ። ሃይማኖት እየለየንም ደግ ነገር እናደርጋለን ። ቀጥተኛ ሕይወትና መልስ የለንም ። ደህና ነህ ወይ? ስንባል እገሌ ደህና ነው ፣ ምን ይሆናል ብለህ ነው እንላለን ። ንስሐ ግቡ ስንባል ፈረንጆቹ ይህን ሁሉ እየሠሩ በጥሩ ይኖራሉ እንላለን ።
ብታውቂ በማለት ጌታ ተናገረ ። የዘላለም ውኃ የሚሰጠውን ባለማወቅ አጉላላችው ። የፈጠረው ሳይከለክላት የተቀበለችው ከለከለችው ። የቤተ ልሔም ሰዎች በበረት የተወለደውን ጌታ አላወቁም ። ቢያውቁ ኑሮ እነርሱ በበረት አድረው ጌታን በቤታቸው ያስተናግዱት ነበር ። ቢያውቁ ኑሮ በእንግዶች ማረፊያ ያረፈውን ሰው በሙሉ አስወጥተው እርሱን ያስገቡት ነበር ። አውቀውስ ቢሆኑ የክብርን ጌታ ባልሰቀሉትም ነበር” ተባለ ። 1ቆሮ. 2፡8 ። አለማወቅ ሰቃልያነ እግዚእ ያደርጋል ። አለማወቅ ለሰጪው እንዲከለክሉ ያደርጋል ፣ አለማወቅ ንጉሡን ደጅ ያስጠናል ፣ አለማወቅ የሰማይ የምድሩን ጌታ በበረት ጥሎ ሰውን በቤት ያስተኛል ።
ዛሬም አለማወቅ እየበዛ ነው ። ሰው ስለመሰብሰብ እንጂ ስለመስጠት አያስብም ። የሰበሰበውን እንደሚበላው ግን እርግጠኛ አይደለም ። ስግብግብነት እየበዛ መጨካከን እየነገሠ ነው ። ሁሉን ለእኔ የሚባል የልጅነት ጠባይ በዕድሜ የገፋነውንም እየተሟገተን ነው ። ብዙ ሰው የራሱን ደሴት ሠርቶ መኖር የሚፈልግ ነው ። በዙሪያው ሰው ሳይሆን ውኃ ብቻ እንዲኖር የሚፈቅድ አያሌ ነው ። ዝግ ልቦች የፈጠሩአቸው ብዙ ዝግ ቤቶች አሉ ። የመጠባበቅ ሕይወት እየነገሠ ነው ። ካልደወለ አልደውልም የሚል ድምፅ በየቀኑ ይሰማል ። የብድር እንጂ የነጻ ፍቅር እየተሸኘ ነው ።
የራሱ ጉዳይ የሚሉ ድምፆች ትዳርንና ወዳጅነትን ጠቅጥቀን እንድንሄድ እያደረጉን ነው ። ራስን ብቻ ማዳመጥ ለማንም ሰው ስሜት እንዳንጠነቀቅ እያደረገን  ነው ። በአጭር ቃል አብደናል ። የማያደርስ መንገድ ላይ ጉዞ ጀምረናል ። ይሮጣል ይሮጣል ፣ ብዙ ሰው ግን ግቡን አያውቀውም ። እናውቃለን እንላለን ፣ የቅጥፈት እንጂ የእውነት እውቀት እየተለየን ነው ። ዝምድናን አብሮ መኖርን ስናፈርስ ትንሽ እንኳ ቅር አይለንም ። ቤት ለመሥራት አገር ማፍረስ አለማወቅ ነው ። ልጅን ለማሳደግ የትምህርት ቤት መሥሪያን መስረቅ በእውነት አለማወቅ ነው ። የእርዳታ እህል መዝረፍ በእውነት ትልቅ የአእምሮ ድህነት ነው ። ከሬሳ መዝረፍ ከሰውነት ተራ መውጣት ነው ። የደከመውን ይህን ሕዝብ መግረፍ በእውነት ጀግና የማያሰኝ ነው ።
“ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል” ይላል ። ሆሴ. 4፡6 ። ትንቢት በማጣቱ ጠፋ አይልም ፣ እውነትም ይሁን ሐሰት እተነብያለሁ የሚል ብዙ አለ ። ፈዋሽ በማጣቱ ጠፋ አይልም ፣ ሐኪም ቤት እናዘጋለን የሚሉ ፈዋሾች በዝተዋል ። የጠፋነው እውቀት በማጣት ነው ። እግዚአብሔር በእውቀት ይባርከን ።
የለህም ያሉህን ባለመኖር የሸኘህ ፣ የተገዳደሩህን በጣትህ የረታህ የማመልክህ ብሩህ ጌታ አመሰግንሃለሁ ። የመረጥክልኝን ትቼ የመረጥኩትን ሳሳድድ ፣ ደርሼም ገና እፈልጋለሁ ። ያልከው በሕይወቴ ይሁን ። ሁለንተናዬን ሰጥቼ ላከብርህ እሻለሁ ። እጆቼን በእጆችህ ያዛቸው ። አገሬ እስክገባ አጥብቀህ ያዘኝ ። የእኔ ባልሆነው ዓለም እንዳልደናገር ምራኝ ። ጣዕም ባለው ስምህ ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 21
ግንቦት 21 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም