መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እስከ መጨረሻ መውደድ

የትምህርቱ ርዕስ | እስከ መጨረሻ መውደድ

 “ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት ፥ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ ፥ በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው ።” ዮሐ. 13፡1
“በተቀየረብህ ሰው ምክንያት የኀዘን ኑሮ አትግፋ ፣ ይህ ሰው ማስመሰሉ ደክሞት ወደ እውነተኛ ማንነቱ ተመልሷልና” የሚል አንድ አባባል ሰምቻለሁ ። የከዱን የሚመስሉን ሰዎች አብረውን የነበረ ቀን ነው የከዱን ፣ አሁን ግን ጊዜያችሁን አላባክንም ብለው ሄደዋልና ታማኝ የሆኑት ዛሬ ነው ። ብዙ ዘመን ከእኛ ጋር የኖሩት በጭምብል ተሸሽገው ነው ፣ አሁን ግን መሸፈኛውን አውልቀው ገስግሰዋል ። እስከ ዛሬ ሕመም አልባ በሽታ ነበሩ ፣ ዛሬ የሚጠዘጥዝ በሽታ ሆነዋል ። እስከ ዛሬ ሌሎችን እያባረሩ እነርሱ ብቻ አጠገባችን ነበሩ ፣ አሁን ግን ራሳቸውንና መሰላቸውን ይዘው ሄደዋል ። እስከ ዛሬ ድረስ አብረውን የሌሉትን አሉ እያልን እንታለል ነበር ፣ አሁን ሄደዋልና የሌለንን ነገር በትክክል አውቀናል ። አስመሳዮች ከአጠገባችን የሄዱ ቀን ዳግም እንደ ተወለደ ሰው ዓይናችን ተገልጦአል ። እያየን የማናይ ነበርና አሁን ግን አጥርተን አይተናል ። በሌለን ሺህ ከመዝለል ፣ በሌለን ምንም መጸለይ ይሻላል ። አሉ ብለን ከአምልኮ ያራቁን ሲሄዱ የለኝም ብለን እንድንጸልይ ያደርጉናል ። አስመሳዮች ከአጠገባችን የሄዱ ቀን ጠባያቸው ተገለጠ እንጂ ያን ቀን ማስመሰል ጀመሩ ማለት አይደለም ። አጠገባችን ሳሉ አናያቸውም ፣ በሩቅ ያሉ ግን አልሰሜን ግባ በለው እያሉ ለእኛ ያዝኑልን ነበር ፤ ሲርቁን ግን ትክክለኛ ማንነታቸውን አየን ። ሰዎች የከዱን ቀን መዘመር ፣ አስመሳዮች የሄዱ ቀን መሸለም ይገባናል ። ለሐሰተኛ ማንነታቸው ስንመጸውት ኑረን ለእውነተኛ ማንነታቸው መናደድ አይገባንም ። የሰጡን ማደንዘዣ እስከ ነገ እንደሚበቃ እያወቁ ዛሬ በመሄዳቸው ጊዜያችን አትርፈዋል ፣ የዓይናችንን ብዥታ አሳውቀውናልና ልናመሰግናቸው ይገባል ። አንድ ሰው፡- “ብዙዎች መጥተው ብዙዎች ሄደዋል ፣ አንድ ግን ቀርቷል” ብሏል ። እናንተስ  የቀረላችሁ አንድ ማን ይሆን ?

ሰዎች በሰላም መንገዳቸውን እየሄዱ ተባራሪ ጥይት ይገድላቸዋል ። የተተኮሰበት ድኖ እነርሱ ያለ ዓላማቸው ይሞታሉ ። አንዳንዶች የሚደባደቡ ሰዎችን ሲያዩ በስሜት ዘለው ሲገላግሉ ይሞታሉ ፣ ሁለቱም ጠበኞች ያልተጣሉት ሰው ፊታቸው ሲወድቅ ያዩታል ። የተጣላው ቀርቶ ገላጋይ ይሞታል ። ይህ ሟች ስሜቱ እምቢ ብሎት ገብቶ ትንሽ መንገዱን አቋርጦ ትልቅ የሞት መንገድ ይጀምራል ። ፋኖ ፋኖ እየተባለ ሲዘፈንም የመለከት ድምፅ መቋቋም አቅቶት ዘሎ ጦር ሜዳ የሚገባ ፣ ቦምብ በደረቴ አመክናለሁ ብሎ እንዲሁ የሚቀር አለ ። እደሰታለሁ ብሎ አስቦ ከዝሙት ሞትን ያጨደ ሰው አለ ። እገሌ ከሌለ እኔም አልኖርም በማለት በኀዘን ራሱን ሰርስሮ ያነቀና የገደለ ብዙ ነው ። መኖር እየፈለገ የተፈጥሮ ግዳጅ ሆኖበት የሚሞት እልፍ ነው ። መኖር ሰልችቶት የመቀበሪያ ሳጥኑን ገዝቶ የሚጠብቅ ፣ የመቀበሪያ ፉካውን አሳምሮ የሚኖር አያሌ ነው ። ብዙ ዓይነት ሟቾች ቢኖሩም ሞት ግን አንድ ነው ። ሞት ሞት ቢሆንም ትርጉም የሚሰጠው አኗኗሩና አሟሟቱ ነው ። የሌላውን ሞት ቤዛ ላይሆን የወሰደ ፣ አድናለሁ ብሎ የሞተ ፣ በወኔ ያሸለበ ፣ በሞኝነት የወደቀ ፣ በግድ ያለፈ ፣ በቃኝ ብሎ ያንቀላፋ አለ ። የክርስቶስ ሞት ግን ከዚህ ልዩ ነው ። ወድዶ ፈቅዶ ሙቷልና በተባራሪ ከሞተው ልዩ ነው ። በስሜት ሳይሆን በዓላማ የሞተ ነው ። በወኔ ሳይሆን በፍቅር የታረደ ነው ። በሞኝነት ሳይሆን በዘላለም ጥበብ የተሠዋ ነው ። በግድ ሳይሆን ሊሞትልን በሥጋ የመጣ ነው ። መኖርን ሰልችቶ ሳይሆን የሚያሳሳ ዕድሜውን ለሰው የሰጠ ነው ።
ዓለም በበሽታ ፍርሃት ተውጧል ። እሞታለሁ ብሎ ተሸብሯል ። በካንሰርና በመኪና አደጋ በየቀኑ ብዙ ሕዝብ ይሞታል ። እሞታለሁ እያሉ መሞት ግን ከባድ ነው ። ሞትን ሺህ ጊዜ ማየት ብርቱ ነው ። በዚህ ሰዓት ለፍቅር ቦታ ላይኖረን ፣ ከሞት ድምፅ በላይ የፍቅርን ቅላፄ ሰምተን ሌሎችን ለመውደድ እንቸገራለን ። ጌታችን ግን ስለ እኛ ሊሞት በተቃረበበት ሰዓት የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው ። ከፋሲካው በዓል በፊት ከምሳሌውም ከአማናዊውም ፋሲካ በፊት ደቀ መዛሙርቱን ወደዳቸው ። ከመሥዋዕትነት በፊት ፍቅር ይቀድማል ፣ ብሉይና ሐዲስን ከማመስጠር በፊትም መውደድ ይቀድማል ። ለማንወደው ወገን ብንሞት እንኳ እያፌዝን ነው ። ፍቅር የሌለበት መሥዋዕትነት አያርግም ። በጌታችን ፍቅር ውስጥ ሦስት ነገሮችን ማውጣት እንችላለን፡-
1-  አስቀድሞ የወደደ ፤
2-  ዛሬም የወደደ ፤
3-  ለዘላለም የሚወድ ፤
ዛሬ በጣም የምንወዳቸው ሰዎች ትላንት በጣም እንጠላቸው ነበር ። ትላንት በጣም የምንወዳቸውን ሰዎች ደግሞ ዛሬ ጠልተናቸዋል ። የእኛ ፍቅር ትላንት ቢኖር ዛሬ ትዝታ ፣ ዛሬ ቢኖር ነገ ላይ ታሪክ ነው ። እርሱ ግን አስቀድሞ የወደደ ነው ። የሚወዳቸውን የወደደ ሳይሆን የወደዳቸውን የወደደ ነው ። ዛሬ የምንወዳቸው ሰዎችን አእምሮአችንን አስቀምጠን ልናውቃቸው አንፈቅድም ፣ ፈቃዳችንን አስቀምጠን ልንወስን አልቻልንም ። የዛሬው ፍቅራችን መሠረቱ ስሜት ነው ። ስሜት የጀበና ቱግታ ነው ። በትንሽ ውኃ ይበርዳል ፣ ወይም የተሸከመውን ሸክላ አቆሽሾ ፣ ራሱም አልቆ ይበርዳል ። የተሸከማቸውን የሚያቆሽሹ ዛሬ ማነስ ፣ ነገ ማለቅ ይከተላቸዋል ። ክርስቶስ ግን የወደደን አውቆን ነው ። አውቆን ብቻ ሳይሆን አውቆልንም ነው ። እኔ ልሙትለት እርሱ ይኑር ብሎ የወደደን ነው ። ነገ የምንወዳቸውን አናውቅም ። ይህች ጀምበር ብዙ ወዳጆችን ታሳጣናለች ። ክርስቶስ ግን ባልተጀመረ ነገ ፣ ባልታየ ነገ የሚወደን ነው ። ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን ትላንት ይወዳቸው ነበር ። እንደ ሕፃን ሁለንተናቸውን ግልጥ ባደረጉበት ዘመን ፣ ሰማይን እየነገራቸው የእስራኤል መንግሥት በሚናፍቃቸው ትላንት ፣ የሚናገረውን ሳይሆን የሚመኙትን በሚሰሙበት ወራት ይወዳቸው ነበር ። ዛሬም በምሴተ ሐሙስ ግራ ተጋብተው ፣ ከይሁዳ ጋር ለመቍረብ ተሰናድተው ፣ ከአሥራ ሁለት ቍጥር ውስጥ አንድ ከዳተኛ አፍርተው ክርስቶስ ይወዳቸው ነበር ። ነገ ሁሉም በቆሙበት አቅጣጫ ቀኝ ወደ ኋላ ዙር ብለው ሲሮጡ ፣ ጴጥሮስ ሲክድ ፣ ይሁዳ ሲሸጥ ፣ ጴጥሮስ ሲጸጸት ፣ ይሁዳ ሲብስበት ፣ አንድ ቀን እንኳ ከክርስቶስ ጋር መቆም ሲያቅታቸው ፣ ከአሥራ አንድ ወዳጅ ዮሐንስ ብቻ እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ ሲጓዝ  ጌታ ይወዳቸው ነበር ። የትላንትን አለማወቅ ፣ የዛሬን ስሜት ፣ የነገን ፈቃድ የታገሠና እንደገና የሰበሰባቸው ይህ ፍቅር ነው ።
መሞቱን ያወቀ ሰው ሊወድ ይቸገራል ። ዘመኑን መራራ ያደረጉትን ሰዎች ሞት ሳያይ በመሄዱ ያዝናል ። መሞት ብቻውን አፍቃሪ አያደርግም ። ወደ አብ እንደምንሄድ ስናውቅ እንዳፈቀርን እንሞታለን ። ዓለም ከነሣችን የአብ ፍቅር የሚሰጠን ይበልጣልና ። ክርስቶስ እንኳ በዚህ ዓለም የነበሩት ወገኖች ነበሩ ። ሁላችንም በዚህ ዓለም ላይ ጥሩ ወገኖች አሉን ፤ ፍጹም ወገኖች ግን የሉንም ። ሞት ወደ አብ የምንሄድበት ብርሃናዊ መንገድ የሆነው ከክርስቶስ ቤዛነት በኋላ ነው ። ጌታችንም በመስቀል ላይ የተናገረው የመጨረሻው ጩኸት፡- አባት ሆይ ፥ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” የሚለው ነው ። /ሉቃ. 23፡46/ ። እስከዚህ ቀን ድረስ ሞት ነፍስ በዲያብሎስ እጅ የምትወድቅበት ነበረ ። ጌታችን ይህን አዋጅ በታላቅ ጩኸት ተናገረ ። የነፍስ አድራሻዋ በአፍቃሪው አብ እጅ ሆነ ።
የወደድናቸውን እስከ መጨረሻ መውደድ መልካም ነው ። ፍቅር ፌርማታ የለውምና ባንወርድ ጥሩ ነው ። አመስግነን ባንራገም ፣ የፍቅር ጦማር ጽፈን የሞት ደብዳቤ ባንቸከችክ መልካም ነው ። ከፍቅሩ ጋር የሚሞት ክቡር ነው ። ፍቅር ርቆን ልከኛ ጠብ እንደ ጽድቅ በሚታይበት በዛሬው ዘመን እስከ መጨረሻው መውደድን ከክርስቶስ መማር አለብን ። የተሰጠን ዕድሜ እንኳን ለጠብ ለፍቅር አይበቃም ። ይህን ጥቅስ በማንበብም በመዘከርም ባለንበት በዚህ ጊዜ እስከ መጨረሻ መውደድን ለልባችን መንገር አለብን ።
እስከ መጨረሻው ድረስ የወደደን አንድ አለ ። ከሰው ወገን የነገ ወዳጄ እገሌ ነው ብለን በእርግጠኝነት መናገር አንችልም ። እስከ ነገ የሚወደን አምላክ  ግን አለ ።
ጸሎት
ጌታዬ ሆይ ያንተ ፍቅር ምንኛ ውብ ነው ። አይቼ ልተነትነው ፣ ተመልክቼ ልጠግበው በፍጹም አልችልም ። ከሚሸጥህ ጋር እንጀራ የሚቆርስ ፣ ከሚክድህ ጋር ገበታ የሚቀመጥ ያንተ ፍቅር እንዴት ድንቅ ነው ። ድሀና ምስኪንን የማይጠየፍ ፣ ሰውን በልብስ የማይለካ ፣ የትላንት አለማወቅን ፣ የዛሬ ስሜትን ፣ የነገ ክዳትን በይቅርታ የሚያይ ያንተ ፍቅር ሰማያዊ ነው ። ኦ ያንተ ፍቅር ጠፍቼ የተገኘሁበት ፣ በትከሻ ላይ የተሳፈርኩበት ፣ የሞት ሸለቆን የተሻገርኩበት ነው ። ፍቅርህ ማልዶ አዲስ ነው ። የማይለመድ አዲስነት ነው ። ራሱን ለጠላ ዋስ ፣ ሰው ገሸሽ ላለው መደበቂያ ነው ። ኦ ያንተ ፍቅር እንደገና የተወደድኩበት እውነት ነው ። ይህ ፍቅርህ ይቆጣጠረኝ ። ለዓለም ሳይሆን ላንተ መገበር ይሁንልኝ ። እስከ መጨረሻው መውደድን አስተምረኝ ። ሳልደርስ ወረት አያውርደኝ ። በታዳጊው ፍቅርህ ለዘላለሙ አሜን ።
የመስቀሉ ገጽ 1
ሚያዝያ 7 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም