የትምህርቱ ርዕስ | ትልቁ ፈተና

     አንድ መነኩሴ አባ አጋቶንን እንዲህ ሲል ጠየቀው፡- “ትእዛዝ ታዝዤ ነበር ነገር ግን በቦታው ላይ ፈተና አለ ። በትእዛዙ መረት ለመሄድ ፈቃደኛ ነኝ ነገር ግን ፈተናውን እፈራለሁ ።” ሽማግሌውም እንዲህ አለው፡- “አጋቶን ቢሆን ኖሮ የታዘዘውን ፈጽሞ ፈተናውንም ድል ያደርግ ነበር ።” (አጋቶን 13)
     የክርስትና ታሪክ ፈተናን ፈርተው ባልጀመሩ ዓለማውያን ፣ በፈተና ደንብረው በተመለሱ ዴማስያውያን ፣ ፈተናውን ድል ነሥተው በከበሩ ቅዱሳን የተሞላ ነው ከሦስቱ ሁለቱ እጅ ለክብር የሚበቃ አይደለም መንገዱ ጠባብ ነውና ከሦስቱ አንዱ እጅ ይተርፋል ብዙ ሰዎች ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን ለመፈጸም ፈቃደኛ አይደሉም ንስሐ ለመግባት ፣ ቅዱስ ቊርባን ለመቀበል ይቸገራሉ ለችግራቸው መፍትሔ ለማግኘት ግን ፈዋሽ ተነሣ በተባለበት አገርና ከተማ ሁሉ ይባክናሉ አንዳንድ ችግሮች በንስሐና በቅዱስ ቊርባን የሚፈቱ ናቸው እነዚህ ሰዎች ሌሎቹን ጸጋዎች የሚያከብሩትን ያህል ንስሐን ግን ማክበር አይሆንላቸውም እግዚአብሔርን ለሥጋ ችግር እንጂ ለነፍስ መፍትሔ አይሹትም ነፍስ ስትፈወስ ሁሉም ነገር እንደሚፈወስ መቀበል አይሆንላቸውም ንስሐ እንዲገቡ ሲነገራቸው ፈተናውን እፈራለሁ ይላሉ የቆሸሸ ሰው ታጠብ ሲባል እንደገና መቆሸሹን እፈራለሁ አይልም እነዚህ ሰዎች ግን ትልቁ ሰይጣናዊ ፈተና ለንስሐ ጠንካራ ልብ መያዝ እንደሆነ አይረዱም ቃየንን ተቅበዝባዥ ፣ ዔሳውን የቁጭት ሰው ያደረገ ፤ ፈርዖንን በኤርትራ ባሕር ያሰጠመ ፣ ይሁዳን ለገመድ የዳረገ ንስሐ አለመግባት መሆኑን ገና አላወቁም እነዚህ ሰዎች የበደላቸው ሰው ይቅርታ ሳይጠይቃቸው ገንዘብ ስጠን ቢላቸው ይደነቃሉ መጀመሪያ ይቅርታ በለኝ ይላሉ እነርሱ ግን ይቅርታን ሳያገኙ ከእግዚአብሔር ዘንድ ጸጋን ይለምናሉ ባልታጠበ ገላ ሽቱ መቀባት ቆሻሻውን ማጉላት ነው ንስሐ ባልገባ ማንነትም የሚገኝ ፈውስና በረከት የበለጠ ለመጥፋት ነው
ዓለማዊነት የተጫናቸውና በከንቱ ጨዋታ እንደ ሕፃን የሚታለሉ ሰዎች የቤተ ክርስቲያንን አጥር የሚዞሩ እንጂ ወደ ውስጠኛው አገልግሎት የሚገቡ አይደሉም ከእግዚአብሔር ጋር ለመወዳጀት ሳይሆን የከፋ ጠብ ላለመጣላት ብቻ የሚያስቡ ናቸው እገዚአብሔርን እወዳለሁ አይሉም ፣ እግዚአብሔርን አልጠላም ግን ሊሉ ይችላሉ ፍቅር ማለት አለመጥላት አይደለም የብዙ ሰው ንግግር ተሳልሜ ልመለስ እንጂ ንስሐ ገብቼ ፣ ቆርቤ ልመለስ የሚል አይደለም ዛሬ ንስሐ የሚገባ ሰው ቢበረክት አገር ሰላም ይሆን ነበር ምክንያቱም ንስሐ ሲገባ የበደለውን ወንድሙን ክሶ ፣ የቀማውን ንብረት መልሶ ነውና ዓለማዊነት ዕለት ዕለት እየበዛ ነውና ይህ የሚያሳየን ሰው ምን ያህል ተስፋ መቊረጡን ነው ጠንከር ያለ ሕይወት አይደለም ፣ ጠንከር ያለ ቃል መስማት የማይፈልጉ ፣ ገብስ ገብሱን ብቻ እየመረጡ የቀለለ ኑሮ የሚገፉ አያሌ ናቸው ሰው ንስሐ ካልገባ ፣ ወደ ክርስቶስ ሥጋና ደም ካልቀረበ ሃይማኖቱን በገዛ ኑሮው እየተቃወመ ነውና ሃይማኖቴ ማለት አይችልም እርሱ ያላመነበትን እንዴት ይከራከርለታል ?
ብዙ ክርስቲያኖች ወደ እግዚአብሔር መጥተው ወደ ኋላ ተመልሰዋል የደነበሩበትን ነገር ሲናገሩ ቄሱ እንዲህ ሲያደርግ ፣ አገልጋዩ እንዲህ ሲፈጽም አይቼ ይላሉ በእግዚአብሔር ቤት ከአገልጋዮች ጋር ያለን ግንኙነት ከጸጋቸው እንጂ ከግላዊ ኑሮአቸው ጋር ሊሆን አይገባም መጽሐፍም ሰውን ተመልከቱ አላለም “ስለዚህ ፥ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋዮች የሆናችሁ ቅዱሳን ወንድሞች ሆይ ፥ የሃይማኖታችንን ሐዋርያና ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስን ተመልከቱ” ዕብ. 3፡1 ሌሎችም ልዩ ልዩ ፈተናና መከራ ሲመጣ ፈርጥጠው ይወጣሉ ክርስትናን ለመደሰቻ ብቻ መምረጥ ተገቢ አይደለም መስቀሉን ያላየ ትንሣኤውን አያይም ሌሊትን ያልታገሠ ለማለዳ አይደርስም ክረምትን ያልቻለ በጋውን አይመለከትም ዴማስ አገልግሎቱን ሸኝቶ የተመለሰ ፣ በመጀመር ጎበዝ በመፈጸም ሰነፍ የሆነ ሰው ነው ያላለቁ መንገዶች የታላላቅ ትካዜ መገኛዎች ናቸው ብዙዎች የኃጢአት ወንበራቸው ላይ ሁነው በረጅሙ ተንፍሰው ሲናገሩ ይሰማሉ፡- “ክርስቲያን ነበርሁ” ፣ “አገልጋይ ነበርሁ” ይላሉ ነበርሁ የሚያምረው ለኃጢአት እንጂ ለጽድቅ አይደለም
ብዙ የጸኑ ፣ ወንጌልን ዓላማ ፣ ክርስቶስን መሪ ያደረጉ ቆራጥ አርበኞች በክርስትና ውስጥ አሉ የሚልሞሰሞሱትን ዓለም ስትንቅ እነዚህን ግን መድፈር አልሆነላትም የሚያምርባቸውን በትክክል የለዩና ያንንም ሁነው የተገለጹ አያሌ ወታደሮችን ወንጌል አብቅላለች እነዚህን ስናይ እንበረታለን በጭብጨባ ያልቀሩ ፣ በስድብም ያልተደናቀፉ ፣ በወረትም ያልተነኑ ፣ በስህተት ትምህርትም ያልተጠለፉ ፣ እረኞቻቸውን በማነቅም ያልተባበሩ አያሌ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያን ወጥተዋል የቤተ ክርስቲያን ውለታ የከበዳቸው ፣ ዞረው የበሉበት ሰሐን ላይ ያልተፉ ፣ ያጠመቁአቸውን ያልከሰሱ አያሌ ቡሩካን ዛሬም አሉ ክፉዎቹ ስለሚጎሉብን እንጂ ደጋጎቹ ጨርሰው አልጠፉም
ፈተናን የምናሸንፈው ባለመታዘዝ ሳይሆን በመታዘዝ ነው የእግዚአብሔርን ሥራ ለመሥራት ፈተናን ከፈራን ሰይጣንን አከበርነው ማለት ነው ፤ ከታዘዝን እግዚአብሔርን አከበርነው ሰይጣን ድል የሚነሣው በቃል ግሣጼ ሳይሆን በመታዘዝ ነው “እንግዲህ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል” ይላል ያዕ. 4፡7 ልብ በሉ ሰይጣን ከእኛ የሚሸሸው “ይውደም” እያልን ስለፎከርን ሳይሆን ለእግዚአብሔር በመገዛት ነው የዛሬው ትውልድ ቅዱሳን መላእክትን ማክበር እያቃተው ሰይጣንን ግን የሚያከብር ነው እንዴት የጸኑትን ትተን የወደቁትን እናከብራለን ?
የታዘዝነው ቦታ ጋ ስንደርስ የፈራነው ፈተና የለም ፈተናንም የምናሸንፈው በመሥራት ነው ተማሪ ፈተናን የሚያልፈው በማጥናት ነው የታዘዝነውን ስናደርግ የምንፈራውን ፈተና እናጣዋለን መፈተን ሰው መሆን ፣ አለመታዘዝ ግን ሰይጣን መሆን ነው
ጸሎት
ስምህ ቅዱስ የሆነ ፣ ግርማዊነትህ ያልተደፈረ ፣ ዳርቻዎችን ሁሉ በዓይን ጥቅሻ የምትቆጣጠር ፣ ክንድህ የሚያደቅ የይሁዳ አንበሳ በእውነት አመሰግንሃለሁ የመጀመር ፍርሃት ፣ የመጨረስ ጽናት እያጣሁ እናጣለሁ ያየህልኝን ለማየት ፣ ወደፈቀድከው ለመጓዝ ዓይኔን አብራው ትልቁ ፈተና አለመታዘዝ መሆኑን አሳውቀኝ ሁልጊዜ በማላፍርበት ደግነትህ ለዘላለሙ አሜን
የበረሃ ጥላ 7
ረቡዕ መስከረም 7 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም