መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ትጉና ጸልዩ

የትምህርቱ ርዕስ | ትጉና ጸልዩ

 የተጋነው ለምንድነው ? የተጋነው ለጸሎት ሳይሆን ለወሬ ፣ ለወንጌል ሳይሆን ለመረጃ ፣ ለፍቅር ሳይሆን ለሐሜት ፣ ለእርቅ ሳይሆን ለማባላት ፣ ለምስጋና ሳይሆን ለትችት ፣ ለአንድነት ሳይሆን ለመከፋፈል ፣ ለይቅርታ ሳይሆን ለቂም ፣ ለመገንባት ሳይሆን ለማፍረስ ፣ የወደቀን ለማንሣት ሳይሆን ለመርገጥ ፣ ለማበርታት ሳይሆን ለመፍረድ ፣ ለመስጠት ሳይሆን ለመቀበል ፣ ለመባረክ ሳይሆን ለመራገም ፣ ሆሳዕና ለማለት ሳይሆን ስቀለው ለማለት ፣ ለማሳመን ሳይሆን ለማውገዝ ነው ። ለእግዚአብሔር ሥራ ካልነቃን ለሰይጣን ሥራ እንነቃለን ።
ስለ ሰዎች ብዙ እናውቃለን ፣ በፍርድ ቀን ስለምንጠየቅበት ስለ ራሳችን ግን ምንም አናውቅም ። ሰዎች አጠፉ እንላለን ፣ የራሳችንን ስህተት ግን ካባ እናለብሰዋለን ፣ በእነ እገሌ ቍጣ መጣብን እንላለን ፣ ራሳችንን ግን የእግዚአብሔር ባለሟል እናደርጋለን ።

ለቁርስ ሃያ ደቂቃ እንመድባለን ፣ ለአምስት ደቂቃ ግን ከልባችን አንጸልይም ። ለገንዘብ ስምንት ሰዓት እንሮጣለን ፣ ለእግዚአብሔር ሥራ ግን ምንም አንሮጥም ። ለስፖርት ሁለት ሰዓት መድበናል ፣ ቤተ ክርስቲያን ለመሄድ ግን ደክሞናል ። ለዜና ሠላሳ ደቂቃ እንሰጣለን ፣ ለቃሉ ግን አሥር ደቂቃ የለንም ። ለፊልም ሁለት ሰዓት ሰጥተናል ፣ ድሆችን ለመጎብኘት ግን አንድ ደቂቃ የለንም ። ለሻይ ቡና ሠላሳ ደቂቃ አለን ፣ ለምስክርነት ግን ምንም ሰዓት የለንም ። ከጓደኞቻችን ጋር ሦስት ሰዓት እናወራለን ፣ ከመንፈሳውያን አባቶች ጋር ግን የውልብታ ያህል ጊዜ ሰጥተናል ። ስንት ሰው እንደ ሞተ ለመስማት እንጓጓለን ፣ ስለ ዳነ ሰው ለማመስገን ግን ግዴለሽ ነን ። ጊዜን ላልሰጠን ዓለም ጊዜ ሰጥተናል ፣ ጊዜን ለሰጠን አምላክ ግን ጊዜን ነፍገናል ።ጥቅጥቅ ያለ የጋዜጣ ጽሑፍ ሃያ ገጽ እናነባለን ፣ መጽሐፍ ቅዱስ አንብቡ ስንባል የማንበቢያ መነጽር አልገዛሁም እንላለን ። የስድብ ጹሑፍ አሥር ገጽ እናነባለን ፣ የእግዚአብሔርን ቃል አሥር መስመር ለማንበብ ለጥሩ ዘመድ የሚሆን እንባ እናፈሳለን ፣ እናፋሽካለን ። ጀርባችንን የሰጠነውን እግዚአብሔር በክፉ ቀን እንሻዋለን ፣ ክፉ ቀን አልፎ ያልጨረስነውን ክፋት ለመጨረስ ዕድሜ እንለምነዋለን ። አዎ ትጉና ጸልዩ ።
ዓይናችን እንባ እያፈሰሰ ፣ ልባችን ይስቃል ። እያዘንን መልሰን እናፌዛለን ። ምስኪን ነው እያልን ዞር ብለን ከባድ ሰው ነው እንላለን ። በአፋችን እሺ እያልን በልባችን እንቢ እንላለን ። ካንተ በፊት ያድርገኝ እያል ያለ ድምፅ ደሀው ምን በወጣኝ እንላለን ። አድናቂህ ነኝ እያልን በውስጣችን “ሰው መሳይ በሸንጎ” በማለት እንሳደባለን ። ሰጠሁ እያልን በልባችን ስንት አተርፋለሁ እንላለን ። መነንኩ እያልን ከነቆባችን እንዘላለን ።
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የአዲሱን ኪዳን ድንቅ ሥርዓት ከመሠረተ ፣ ደቀ መዛሙርቱንም ካቆረበ በኋላ ትጉና ጸልዩ አላቸው ። ሰዓቱ ምሽት ነው ። ዓለም ጌታን ለመስቀል የተሰናዳችበት ነው ። ቦታው የጌቴሴማኒ ጫካ ነው ። ይሁዳ ጠላት እየመራ ሊመጣ ነው ። ተግተው ካልጸለዩ ጨለማው ሊያስደነግጣቸው ፣ ከዓለም ጋር ጌታን ሊሰቅሉ ፣ በጫካው ውስጥ ከይሁዳ ጋር አምላክን ሊሸነግሉ ይችላሉ ። ተግተው የሚጸልዩት ከራሳቸው ለመዳንም ነው ። ክዳት የሚገባብን የውጭ ወራሪ ሳይሆን ከውስጣችን ብቅ የሚል ሰባሪ ነው ። እርሱን የሚጠቀጥቀው በጸሎት መትጋት ብቻ ነው ።
ከቆረቡ ፣ ከዘመሩ ፣ ኅብረት ካደረጉ በኋላም መፈተን አለ ። እግዚአብሔር ከእኛ ጋር የሆነው እኛ ከእርሱ ጋር እንዳንሆን አይደለም ። ያመነው በጎ ላለ መሥራት ፣ የቆረብነው ተኝቶ ለማደር ፣ ኅብረት ያደረግነው ተመሳስሎ ለመኖር አይደለም ። ጌታችን በዚህች ሌሊት ሁላችሁ በእኔ ትሰናከላላችሁ ሲል ጴጥሮስ ሁሉ ቢክዱህ እኔ አልክድህም አለ ። እምነት ሳይሆን ፉከራ አሰማ ። ውጤቱ ግን ሁሉ ሳይክዱ ጴጥሮስ ካደ ። ስለ ራሳችን ያለን ከፍተኛ ግምት ፣ ስለ ሰዎች ያለን ዝቅተኛ ግምት የማይጨባበጥ ነው ። ያውም በሚያውቀን እግዚአብሔር ፊት መፎከር ከንቱ ነው ። “እመት ስመኝ ለማያውቅሽ ታጨኝ” እንዲሉ ። ጴጥሮስ በራሱ ተማመነ ። በራስ መተማመን የሥነ ልቡና ግንባታ ነው ፣ በእግዚአብሔር መተማመን ግን የሃይማኖት ፍሬ ነው ። በራስ መተማመን ሌሎችን እንዲንቅ አደረገው ፤ ሌሎችን መናቅም ተግቶ እንዳይጸልይ አደረገው ።
ጌታችን አሁንም ጴጥሮስን፡- ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ ፤ መንፈስስ ተዘጋጅታለች ሥጋ ግን ደካማ ነው አለው።” ጸሎት ወደ ፈተና እንዳንገባ ይጋርዳል ፣ ከገባንም የውጪያውን በር ያሳየናል ። የፈተና ዘመንን ጉልበትም ሀብትም አያልፈውም ፣ ጸሎት ብቻ ድልድይ ሁኖ ከመከራ ቀን ያሻግራል ። በዚያች ሌሊት የነበረው ፈተና ምንድነው ? ስንል ክርስቶስን መካድ ነው ። በሕይወት ውስጥ ሕይወት የሆነውን ጌታ ከመካድ የበለጠ ፈተና የለም ። ያለ መጸለይ ፈተና የመካድ ፈተና ውስጥ ይጥላል ። በጸሎት የደከሙ እንደ ጴጥሮስ ሰይፍ ለመምዘዝ ይተጋሉ ፣ ለመካድ ቅርብ ይሆናሉ ። መንፈሳዊ ውጊያን በጸሎት መዋጋት ካልቻልን በሰይፍ ወይም በስድብ ሥጋዊ ውጊያ መዋጋት እንጀምራለን ።
ጴጥሮስ በራስ መተማመኑ ሌሎችን እንዲንቅ ፣ ሌሎችን መናቁ ተግቶ እንዳይጸልይ ፣ ተግቶ አለመጸለይ ፣ ሰይፍ እንዲመዝዝ ፣ ሰይፍ መምዘዝ ጌታን እንዲክድ አደረገው ።
በራስ መተማመን፡- ዓለሙ እምቅ ኃይል አለህ እያለ ይሸነግለናል ፣ እኛ በውስጣችን ያለው እምቅ ድካም ነው ። ደክመን የማናባራ ሰዎች ነን ። የአረም እርሻ እስክንመስል መልካም ነገር ይታጣብናል ። የትችላለህ ስብከቶች እውነተኛውን ወንጌል እንድንንቅ አደረጉን ። የሐሰት ነቢያት በራስ መተማመን ስብከቶችን በመስበክ በትዕቢት ይጥሉናል ። እንደ አዝማሪ ስማችንን እየጠሩ ሲያወድሱን ኪሳችን ኪሳቸው ይሆናል ። በሽታ መጥቶ ተጠንቀቁ ሲባል የእኔ እጅ በሽታ ያቃጥላል እያልን እንድንቃጠል ያደርገናል። በራስ መተማመን እንደ ባሎን በነፋሱ አቅጣጫ እንድንጓዝ ፣ እንደ ፊኛ አብጠን በአየር ላይ እንድንጎማለል ያደርገናል ። እኔ ፣ እኔ የሚሉ የበታችነት ስሜት የሚወልዳቸው ድምፆችን እናበዛለን ። እኔ ፣ እኔ በማለት ትዳር ይፈርሳል ፣ ወዳጅነት አፈር ይበላል ።
ሌሎችን መናቅ፡- የተከበረ ያከብራል ፣ የተናቀ ይንቃል ። የበታችነት ስሜት የበላይነት ስሜት ይወልዳል ። ስለ ሰዎች ክፉ ሲያወሩ የሚውሉ ስለ ራሳቸው ማሰብ የማይፈልጉ የኅሊና ቍስለኞች ናቸው ። አሁንም ስለ ሰዎች የሚያወሩ ግባቸው እኔ ትልቅ ነኝ ለማለት ነው ። ሌላውን ካላሳነሡ ፣ ሌላውን መናፍቅ ፣ የሚሸቃቅጥ ካላሉ ስቃዩ አይታገሥላቸውም ። እምነት እፎይ ያሰኛል ። የሰው ጓዳ ሲቧጥጡ ማደር አለመተኛት ፣ አለማረፍ ነው ።
ተግቶ አለመጸለይ፡- የዚህ ዓለም ዘመን በጣም አጭር ነው ። ያዕቆብ ዘመኔ አጭር እርስዋም መከረኛ ናት ያለው መቶ ሠላሳ ዓመት ኑሮ ነው ። /ዘፍ. 47፡9/ የእኛ አርባና ሃምሳ ዓመት ምን ሊባል ነው ? በአራዊት መንደር ውስጥ የሚያልፍ ሰው ሊይዛቸው የሚገቡ የተለያዩ ነገሮች አሉ ። አንበሳ ሰፈር ሲደርስ እሳት መያዝ አለበት ። አንበሳ እሳት ጎፈሬውን ከያዘ እንደማይለቀው ያውቃል ። ስለዚህ ይፈራል ። ሰይጣን የሚፈራው ፉከራን ሳይሆን ጸሎትን ነው ። በሰላም ውለን ስንገባ የሚታየን ተመስገን ብሎ ለመጸለይ ነው ወይስ ቴሌቪዥን ለመክፈት ነው ? ተግቶ መጸለይ በማዕበል ውስጥ በሰላም ያሻግራል ።
ሰይፍ መምዘዝ፡- ለጸሎት የተኛው ጴጥሮስ ሰይፍ ለመምዘዝ ነቃ ። እግዚአብሔር ቅዱስ ነው በመግደል አይከብርም ። እግዚአብሔርን በጸሎት ሳይሆን በስድብ ለማስከበር የወጡ እንዴት ማስተዋል አጥተዋል ? እንኳን እግዚአብሔር የመከራቸው ጨዋ ያሳደጋቸው አይመስሉም ። ጴጥሮስ በሰይፉ የጆሮ ቀንበጥ እንደ በጠሰ ጭው የሚያደርግ ስድብ ይዘው የሚወጡ አያሌ ናቸው ።
ክርስቶስን መካድ፡- ክህደት ወይ በአፍ ወይ በተግባር ነው ። በአፋቸው እግዚአብሔር አለ እያሉ በሥራቸው ግን እንደሌለ አድርገው የሚኖሩ አሉ ።እንደ ጴጥሮስ በአፍ እየካዱ በልብ ማመን ፣ እንደ አርዮስ በአፍ እያመኑ በልብ መካድም አለ ። ክህደት ግን ሩቅ አይደለም ። ጴጥሮስም ክዷልና ። እኔ አላደርገውም አትበሉ ፣ ጴጥሮስም አላደርገውም ብሎ አድርጎታል ። ተግቶ መጸለይ ግን ይሻላል ።
ሰዓቱ ጨለማ ፣ ዓለም ክርስቶስን በክፋት ሥራዋ ልትሰቅል የወጣችበት ፣ ይሁዳ ጠላት መርቶ የመጣበት ፣ ድንዛዜ የበዛበት ቢሆንም አሁንም ተግታችሁ ጸልዩ ። በመንፈስ ካልተዋጋችሁ በሥጋ ትዋጋላችሁ ። የሥጋ ውጊያ መጨረሻው ክህደት ነው ።
ጸሎት
ጌታዬ ሆይ አንተ ራስህን ለእኔ የሰጠህበት ልክ እኔ ራሴን ላንተ ለመስጠት የሰሰትኩበት ልክ ሊወራ አይችልም ። ላንተ የሰሰትኩትን ለዓለም ሰጥቻለሁ ። ስጸልይ ለማደር ደክሜ ስበድል አድራለሁ ። አንተ ያለ እኔ ትኖራለህ ፣ እኔ ያላንተ አልኖርም ። ከማስፈልግህ ይልቅ ታስፈልገኛለህ ። እባክህን በቃልህ ላስስህ ፣ በእምነት ላግኝህ ። የጸሎት ሕይወቴን ጠግንልኝ ። መፍትሔውን እያወቅሁ እሞኛለሁ ። ፀሐይህ አይጠልቅም ፣ ፍቅርህም አይለወጥም ። ለዘላለሙ አሜን ።
የመስቀሉ ገጽ 2
ሚያዝያ 8 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም