መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » አስተማሪዎቻችን

የትምህርቱ ርዕስ | አስተማሪዎቻችን

“ደስተኛ ያልሆኑ ደንበኞችህ ዋናዎቹ አስተማሪዎችህ ናቸው ።” ቢል ጌትስ

ጀማሪዎች የሚኖራቸውን ፣ ማዕከላውያን ያላቸውን ፣ ምሉዓን የሌላቸውን መስማት ይፈልጋሉ ። ጀማሪዎች ተስፋ ይፈልጋሉና የሚኖራቸውን ፣ ማዕከላውያን ብርታት ይፈልጋሉና ያላቸውን ፣ ምሉዓን ግን ማደግ ይፈልጋሉና የሌላቸውን መስማት ይናፍቃሉ ። ጀማሪዎችን ያላቸውን ብንነግራቸው ትዕቢተኛ ፣ የሌላቸውን ብንነግራቸው ደንባራ ይሆናሉ ። ማዕከላውያን ለበጎ ሥራ ሲጣጣሩ ተቃውሞን ይፈራሉና ያላቸውን መልካም ነገር ብቻ መስማት ይሻሉ ። ለማዕከላውያን የሌላቸውን ብንነግራቸው ቶሎ ተስፋ ይቆርጣሉ ። ምሉዓን ገና የማደግና የመለወጥ ናፍቆት አላቸውና የሌላቸውን ሲሰሙ እንደገና ለመሥራት ይነሣሉ ። ለምሉዓን የሚኖራቸውን ብንነግራቸው የሚኖረኝ ስኬት ካለኝ ክርስቶስ አይበልጥም ብለው አርፈዋል ። ያላቸውን ብንነግራቸው ያረጋጋቸዋል እንጂ አያሠራቸውም ። የጎደላቸውን ስንነግራቸው ግን ገና መሥራት እንደሚችሉ ይሰማቸዋል ። ለሰው በቅንነት የሌለውን መንገር መሙላት ትችላለህ ብሎ ማክበር ነው ። ለሰው በጥመት የሌለውን መናገር እኔ ካንተ እሻላለሁ ለማለትና የበታችነት ስቃይን ለማስታገሥ የሚደረግ ሙከራ ነው ።

በዚህ ዘመን በሀብት ቍጥሩ ከፍተኛ ተብሎ የሚነገርለት ቢል ጌትስ ነጋዴ ነውና በንግዱ የተማረውን ሲገልጥ፡- “ደስተኛ ያልሆኑ ደንበኞችህ ዋናዎቹ አስተማሪዎችህ ናቸው” ብሏል ። ደንበኞች ለምን ደስ አልተሰኙም የሚለው ነገር እንደገና ለማሰብ ዕድል ይሰጣል ። የሠሩትን ፣ ያቀረቡትን ፣ ያደነቁትን ነገር ከልሶ ለማየት ያስችላል ። የማይረኩ ደንበኞች ጎደለ የሚሉት ነገር ቀጣዩ ሥራ ላይ ሲጨመር የበለጠ እየተዋበ ይመጣል ። ውበት የሚመጣው ጉድለትን ከማስወገድ ነው ። ዓይን ላይ ያለውን ቆሻሻ ማጽዳት ውበት ያመጣል ። ውበት ያለው ጉድለት አጠገብ ነው ። የዓይንን ቆሻሻ ለማየት መስተዋት ወይም ወዳጅ ሊነግረን ያስፈልጋል ። ውበት የሚመጣው ጉድለትን ከማወቅ ነው ። ሰው የዓይኑን ቆሻሻ ሲያይ ቀጠሮ አይሰጥም ። ወዲያው ለማስወገድ ይነሣል ። አንዳንድ ሰዎች የዓይናችንን ቆሻሻ እያዩ አይነግሩንም ። ዓይን ስንቱን ሲያይ ራሱን አያይም ። አንዳንዶች ደግሞ ቆሻሻ እንዳለብን ወይ በቅንነት አሊያም ራስህን አታጸዳም ወይ? በማለት በነቀፋ ይነግሩናል ። በቅንነትም በጥመትም ቢነግሩን የቆሻሻው መኖር ትክክለኛ ከሆነ ወዲያው እናስወግደዋለን ። ወዳጆቻችን ደግሞ ቆሻሻችንን ከመንገር ሊያነሡልን ሲጣደፉ ለዓይኔ የራሴንም እጅ አላምነውም ብለን ቶሎ ብለን እናስወግደዋለን ። ይህን ጎዶሎህን አስወግድ ወይም ልታስወግደው አትችልም በማለት ንግግር የሚጀምሩ አሉ ። በጸጋ  የበሰሉ ግን ማስተካከያውን መንገድ በማሳየት እንዲህ አድርገህ ብታስተካክለውስ ? ይሉናል ። ችግሩን ብቻ ሳይሆን መፍትሔውንም ያሳዩናል ።

ደስተኛ ያልሆኑ ተማሪዎቻችን ብዙ እንድናነብ ፣ የማብራራት ችሎታችንን እንድናዳብር ፣ የንግግር ጥበብን እንድንማር ፣ አሳብ ያለውን ቋንቋ እንድንጠቀም ያደርጉናል ። አንባቢዎቻችን ደስተኛ ካልሆኑ የአቀራረብ ስልታችንን ስናስተካክል መልካም ፀሐፊ ያደርጉናል ። የምንመራቸው ወገኖች ደስተኛ ካልሆኑ የት እንደምናደርሳቸው በትክክል አላወቁምና ራእይ እንዲኖረንና ራእያችንን መግለጥ እንድንችል ያደርጉናል ። የተደሰቱብን የጨበጥናቸው ድሎች ሲሆኑ ያልተደሰቱት ግን የምንጨብጣቸው ድሎች ናቸው ። የተደሰቱብን ሳይገባቸው ሳይረዱት ሊሆን ይችላል ። የሚነቅፉን ግን ሥራችንን እንድንመዝን ያደርጉናል ። የማይደሰቱብን ብዙዎች ሊሆኑ ይችላሉ ። የእነርሱን ጠባይ ከመገምገም ፣ ቅንነት የላቸውም ብለን ከመቀየም ያልተደሰቱብንን ነገር ደግሞ ማየት መልካም ነው ። ሲፈጠሩ ለነቆራ የተፈጠሩ የሚመስላቸው ሁልጊዜ ትችት ያበዛሉ ። አንዳንዴ ወዳጆቻችን የማይነግሩንን ጉድለት ስለሚነግሩን ልናመሰግናቸው ይገባናል ። ከጠመንጃ አፍ ደግ ነገር እንደማይወጣ ከእነዚህ ሰዎች አንደበትም የሚያንጽ ነገር አይወጣም ። ራሳቸውን የጥበብ ፖሊስ አደርገው ያስቀመጡ ፣ ጥበብ አምጡ ቢባሉ በሬን እንደማለብ ወተት የማይወጣቸው ፣ ለመንቀፍ ግን የሰሉ ሰዎች አያሌ ናቸው ። ቢሆንም ይጠቅሙናል ። እነርሱ በጥመት የተናገሩትን እኛ በቅንነት መስማት ይገባናል ። ሐኪም ቤት በዋነኝነት የምንሄደው በሽታችንን እንጂ የማያመንን ጎን እንዲነግሩን አይደለም ። በሽታችንን ለመስማት ብዙ ንዋይ እናፈስሳለን ።

አንዳንድ ባሎች በሚስታቸው ደስተኛ አያደሉም ። እርስዋም ችግሬ ምን ይሆን ? ስትል ፍጹም መንፈሳዊ ወደ መሆን ትደርሳለች ። አንዳንድ ሴቶች በባሎቻቸው ደስተኛ አይደሉም ። ባልም የጎደለኝ ምንድነው ? በማለት ራሱን ሲያይ የበለጠ እየታነጸ ይመጣል ። መምህራኖቻችን ደስተኛ ካልሆኑብን ብዙ ለማጥናትና እውቀት ጠገብ ለመሆን እንጥራለን ።

አንዳንድ ዓለም አቀፍ ተቋማት የጎደለንን አሳውቁን በማለት ችግሮችን ነቅሰው ለሚያወጡ ድርጅቶች ራሳቸውን ክፍት ያደርጋሉ ። ነቃሾቹም ብዙ ክፍያ የሚጠይቁ ሲሆን ድርጅቱ ያለውን ችግር ያለ ይቅርታ ዘርዝረው ያቀርባሉ ። ደስተኛ ያልሆኑብን ግን በነጻ የጎደለንን ነገር እየነገሩን ነውና እንደ አስተማሪዎቻችን ልንወስዳቸው ይገባል ። የተናገሩበትን መንፈስ ማጥናት ጥቅም የለውም ። ይህችን ዓለም ያሳወቁን ከደጎች ይልቅ ክፉዎች የሚባሉት ናቸው ። ደጎችም ጌታን አሳይተውናልና ምስጋና ይገባቸዋል ። እንደገና መሞከር ግን ሥራችንን ውብ ያደርገዋል ። ሠርተን የማንፈጽም ፤ ተሠርተንም የማናልቅ ነን ።

አቤቱ ሥራችንን ባርክልን ።

የብርሃን ጠብታ 9

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 16 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም