የትምህርቱ ርዕስ | አዳምጣለሁ -1

ይቅር በለኝ አዳምጣለሁ ። ያንተን ቃል አይደለም ፣ አሉታዊ ድምፅን ፣ ከውስጤ የሚያስተጋባውን የአለቀልህን ነጋሪት አዳምጣለሁና ይቅር በለኝ ። ነፋሱ መንቀሳቀስ ፣ ፀሐዩ መፈንጠቅ ፣ ጨረቃ መድመቅ ፣ ከዋክብት መፍካት አቁመዋል የሚለውን የውሸት ድምፅ እውነት ብዬ ስቀበል ያንተን ቃለ ጽድቅ ግን እጠራጠራለሁ ። የማትጠልቅ ፀሐይ ፣ የማትጠፋ መቅረዝ ፣ የሕይወቴ ሕይወት አንተ መሆንህን ቃልህ ሲነግረኝ አላዳምጥም ። አዳምጣለሁ ይቅር በለኝ ፤ ዘመንህ ገሰገሰ ፣ ዕድሜህ ያለ ብልሃት አለቀ ፣ ወራትህ ከሸማኔ መወርወሪያ ይልቅ ፈጠነ የሆንኸውና ያደረግኸው ነገር የለም የሚለኝን የጠላት ድምፅ ሕሊናዬን የተከራየውን የባላጋራውን የቃል ፍላጻ አዳምጣለሁና ይቅር በለኝ ። መሆን ይቀድማል ፣ ተግባር ይከተላል ፤ ካልሆነ ማንነት ተግባር ቢወጣ አይፈውስም ። ከማይራራ ልብ ስጦታ ይወጣል ፣ ወይ ጉቦ ወይ ዝና ፍለጋ ይሆናል ። መሆንን ሰጥቶ ማድረግን የሚያስቀድም እግዚአብሔር ነው ። በገባዖን ሰማይ የቀኑን ሠርክ ማለዳ ያደረገ ፣ ባለቀ ቀን ላይ ቀንን የጨመረ ፣ ተፈጥሮ የሚገዛለት ፣ ጨለማ በእርሱ ዘንድ የማይጨልም ፣ ቀን ቢሉት የማይመሽ ዕድል ፣ ብርሃን ቢሉት የማይጨልም እውነት እግዚአብሔር አለልህ የሚለኝን የመንፈስ ቅዱስ ድምፅ አላዳምጥምና እባክህ ይቅር በለኝ ።

አዳምጣለሁ ይቅር በለኝ ስለ ልደቴ ሳላመሰግን ስለ ሞቴ የሚያስፈራራኝን ፣ እንዴት እዚህ ደረስሁ ? ማለትን ትቼ እንዴት እሆናለሁ ? የሚለኝን ፣ ስለ መኖሬ አስረስቶ ስለ ስኬቴ የሚያዋራኝን ፣ ስለ ጠባቂ መልአኬ አስረስቶ ስለ ከዱ ሰዎች የሚያናግረኝን የጠላቴን ድምፅ አዳምጣለሁና ይቅር በለኝ ።

ጠላቴን በሁለት ጆሮ ፣ አንተን በአንድ ጆሮ አዳምጣለሁና ይቅር በለኝ ። በአንዱ ጆሮ ሰምቼህ በሁለተኛው አፈሰዋለሁ ። ቃልህን በምሰማበት ቦታ አልጋዬንና ትራሴን ልዘርጋ ወይ ? ስሰማህ መልአክ ፣ ስወጣ ሰይጣን ሆኛለሁ ። ጌታ ሆይ አዳምጣለሁና ይቅር በለኝ ። ስለ ታሪክ እጣላለሁ ፣ ስለ ነገ ሰንፌአለሁ ። ጥያቄዬ እያሳሰበኝ የሌሎችን እንቆቅልሽ አናንቃለሁ ። ለመተኛት አልጋ ገዝቻለሁ ፣ እንቅልፍ ግን ያንተ ጸጋ ነው ። ስትነሣ ብትወድቅስ ፣ ስትቆርብ ብታፈርስስ ፣ ስትቀደስ ብትረክስስ ? የሚለውን ድምፅ አዳምጣለሁ ። ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ የሚለውን ያንተን ቃል ግን አላዳምጥምና ይቅር በለኝ ። እዚህ የደረስኩት በዕድሌ ሳይሆን ባንተ የአሳቢነት ስጦታ ነው ። ራሴን በቤትህ ያገኘሁት በእረኝነትህ ፍለጋ ነው ። የሚበዛውን ወራት በራሴ አልኖርኩም ፣ የቀረውን ትንሽ ዕድሜ በአቅሜ ለክቼ እፈራለሁ ። ጌታ ሆይ ! የምኖረው እስከ ዛሬ ማታ ሊሆን ይችላል ። የምጨነቀው ግን ለሺህ ዓመት ቀለብ ነው ።

አላዳምጥምና ይቅር በለኝ ። አንተ የራስህ ፣ አንተ የወላጆችህ ዕቅድ አይደለህም ። አንተ የማኅበረሰቡ ሎሌ ሳይሆን አንተ ለጌታ ፈቃድ የተሠራህ ነህ ። አንተ የሚመስልህ የሌለ ልዩ ነህ ። አንተ ከስኬት በላይ የእግዚአብሔር ልጅ ተብለህ የምትጠራ ነህ ። አንተ ርካሽ ቦታ ብትገኝም የሠራህ እጅ ውድ ነው ። አንተ ሰዎች ቢጥሉህም ብርና ወርቅ ዋጋህ አይደለም ። አንተ በወልደ እግዚአብሔር በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተዋጀህ ነህ ።

ጌታ ሆይ ! ይህን ድምፅህን አላዳምጥምና ይቅር በለኝ ። ጨው ካልሟሟ ጣዕም አይሆንም ። ድንጋይ ነው ተብሎ ይጣላልና ዋጋውን ያጣል ። ክርስቲያንም ላንተ በመሸነፍ ይከብራል ። ለእኔነቱ በመሞት ጣዕመ ዓለም ይሆናል ። እባክህ ላዳምጥህና ጨው ልሁን ። አሜን !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 27 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም