የትምህርቱ ርዕስ | ነፍሴን አነሣለሁ

“አቤቱ ፥ ወደ አንተ ነፍሴን አነሣለሁ ።” መዝ. 24 ፡ 1 ።

የፍጥረት ሩጫ ሲገታ ፣ ተራራ ስምጥ ሲሆን ፣ የገዘፈው ሲረቅቅ ፣ የጀመረው መፈጸም ሲሳነው ፣ የታየው ሲታጣ ፣ አለሁ ያለው ከጎን ሲጠፋ ፣ ያቀፈው ክንድ ሲነቀል ፣ ያወደሰው አፍ ዲዳ ሲሆን ፣ ያሳመነው ሲያስክድ ፣ ያገለገለው ክፉ ጌታ ሲሆን ፣ የሞላለት ሲጎድልበት ፣ የቸረው ልመና ሲወጣ ፣ ያፈቀረው ሲያፍር ፣ የወደደው በወደደው ሲቀጣ ፣ ሙሉው ሲጎድል ፣ ቅዱሱ ሲረክስ ፣ ያስተማረው ሲታዘብ ፣ የተማረው ሲጨክን ፣ “ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ ጦርነት ናት” ተብሎ ሲነገር ፤ እኔ ግን ነፍሴን ወደ አንተ አነሣለሁ ። ወደ ቡድን ነፍሴን ባነሣ ቡድንም ይበተናል ። ወደ ታተመው መዝገብ ነፍሴን ባነሣ የታተመም ይከፈታል ። ወደ ተደረገው ነፍሴን ባነሣ የሚያዩት ሁሉ ያቆስላል ። ወደ ፍቅር ነፍሴን ባነሣ ፣ የሰው ፍቅር ሻሽ አያደርቅም ። ወደ መልእክቶች ነፍሴን ባነሣ ከሰላም ይልቅ ጦርነትን ያውጃሉ ። ወደ ሞላለት ነፍሴን ባነሣ ጎድሎበት አገኘዋለሁ ። ወደ አስቂኝ ነፍሴን ባነሣ ፣ ሲያለቅስ አገኘዋለሁ ። ወደ አገራት ነፍሴን ባነሣ ፣ ሲናጡ አያቸዋለሁ ። ወደ ተፈጥሮ ነፍሴን ባነሣ ፣ አቅሙ ሲሰበር አስተውላለሁ ። ወደ ቅርቦቼ ነፍሴን ባነሣ ፣ የገዛ ልቤም ሲከዳኝ አገኘዋለሁ ። አቤቱ ፣ ነፍሴን ወደ አንተ አነሣለሁ ።

ብትምረኝም ብትገድለኝም ፣ ብታነሣኝም ብትጥለኝም ወደ አንተ ነፍሴን አነሣለሁ ። ከዓለም ሽልማት ያንተ ቅጣት ይሻለኛል ። ምድር ከምታለብሰኝ አንተ ብትገፈኝ ይበልጥብኛል ። አቤቱ መልካሙ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! በስቃይ ላሉት ዕረፍት ስጥ ። ከብረው ለተዋረዱት ምሕረት አድርግ ። ቀልባቸው ለከዳቸው መረጋጋትን አድል ። ውስጣቸው ለሚናወጥባቸው ሰላምህን ስበክ ። ከወንጌል ለራቁት በፍቅርህ ድረስላቸው ። ጌታ ሆይ ነፍሴን ወደ አንተ አነሣለሁ ። አንተን ብቻ ተስፋ አደርጋለሁ ። የዘላለም ዕዳህ እኔ አለሁብህና ምን አለብህ ? አትባልም ። ጉዳይህ ስሆን አልጠላኸኝም ። ስበድልህ አልካድከኝም ። ሥጋዊ እግሬን ብዙ ዘመን አንሥቼአለሁ ፣ የእግር ደምበኛህ እንደሆንሁ አውቃለሁ ፤ ዛሬ ነፍሴን ወደ አንተ አነሣለሁ ። ከሞት በሚቀሰቅሰው ድምፅህ ለዘላለሙ አሜን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 19 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም