መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » አንተን አንተን ያሉ

የትምህርቱ ርዕስ | አንተን አንተን ያሉ

በአካል ሦስት ፣ በመለኮት አንድ መባል ገንዘብህ የሆነ ፤ አንድነትህ ሦስትነትህን ያልጠቀለለው ፣ ሦስትነትህ አንድነትህን ያልከፈለው በዘላለም ክብር ውዳሴ ያለኸው አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ጌታዬ ፣ በእቅፍህ ለዘላለም በፍቅርህ እስከ ወዲያኛው ባሪያህን ሰውረው ። አላመሰገኑኝም ብለህ የማትከፋ ፤ ባለማመስገናችን ግን የኀዘን ጥላ የሚያጠላብን ፣ ራሳችንን በመጥላት የምንሞገት እኛው ነን ። ተፈላጊ ነኝ ብለህም ራስህን ገሸሽ አላደረግህም ። ብዙ ሠራዊት አለኝ ብለህም አትመካም ። ሠራዊትህንም የምትጠብቀው ንጉሥ አንተ ነህ ። ለክብርህ ፍጥረታትን ፈጠርህ እንጂ ክብር ለማግኘት ያበጀኸው አንድም ፍጡር የለም ። የሰገዱልህ ሲያምፁብን ፣ ያመፁብህ ይሰግዱልሃል ። በቃልህ የተማሩ በሰላም ሲመጡ ፣ በመከራ የተማሩም እያለቀሱ ይመጡብሃል ። አንድም ቀን የምሽት ወዳጅ ነኝ ወይ ? ብለህ በርህን ዘግተህ አታውቅም ። የመሸበት አሳዳሪ ፣ ከራሱ ለወጣም ራስህን የምትሰጥ አንተ ነህ ። ከስፍራችን ስንናወጥ መልሰን የምናገኝህ ከስፍራህ ስለማትናወጥ ነው ። በምስኪኑ ቤት ስታድር ክብሬ ይጎድላል አትልም ፣ ድሀውን ስትወዳጅ የልብሱ መቀደድ አያሳስብህም ። አንዱን በመስጠት ሌላውን በመንሣት ትባርከዋለህ ። ሁሉን እንደ አመሉ ታሳድረዋለህ ። የሌለህበት ጊዜና ቦታ የለም ። የሌለሁበት ጊዜና ቦታ ግን እኔ አለኝ ። ውስኑ ማንነቴ ጽንፍ አልባ ለሆነው ጌትነትህ ይገዛል ። ለመቅረብ ለሚያስፈራው ግርማህ ምስጋና ፣ ሊርቁት ለሚያሳሳው ሞገስህ ውዳሴ ይሁን ። የቆለፍከውን የሚከፍት ለሌለ ፣ የከፍትከውን የሚዘጋ ለሌለ ቅዳሴ ይሁን ። በኋለኛው ቀን አገኘዋለሁ የምለው ዘመድ የለም ፣ ከሞት በኋላ የማገኝህ ዘመዴ አንተ ነህ ። ጥቂት ደቂቃ ለማመስገን ጊዜ እያጣሁ ለዘላለም ለማመስገን ገነትን እናፍቃለሁ ። ወገንነቴ ካንተ ጋር ነው ። ሌላውን የወገኑ አፍረዋል ፣ አንተ ያሉ ድነዋል ። ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና /2/
የካቲት 16 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም