የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ኑዛዜ

ጌታ ሆይ መኖሪያዬ መሥሪያ ቤቴ ነው አልንህ ፣ መሥሪያ ቤቱም እንዳትመጡብኝ ብሎ ዘጋ ። አዋቂዎች ስለ እኛ እየተመራመሩ ነው እንተኛ አልን ፣ እነርሱም ከአቅማችን በላይ ነው አሉን ። ሰንበትን ሽረን ትምህርት ቤቶችን ከፈትን ፣ ስድስት ቀን የሠራነው ሳይበቃን በሰባተኛውም ቀን እንሥራ አልን ፤ ትምህርት ቤቱም ፤ ለወራት ተዘጋ ። አንድ ሰንበትን ሽረን ሰባቱንም ቀን ሰንበት አደረግኸው ። ከምርጫ ግርግር ለመዳን ብለን ውጭ አገር ኮበለልን ፣ እዚያም ሞት ቀድሞ ጠበቀን ። ይህ መሬት የእኛ ነው ውጣልን ተባባልን ፣ እጃችሁ የእናንተ አይደለም አፋችሁን አትንኩ ተባልን ።ጎዳናው ማረፍ ፈልጎ ለመነህ ፣ አንተም ሰምተኸው ጸጥ አደረግከው ። ሰማዩን በተበከለ አየር ጋረድነው ፣ እኛን እቤት ስታስቀምጥ ውበቱ ፈክቶ ይኸው እየሳቀ ነው ። በሽታውን ከእንስሳ መጣብን አልን ፣ በልተውን ሳይሆን በልተናቸው መሆኑን ረሳን ። ጭጋጉ ያደጉ ከተሞችን ሸፍኖ ነበር ፣ ይኸው ከዋክብት ሊያበሩ መጡ ። አንድ በሽታ ሲመጣ የሚያጠቃው ጥቁሮቹን ነው አልን ፣ ሁሉም የሚያቃስትበትን በሽታ አመጣህ ። እግዚአብሔር አላመጣውም ሰዎች ለቀውብን ነው አልን ፣ ክፉዎችን በክፉዎች እንደምትቀጣ ረሳንህ ። እኛን አይነካንም ብለን ተመጻደቅን ፣ እምነታችን ከካዱት የተለየ እንዳልሆነ አሳየኸን ። ጸሎታችን ልዩ ነው አልንህ ፣ የወንድም ቀባሪዎችን ጸሎት መስማት መቼ ጀምረህ ነው ? ያልታመመውን ካልፈወስን እያልን ነገድን ፣ የታመመ ሲመጣ አዳራሹን ለቀን ወጣን ። እግዚኦ ብንል አልን ቅዱሶቹን አርክሰን ፣ አማኞቹን አውግዘን ፣ ንጹሖቹን ስም ሰጥተን የምትሰማን መስሎን ተታለልን ። አቤት ፣ አቤት እያልንህ እህል እንደብቃለን ። እየጸለይን ሰውን እንዘርፋለን ።

የእኔ ዘር ያልሆነ አልይ አልን ፣ እናትና ልጅን የማያስተያይ በሽታ ተማለን አወረድን ። ሰው ዘቅዝቀን ሰቀልን ፣ አየር የሚያሳጣ ጉድ መጣብን ። ያለ ፍርድ ሰውን እንደ እባብ ቀጥቅጠን ገደልን ፣ ፍርድ ቤት የሚያዘጋ የበሽታ ባለሥልጣን ከተፍ አለብን ። የገደልነውን ሬሳ አይነሣም ብለን ፎከርን ፣ ቀባሪ የሚያሳጣ ደዌ ጎተትን ። ጠግበን ነበረ ፣ የምንናገረውን መመጠን አቅቶን አፍስሰነው ነበረ ። በሰማይ ደመና እንጂ ዙፋን አልታየንም ነበር ። ጌታ ሆይ እንዴት ታዘብከን ።
በጣም ተገፋፋን ፣ አብሮ አደጎች ተካካድን ፣ በሚያራርቅ ሕመም አትነካኩ ተባልን ። ሥልጣኔአችንን የሚያቆመው ኃይል የለም ብለን ተናግረን ሳንጨርስ ጉንፋን አቆመን ። የአንዲት አገር በሽታ ነው ብለን ስንሳደብ የሁሉም አገር እንዲሆን አደረግን ። ተፋፍገው የሚኖሩ ድሆች በሽታ አያጣቸውም አልን ፣ ቤተ መንግሥት የሚኖሩ ሲጠቁ አየን ። ፈረንጅ አገር ሂዶ መምጣት ልዩ ነገር መሰለን ፣ ዛሬ የሚያሳስበን ሆነ ። ግደለኝ እያልንህ ስንለምንህ ከረምን ፣ ዛሬ አልኮል ለመግዛት ተሰለፍን ።
የዛሬውን ችግር ሳናይ የትላንቱን አደነቅን ፣ ይባስ እንደማያልቅ አስተማርከን ። ሁሉም ነገር አንድ ቀን ቀጥ እንደሚል ዋዜማውን አሳየኸን ። ቃልህን ለመስማት ኮራን ፣ የተማርኩት በቂ ነው አልን ፤ ስብከተ ወንጌል የለም ተባልን ። ቅዳሴ ለማስቀደስ ተፈተንን በየቤታችሁ ሁኑ ተባልን ። ሰው ሰብስቦ ማስተማር ሰለቸኝ አልን ፣ ባዶ ቤት መስበክ ጀመርን ። ሰው ሰላም እንዳይለን እንሸሽ ነበር ፣ በአዋጅ አትጨባበጡ ተባልን ። የጠላነው መነካካት ዛሬ ሕግ ሆኖ መጣ ። መተቃቀፍ አስጠላን ፣ የሚተቃቀፉትን ፖሊስ ይለይ ተባልን ። ጨረቃ ላይ ደርሰናል ብለን ስንኮራ ገና እጃችሁን ታጠቡ የሚል ምክር እንሰማለን ። ጠላት አለብኝ እያልን ስንለፈልፍ በእጃችሁ ዓይናችሁን እትንኩ ፣ እጃችሁ ነው ጠላታችሁ ተባልን ።
ለትዳራችን የሚሆን ጊዜ አጥተን ተረሳስተን ነበር ፣ አሁን ሃያ አራት ሰዓት አብረን ስንቀመጥ ተፋጠጥን ። ሥራችንን ጠልተን ጥቁር ሰኞ እንል ነበር ፣ ዛሬ መሥሪያ ቤቱ ናፈቀን ። ሰዓቱ ሳይሞላ ከሥራ ወጥተን ነበር ፣ ዛሬ ትርፍ ሰዓት መሥራት አማረን ። ከሠራነው ላይ አሥራት ለመስጠት ተፈትነን ነበር ፣ ዛሬ ግን ያስቀመጥነውን ያለ ደስታ እንበላለን ።
ጌታ ሆይ ጣትህን ብትዘረጋ እንዲህ የሟሸሽን ክንድህን ብትዘረጋ የት ልንገባ ነው ? ብናኝ ልጆችህን ይቅር በለን ። አክብረኸን ማረን እንጂ አክብረኸን እንዳትጣላን ። እኛ ሰው ፣ አንተ አምላክ ነህ ። እባክሀ ይቅር በለን ። በመልካም አስበን ።
ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ክብር ምስጋና ይሁን ። ከምታልቀዋ ከዛሬዋ ቀን እስከማይፈጸም ዘመን ። ከደካማው ልባችን እስከ ጸናው ሰማይ ። ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና 19
መጋቢት 21 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ