የትምህርቱ ርዕስ | አሻግረን

ወዳጄ ሆይ !

ከታገሥህ ሁሉም ያልፋል ፣ በሕይወትህ ከወሰንህ ግን አለማለፍ ዘላለማዊ ይሆናል ። ሞት ወዳንተ መምጣቱ አይቀርምና አንተ ወደ ሞት አትሂድ ። ወደዚህ ዓለም ተመልሰህ አትመጣምና ሕይወትህን ተንከባከባት ። ብረት ብታገላብጥ ፣ ድንጋይ ብታንከባልል የቆምከው ግን በአፍንጫ እስትንፋስ ነውና በማስተዋልና በጥንቃቄ ኑር ። አለመሳካት ማለት አለመኖር ማለት አይደለም ። ራእይ አልባ ሰው ካርታውን የጣለ መንገደኛ ነው ። ውጤቱም ተንከራታች መሆን ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

ሰዎች የዘሩትን ሲያጭዱ ስታይ አንተም ዛሬ እየዘራህ ነገ ደግሞ የምታጭድ መሆኑን አስብ ። የዕድሜ ጀምበር የሚጠልቀው አንዱ ባንዱ ሲስቅ ነው ። ዕድልን ዕድል ተሰጥቷቸው ካመለጣቸው ሰዎች ተምረሃት አክብረህ ያዛት ። የወደደም ይጠላል ፣ ያከበረም ያዋርዳል ። ሳትዋዥቅ የምትኖር ግን እውነት ብቻ ናት ። 

ወዳጄ ሆይ !

በየዋህነቴ ተጎዳሁ ብለህ ጨካኝ አትሁን ፣ ነገር ግን ብልህ ሁን ። የደስታ ጊዜ ረጅም ቢሆን አጭር ፣ የመከራ ጊዜ አጭር ቢሆንም ረጅም ነው ። ጓደኛን አለማመን ሁልጊዜ በሥቃይ ውስጥ መኖር ነው ። የምትሠራው የሚጠፋህ ራስህን ማድነቅ ስትጀምር ነው ። መልካም ሰውን በውድ ገዝተን በርካሽ መሸጣችን ትልቁ ኪሣራችን ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

ሰው ስልክ ሲያወራ ሣንቲሜ ቆጠረ እንጂ ዕድሜዬ ቆጠረ አይልምና ከዕድሜው ይልቅ ለሣንቲም ዋጋ እንደ ሰጠ ያሳያል ። በሽተኛ በሌለበት እንፈውሳለን የሚሉ ፣ በሽተኛ ሲመጣ ግን የሚጠፉ ናቸው ። ፈውስ በፕሮግራም ሳይሆን በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው ። ማስታወቂያ የበዛበት አገልግሎት ከእውነት ይልቅ የዝና ፍቅር ያለበት ነው ። ነቢያት ስላልመጣው ዘመን ያውቁ ነበር ፤ እኛ የምንኖርበት ዘመን ተሰውሮብናል ። ሐዋርያት ሄደው ይሰብኩ ነበር ፣ እኛ ግን መጥታችሁ ተሰበኩ እንላለን ። ሰማዕታት ለክርስቶስ ፍቅር ሞቱ ፣ እኛ ግን ለጥቅማችን እንገድላለን ። ጻድቃን ጣዕመ ዓለምን ንቀው መነኑ ፣ እኛ ግን ዓለም መራራ ሆናብንም ገና እንፈልጋታለን ። ቅዱሳን ከሕግ አልፈው በትሩፋት ኖሩ ፣ እኛ ግን የታዘዝነውን መፈጸም ተስኖናል ። ደናግል መነኮሳት የክርስቶስ ሙሽሮች ሆኑ ፣ እኛ ግን በአሚናችን/በአንድ መጽናት አቅቶናል ። ሊቃውንት አህያ የማትሸከመውን መጽሐፍ በቃላቸው አጠኑ ፣ እኛ ግን በአንድ ጥቅስ ያዙኝ ልቀቁኝ እንላለን ። 

ጌታ ሆይ ከዘመን ማዕበል እባክህ አሻግረን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ኅዳር 21 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም