መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ትልቅ ተአምር

የትምህርቱ ርዕስ | ትልቅ ተአምር

 አንድ ሰው መጥቶ ለአንድ ቅዱስ አባት ጥያቄ አቀረበለት፡- “ተአምር መሥራት እፈልጋለሁ ፣ እንዴት ላድርግ ?” 

ቅዱሱ አባት መለሰለት:-

 

“አንድን ሰው ወንጌል እንዲያነብ ካስተማርከው ዓይን አበራህ ማለት ነው ፣ 

ድሆችን እንዲረዳ ካስተማርከው ሽባውን አዳንህ ማለት ነው ፣ ወደ ቤተ ክርስቲያን መሄድ እንዲችል ካደረግህ አንካሳውን ፈውሰሃል ፣ ሙት ማንሣት ከፈለግህ ደግሞ ንስሓ እንዲገባ አድርገው ያኔ የሞተ ሰውን አስነሥተሃል ማለት ነው ፤

በል ሂድና ተአምር ሥራ!”

. . .

ጸሎትን እንደ ወታደር ማሰልጠኛ ካምፕ መጠቀም የሚፈልጉ ፣ ሰባት ቀን ዘግቼ ብወጣ አጋንንትን አርበደብዳለሁ ብለው የሚያስቡ ሰዎች አሉ ። ጸሎት ግን የእግዚአብሔርን ፊት የምንፈልግበት እንጂ ከአጋንንት ጋር ነጻ ትግል የምናደርግበት አይደለም ። አንዳንድ ሰዎች መንፈሳዊነት በጣም ሲሰማቸውና ብርቱ ጸሎት ያቀረቡ ሲመስላቸው እነርሱ ባለፉት ሁሉ ሰው የሚወድቅ ፣ በተሳፈሩበት ሠረገላ ሁሉ አጠገባቸው ያለው የሚጮኽ ይመስላቸዋል ። ጸሎት ጸልየን ስንነሣ ሰላማዊ ጌታ ጋ ደርሰን ስለመጣን ፣ ሰዎችም የእኛ ሰላምና ዕረፍት ያገኛቸዋል ብለን ማሰብ እንጂ ፣ እነርሱ ክብራቸውን ጥለው ሲጮኹ የእኛ ቅድስና የሚገለጥ ከመሰለን ይህም በመልካሙ ነገር መበደል ነው ። ምዕራባዊ ቅኝት ያላቸው ስብከቶች ክብረ ነክ የሆኑ ፣ የሰውን ልዕልና የሚንዱ ናቸው ። በዚህ ቅኝት ውስጥ ያሉ ሰዎች ሰውን በጣም ትኩር ብዬ ሳየው ታሪኩ ይገለጥልኛል ፣ ሳፈጥበት መንፈሱ ይጮኻል የሚል አስተሳሰብ አላቸው ። እግዚአብሔር ሰውን እንዴት እንደሚያከብረው ለመረዳት በአርአያው መፍጠሩን ፣ ከነጻነት ጋር ማበጀቱን ፣ ለእርሱ ሲል በመስቀል ላይ መሞቱን ፣ የሚያስገድዱ ኃያላንን ሳይሆን የሚሰብኩ ሐዋርያትን መላኩን ማስታወስ ያስፈልጋል ። መንፈሰ እግዚአብሔር ባለበት ሁሉ ክብር አለ ። እግዚአብሔር መንግሥት ነው ፣ በቤተ መንግሥት ደግሞ ክብር አለ ። 

ተአምራት የማድረግ ጸጋ ከስብከት ጸጋ ይልቅ የሚፈለገው ብዙ ተከታይ ስለሚያተርፍ ነው ። ሰዎችን ለእግዚአብሔር የሚመኙ ማስተማርን ሲፈልጉ ፣ ሰዎችን ለራሳቸው ደጋፊነት የሚሹ ተአምራትን ይፈልጋሉ ። ተአምራትን የማድረግ ፍላጎት ብዙ ገንዘብ የመሰብሰብ ፍላጎት ያላቸው ሰዎች ፣ በሰው ቍስል የሚነግዱበት ዘዴ ነው ። ጌታችን በሽተኞችን ፈውሶ ለማንም እንዳይናገሩ እንዳዘዘ የሚናገር ወንጌል ይዘን ፣ ቪድዮ ቀራጺ አቁመን ተአምራት ለማድረግ እንሞክራለን ። ጌታችን የዳነው ሰው እንኳ ዝም እንዲል ሲናገር ፣ አሁን ግን የዳነው ዝም ብሎ ፈወስን የሚሉ ሰዎች ይለፈልፋሉ ። ከልብ ስናጤነው ለማስታወቂያ እንጂ ለሰዎች መዳን አንጨነቅም ። ዝናችንን ለማግነን የሰውን ዝና መናድ ተገቢ አይደለም ። ሐኪም በር ቆልፎ እያከመ ፣ የሥነ ልቡና ባለሙያ ምሥጢርን ጠብቆ እያማከረ መንፈሳዊ ጸጋ አለን የሚሉ ግን ቪድዮ እየቀረጹ ሰው ያስጮኻሉ ። አብዛኛውን ሰው የሚያስጮኸው የጤፍ ዋጋ አምስት ሺህ ብር መግባቱ ነው ። ሌላ ቦታ ቢጮኹ መንግሥትም ዝም አይልም ። እየተከፈላቸው የሚወድቁ ፣ መምህሬ እንዳያፍር እያሉም በየዕለቱ የመገንደስ አገልግሎት የሚያደርጉ ሰዎች አሉ ። የእግዚአብሔር ቤት መሆኑ ቀርቶ የእኛ ቤት ሲሆን ይህን ብናስብ የሚመጥነንን አስበናል ። ተአምራት ግን አጋንንትም በምትሐት ያደርጋሉና በጣም ጥንቃቄ የሚፈልግ ነገር ነው ። ዋናው ሕዝብን ማስጨብጨብ ነው ብለው የሚያስቡ ፣ ነፍሳቸውን በድለው ለሥጋቸው ያደሩ በጥንቆላ ሳይቀር ትርኢት ለማሳየት ይሞክራሉ ። ለስብከት የሚደክመው ሕዝብ ለተአምራት አለሁ ይላል ። በዐውደ ምሕረቱ ተገኝቶ የማይማረው በካምቦሎጆ ተገኝቶ የአንድን ሰው ከተፈጥሮ በላይ የሆነ ኃይል አየሁ ይላል ። ለቅዳሴው የማይመቸው በየሰርጡ የራሱን ተአምር አድራጊ ያስሳል ። እረኝነት የማይፈልገው እረኛ የሌላቸውን እረኞች ያከማቻል ። ለእውነተኛ አገልጋይ እጁ የሚታሰረው ለትርኢት አቅራቢዎች ግን ሠረገላ ይሸልማል ። ሁሉም ቢጤውን ይወዳል ። ሁላችንም ግን ውሸት ሞገስ በማታገኝበት የሥላሴ ዙፋን ፊት አንድ ቀን እንቆማለን ። 

ተአምራትን በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ የሚያከናውን ሰው የተአምራቱን ክብርና ባለቤትነት ራሱ የሚወስድ ከሆነ ፣ ተአምሩም በእርሱ ስም የሚጠራ ከሆነ አደገኛ ነገር ነው ። መንፈሳዊ ጸጋ የሚጠበቀው በመንፈሳዊ ፍሬ ነው  ። ተአምራት የቤተ ክርስቲያን አንድ አገልግሎት እንጂ ሁሉንም የሚጠቀልል አገልግሎት አይደለም ። ተአምራት የማድረግ ጸጋ አለኝ ብሎ ብቻውን ተገንጥሎ የሚወጣ ሰው ፣ እጅ ራሴ በቂ ነኝ ብላ ከሌሎች የአካል ክፍሎች ተነጥላ ለብቻ ለመኖር እንደመወሰን ነው ። እግር የሌለው እጅ ፣ ዓይን የሌለው እጅ ከአንድ የዛፍ ዝንጣፊ የሚለይ አይደለም ። በቤተ ክርስቲያን አምልኮ ፣ ምሥጢራት ፣ ጸጋ ፣ ፍሬ ፣ ኅብረት በአንድ ጊዜ የሚከናወኑ ናቸው ። ይህ ማለት ከቅዳሴ ከዝማሬ በኋላ ምሥጢራት ይፈጸማሉ ። ድሆችን በማሰብ ፣ የተጣሉትን በማስታረቅ መንፈሳዊ ፍሬ ይከናወናል ። ከክርስቲያን ወንድሞች ጋርም የኅብረት ማዕድ ይቆረሳል ። እነዚህ ነገሮች በአንድነት ፣ በአንድ ቤተ ክርስቲያን የሚፈጸሙ ናቸው ። አንዱ ተነጥሎ ከወጣ አደጋ አለው ። አምልኮ ብቻ ብለው ይዘው የወጡ ምሥጢራትን አቃለው ፣ የወጣትነት ጉልበት ያለበት ዝማሬ ለማቅረብ ይሞክራሉ ። ምሥጢራትን ብቻ ይዘው የወጡ ስብከትን ይጥላሉ ። በጎ አድራጎትን ብቻ ይዘው የሚወጡ የእርዳታ ተቋም ይሆናሉ ። ኅብረትን ብቻ ይዘው የሚወጡ መንፈሳዊ ዕድር ያቋቁማሉ ። ተአምራትን ብቻ ይዘው የሚወጡ የራስ ገዝ አስተዳደር ይሆናሉ ። የራስ ገዝ ናቸውና የራሳቸው ፖሊስ ፣ የራሳቸው እስር ቤት ፣ የራሳቸው የስላላ ጓድ አላቸው ።

ዓይነ ሥውሩ ዲዲሞስ፡- “ዓይንህ ባለማየቱ ኀዘን ይሰማሃል ወይ?” ብለው ቢጠይቁት፡- “ማየት የምፈልገው አንድ እግዚአብሔርን ነው ፤ የሥጋ ዓይኖቼ መጥፋት ደግሞ እርሱን ከማየት ከልክሎኝ አያውቅም” ብሏል ። ሰው ውስጣዊ ዓይኑ ካልበራ የላይኛው ቢበራ ጥቅም የለውም ። እግዚአብሔር የሚታየው በጎሉ ዓይኖች ሳይሆን በንጹሕ ልብ ነው /ማቴ. 5፡8/ ። ቤተ ክርስቲያን በጸሎትዋ፡- ሀበነ እግዚኦ አእይንተ አእምሮ ፣ ወትረ ኪያከ ይርአያ ፤

          አቤቱ የልቡና ዓይኖቻችን አብራልን ፣ 

          ዘወትር አንተን ያዩህ ዘንድ” በማለት ትጸልያለች ። ትልቅ ተአምር አለ ። በወንጌል የሰውን ልቡና ካበራን ዓይን አበራን ማለት ነው ። ወንጌል ሲሰበክ ሰው የራሱን ልክና የእግዚአብሔርን ምሕረት በቅጡ ያያል ። 

በዚህ ዓለም ላይ እጅ ለሌላቸው እጅ መሆን ፣ እግር ለሌላቸውም እግር መሆን የሚያስደስት ነገር ነው ። ደስታ ከሥጋ ፈንጠዝያ ፣ ከአእምሮ ጨዋታ ራቅ ያለ ነው ። ደስታ መንፈሳዊ ነው ። በሌሎች ጉድለት ውስጥ የእኛ ደስታ ተቀምጧል ። ድርሻቸውን ስንሰጣቸው ደስታችንን  ይለቁልናል ። ድሆችን ስለ መርዳት መስበክ ወንጌልን መስበክ ነው ። እጅ እግር የሌለው የዛሬው ክርስትና ፣ ድነናል በሚል የሚያደነቁረን ከንቱ ጩኸት ፣ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ አይደለም ። ሽባ ከመተርተር በላይ ድሆችን እንዲረዱ ምእመናንን ማነሣሣት የበለጠ ተአምር ነው ። ተአምር በየዕለቱ አለ ። የሚያስገርም ክስተት በዙሪያችን ሞልቷል ። የሚጠበቅብን እጃችንን  መዘርጋት ብቻ ነው ። 

ወደ ቤተ ክርስቲያን መሄድ በግርድፉ እንኳ ብናየው ቦታ መለወጥ ፣ በዛፎች ሥር ተቀምጦ በነጻ ንጹሕ አየር ማግኘት ፣ የተከፈተ በርን ሳያንኳኩ መግባት ፣ ማነህ ሳንባል ዘው ማለት ፣ አልቅሰን ለምነን ብንወጣ የካርድ ክፈሉ የማንባልበት ነው ። ከዚያ ሁሉ በላይ ጠለቅ ባለ ምሥጢር ስንመለከተው ለአምልኮተ እግዚአብሔር መታደም ፣ የመላእክትና የቅዱሳን የምስጋና ተባባሪ መሆን ፣ በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ፈውሰ ሥጋ ወነፍስ ማግኘት ነው ። 

አንድን ሰው ከመቃብር ከማሥነሣት በላይ ለንስሐ እንዲበቃ መርዳት ከዘላለም ሞት ማዳን ነው ። የሚበልጥ ተአምር በእጃችን እያለ የሚያንሰውን መፈለግ ተገቢ አለማወቅ ነው ። የአንድ ሰው ከመቃብር መውጣት ፈቃደ እግዚአብሔር ያስፈልገዋል ፣ የአንድ ሰው ንስሐ መግባት ግን የተገለጠ አምላካዊ ፈቃድ ነው ። የአንድ ሽባ መተርተር ሊሆንም ላይሆንም የሚችል ነው ። ወደ እግዚአብሔር ቤት መሄድ ግን የእግዚአብሔርና የአማንያን ደስታ ያለበት ነው /መዝ. 121 ፡ 1/ ። በአገልግሎታችን ዓይን የማብራት ተአምራት አላከናወንን ይሆናል ። ሰውን ግን ከዘላለም ጨለማ በወንጌል ካተረፍን የሚበልጥ ተአምር ሆኖልናል ። ተአምር ማድረግ ልፋት የለውም ፣ እውቀት መስጠት ግን መሥዋዕትነት ይጠይቃል ። እግዚአብሔር ተአምራዊ የሆነ ኑሮን በየዕለቱ እንድንኖር አላደረገም ፣ መደበኛውን ኑሮ ከነ ትግሉ በጸጋው እንድንወጣ ግን ፈቃዱ ነው ። የቤተ ክርስቲያን ቋሚ አገልግሎት ወንጌልን መስበክ ነው ። እምነት ከመስማት እንጂ ከተአምራት አይደለም ። የምንሰማውም የእግዚአብሔርን ቃል ነው /ሮሜ. 10፡17/ ። 

ጌታ ሆይ መረሳታችን እየቆጨን ተአምር ማድረግን ስንለምንህ እባክህ አትስጠን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 6 ቀን 2013 ዓ.ም.

https://t.me/Nolawii

እባክዎ ይህን ቻናል ይቀላቀሉ፣  ለሌሎች ወገኖቻችንም ያስተዋውቁ

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም