የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

አባ ጠቅል

“በክርስቶስ ለማድረግ እንደ ወደደ እንደ አሳቡ፥ የፈቃዱን ምሥጢር አስታውቆናልና፤በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው።” ኤፌ. 1፡9-10።

ይህ ዓለም በክርስቶስ ተፈጠረ ። በክርስቶስ ዳነ ። እርሱ የአብ ክንዱ ፣ የአብ እጁ ነው ። ሰው በክንዱ ቢገለጥ ፣ በእጁ ቢሠራ እርሱ ሠራው እንጂ ማንም ሠራው አይባልም ። እንዲሁም ክርስቶስ የሠራው ሁሉ አብ የሠራው ነው ። የአብ ክንዱና እጁ ነውና ። ክንድና እጅ ከአካል ሳይለዩ ሥራ እንደሚሠሩ እንዲሁም ክርስቶስ ከአብ ሳይለይ ወደዚህ ዓለም መጥቷል ። እርሱ በሠራው ሥራም አብ ምክሩ ፣ መንፈስ ቅዱስም ሕይወቱ ነውና ምስጋናችን ሥላሴያዊ ነው ። በሌላ አነጋገር ሦስቱ ፍጹማን የሥላሴ አካላት በምስጋና አንድ ናቸው ። አብ ባለበት ወልድና መንፈስ ቅዱስ እንዳሉ ሁሉ ወልድ ባለበትም አብና መንፈስ ቅዱስ አሉ ። እርሱ አብ ዓለምን የፈጠረበትና ዓለምን ያዳነበት ልጁ ክርስቶስ ነው ። ሰው አሳቡን የሚገልጠው ልቡን አውጥቶ ሳይሆን ቃሉን ልኮ ነው ። እንዲሁም እግዚአብሔር አብ ልብ ነውና አይታይም ፣ ክርስቶስ ቃል ነውና ሥጋ ለብሶ ተገልጧል ። ቃል አሳብና ሕይወት አለው ። ቃል በአሳብ ውስጥ ሲዋቀር ሕይወትም ለአሳብም ለቃልም አስፈላጊ ነው ። እንዲሁም ወልድ ያለ አብ አልነበረም ። መንፈስ ቅዱስም ከአብና ከወልድ ተለይቶ አያውቅም ። ያለ ቃል መገለጥ እንደሌለ አብም ያለ ልጁ ሥራ አይሠራም ። ሕይወት በሌለበትም ህልውና እንደሌለ መንፈስ ቅዱስ በሌለበትም አብና መንፈስ ቅዱስ መኖር አይችሉም ። መንፈስ ቅዱስ ለራሱ ፣ ለአብና ለወልድ እንዲሁም ለፍጥረት ሕይወት ነው ።

ዓለም ሲፈጠርም ሆነ ሲድን የእግዚአብሔር ዘላለማዊ ምክር ፣ አምላካዊ ቃልና ዘላለማዊ ሕይወት አብረው አሉ ። ይህም ሦስቱ አካላት አሉ ማለት ነው ። ተግባሩ አሳብ ፣ ቃሉም ልብ ያለው ነው ካልን እኛም ከተግባራችን በፊት አሳብን ማስቀደም ፣ ከቃላችንም በፊት ማሰላሰል ይገባናል ። እግዚአብሔር በቃሉ ስህተት ሳይኖርበት እንከን በሌለው ምክሩ ይመክራል ። እኛ ግን በቃላችን አፍራሽነት አለብንና አሳባችንም ያልተጣራ ነውና ማሰብ ያስፈልገናል ። ቃላችን አሳብ ያስፈልገዋልና አስበን መናገር ያስፈልገናል ። ተናግረን ማሰብ ግን ሞኝነት ነው ።

ሐዋርያው እንደ ወደደ ፣ እንደ አሳቡ ፣ የፈቃዱ ምሥጢር የሚሉትን ደገኛ ቃላትን ይጠቀማል ። የእግዚአብሔር ውዴታ ሰውን በመፍጠርና በማዳን ተገልጧል ። ሰው ራሱን መቀበል ቢከብደው ለሰዎችም የማይፈታ ቅኔ ቢሆን እንኳ እግዚአብሔር የወደደው ነው ። የተፈጠረው በስህተት ፣ በወላጆቹም ውዴታ አይደለም ። ሰው የእግዚአብሔር ፍቅር ውጤት ነው ። በዚህ ዘመን ፣ በዚህ አገር ፣ በዚህ ቤተሰብ ራሴን ሳገኘው ይህ የእግዚአብሔር ውዴታ ነው ። እግዚአብሔር የወደደውን ማንነቴን እኔ መጥላት ፣ እግዚአብሔር የወደደላቸውን እኛ መጥላት ፣ ጥቁር ነጭ ፣ ሀብታም ደሀ እያሉ ሰውን መናቅ ፣ ማሳደድ አይገባም ። ይልቁንም በጎሠኝነት ሰውን የሚገድሉ በቀጥታ ከዚህ አምላካዊ ውዴታ ጋር እየተጣሉ ነው ። በዚህ ዓለም ላይ እኛ የወደድነው እንጂ አንተ እግዚአብሔር የወደድከው መኖር አይችልም እያሉ ነው ። ሰውን ግዙፍ ሰይጣን ፣ ልቡሰ ሥጋ ጋኔን የሚያደርገው ዘረኝነት ነው ። እግዚአብሔር ፈጣሪነቱን ማንም እንደማይቀማው የአዳኝነቱ ምስጋናም ገንዘቡ ነው ። እርሱ በመውደዱ ታላላቅ ተግባራትን እንደ ፈጸመ ፣ ፍቅሩም ጸጸት የለበትም ። ሰውን ለመፍጠር እግዚአብሔር ከእግዚአብሔር ጋር መከረ እንጂ ማንም ምክር አላቀረበለትም ።

ቅዱስ በሆነው አሳቡ ከዘላለም በፊት አሰበን ። ቀኑ ሲደርስም አዳነን ። ጊዜ ሳይጀመር ወዶናልና በጊዜ ውስጥ ይጠላናል የሚል ስጋት የለብንም ። ነገ ጊዜ ነውና ነገ ይጠላናል ብለን የማንጠረጥረው እግዚአብሔር ነው ። ፍቅሩ እንደ አካሉ ዘላለማዊ ነው ። እንደ ፈቃዱ ይላል ። ፈቃድ መወሰን ፣ የተግባር ዋዜማ ፣ የመሆን ቁርጥ አሳብ ነው ። እንደ ፈቃዱ አዳነን ። ፈቃዱ ምሥጢር ያለበት ነው ። ይህ ምሥጢርም እስከ ጊዜው የተሸሸገ ሲሆን ዘመኑ ሲደርስ የተገለጠ ነው ፤ ሁለተኛው ትርጉሙ ምሥጢር የተባለው ድንቅ ፣ ሊያዩትና ሊያገኙት የሚያጓጓ ተብሎ የሚፈታ ነው ። ይህ ምሥጢርም ፣ የአበው ተስፋ ፣ የነቢያት ትንቢትና ሱባዔ ፣ የክርስቶስ ሰው መሆንም ግቡ በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በእርሱ ለመጠቅለል ነው ። መጠቅለል መግዛትና ማስተዳደር ፣ ሁሉን በእግሩ ሥር ማስገዛት ነው ። ግዛት ከድቶት ወደ ዓለም አልመጣም ፣ ሁሉ ይገዛለታል ። አሁን በሰማይና በምድር ታርደሃልና ተብሎ በሰውና በመላእክት እንዲመሰገን ፣ የአዳኝነቱ የምሥራችም ለፍጥረት ሁሉ እንዲሰበክ የሥላሴ ፈቃድ ሁኗል። እግዚአብሔር አብም በክርስቶስ መመስገንን ወዶአልና “በአሐዱ ወልድከ” – በአንድ ልጅህ ብለን እናመሰግነዋለን ። ይህም ሁሉም ነገር በክርስቶስ መጠቅለሉን የሚገልጥ ነው ። የየዕለት ርእስ ፣ የሰማያውያንና የምድራውያን የምስጋና ድምፅ “ታርደሃልና ቅኔ ይገባሃል” የሚል ነው ።

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /19

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 5 ቀን 2014 ዓ.ም.

እባካችሁ ለሌሎች አካፍሉት

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ