መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የዕለት መና » እሾሁን ሳይሆን ጽጌረዳውን

የትምህርቱ ርዕስ | እሾሁን ሳይሆን ጽጌረዳውን

 
“እግዚአብሔር ፥ ቅዱሳንን ስላገለገላችሁ እስከ አሁንም ስለምታገለግሉአቸው ፥ ያደረጋችሁትን ሥራ ለስሙም ያሳያችሁትን ፍቅር ይረሳ ዘንድ ዓመፀኛ አይደለምና ።” ዕብ. 6፡10
በዮዲት ጉዲት አርባ ዓመት የወደመውን የክርስትና ቅርስ ፣ የታረዱትን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደምናስታውስ ሁሉ በአባ ፍሬምናጦስ የተቋቋመውን የኢትዮጵያ የስብከተ ወንጌል አዝመራም ማሰብ ይገባናል ። በግራኝ መሐመድ አሥራ አምስት ዓመት የተደረገውን ጨካኝ ወረራ እንደምናስብ ሁሉ በጎንደር ዘመነ መንግሥትም የተጻፉትን መጻሕፍት ማሰብ አለብን ። በግብጻውያን የመንበር ጥገኛ ሁነን የማቀቅንበትን ጊዜ እንደምናስብ ሁሉ በተሰዓቱ ቅዱሳን ከፍጻሜ የደረሰውን የቅዱሳት መጻሕፍት ትርጉም ፣ የተሰበከውን ወንጌል ማሰብ አለብን ። በአድዋ ጦርነት የሞቱትን ብቻ ሳይሆን የተገኘውን ፍሬ ፣ በማይጨው ጦርነት የከዱትን ብቻ ሳይሆን ታምነው የቆሙትን ማሰብ አለብን ። ማሰብ የብዙ ነገሮች መነሻ ነው ። የፍቅርም የጠብም ፣ የሰርግም የጦርነትም መነሻ ማሰብ ነው ። ታሪክን ወደኋላ መልሰን ማስተካከል ባንችልም ታሪክን እንማርበታለን ። ታሪክ በክፋቱም በደግነቱን አስተማሪ ነው ። የታሪክ ትርፉም ትምህርቱ እንጂ ያ ጊዜ አሁን የምንመልሰው መሆኑ አይደለም ። “ከታሪክ የማይማር ስህተትን ለመድገም የተፈረደበት ነው” የሚባለው ለዚህ ነው ።
በጎ የሠሩትን ማሰብ አለብን ። አለማሰብ ብዙ እየጎዳን ነው ። “የሞተን አትርሳ ፣ የወደቀን አንሣ” ይባላል ። የሞተን ማንሣት አንችልም ፣ የወደቀን ማውሳት ጥቅም የለውም ። የሞተን ማውሳት ፣ የወደቀን ማንሣት ግን በረከት አለው ። የሞተን አለመርሳት ትምህርቱ ለትውልድ ሰፊ ስለሆነ ነው ። መልካም ሥራም ከመቃብር በላይ እንደሚኖር የሚያስገነዝብ ነው ። እኔም ስሞት እንዲህ እታሰባለሁ ብሎ ሰውን ለመልካም ነገር የሚያነሣሣ ነው ። “የምትሄድበት እንዳይጠፋህ የመጣህበትን አትርሳ” ይባላል ። ድሆች ባለጠጋ ሲሆኑ መልሰው ድሆችን ያስለቅሳሉ ። ይህ የመጡበትን መርሳት ነው ። ስለ ሕዝብ ጭቆና አውርተው ሥልጣን ላይ የወጡ መልሰው ጨቋኝ  ይሆናሉ ። ይህ የመጡበትን መርሳት ነው ። የመጡበትን መርሳት የሚሄዱበትን ያስጠፋል ። ስለዚህ ደም መቃባት ፣ ሰውን ማስለቀስ ይጀመራል ። ፍጻሜውም ውርደትና መከራ ይሆናል ። መርሳት ከድሀ ጎጆ እስከ ንጉሥ እልፍኝ ዋጋ ያስከፍላል ። “ተው አትርሳ ፣ ተሠርቶልሃል የእሳት ገሳ” ይባላል ። ሊጠብቀን የሚችለውን እንቅፋት ማሰብ ለመጠንቀቅ ያግዛል ። ከዚያ ሁሉ በላይ በነፍስ እንደምንጠየቅ ማሰብ በዘመናችን ሁሉ በቅዱስ ፍርሃት እንድንንቀሳቀስ ያደርጋል ። “ያለህበትን ለማወቅ የመጣህበትን አትርሳ” የሚለውም ድንቅ ንግግር ነው ። እየበላን ፣ እየጠጣን ፣ እየሠራን የምናማርረው ትላንት ይህ ሁሉ እንዳልነበረን ስለምንረሳ ነው ። ዛሬ በእጃችን ብዙ ነገር ካለ ትላንት አልነበረም ማለት ነው ። ዛሬ በእጃችን ምንም ከሌለ ነገ ይኖረናል ማለት ነው ። “የወጣህበትን አትርሳ” ይባላል ። የወጡበትን መሰላል መገፍተር ተሰቅሎ መቅረት ነው ። የወጡበት መሰላል ለመውረድም ያስፈልጋል ።
ክፉ ፣ ክፉ ነገሮችን አልረሳ እያልን እንቸገራለን ። በሕይወታችንም የሠራናቸው ብዙ መልካም ነገሮችን ትተን ያጠፋናቸው ነገሮች ላይ እንተክዛለን ። መልካሙን ስናስብ እንደገና እንነቃቃለን ። በትላንት የታሪክ ስህተት ላይ መቆየት አመድ ላይ መንከባለል ነው ። ከመቆሸሽ ውጭ ምንም ጥቅም የለውም ። ታሪክ የሚመዘነው በተሠራበት ዘመን የእውቀት ልክ ነው ። ማንም ስለ ታሪክ ተጠያቂ መሆን የለበትም ። እኛ ትላንት ያልነበርን ፣ ነገ የማንኖር የዛሬ ሰዎች ነን ። ዛሬ ልንተወዉ ሲገባን ባልተውነው ፣ ልናደርገው ሲገባን ባላደረግነው ነገር እንጠየቃለን ። እግዚአብሔር አምላክ ግን ያለፈውን ዘመን መልካም ነገር የሚያስታውስ አምላክ ነው ። ስለ አብርሃም እንጂ በአብርሃም ዘመን ስለነበረው ዓመፀኛ ንጉሥ ዘመን ተሻግሮ አይናገርም ። ስለ ሙሴ እንጂ ስለ ፈርዖን ተናግሮ አያውቅም ። ስለ ዳዊት እንጂ ዳዊትን ስላስጨነቁት ሰዎች ከዘመናት በኋላ አልተናገረም ። ጴጥሮስና ጳውሎስን የገደለ ፣ ክርስቲያኖችን በጣም ያስጨነቀው ኔሮን ቄሣር ስሙ እንኳ በመጽሐፍ ቅዱስ የለም ። የእግዚአብሔር መዝገብ ዘመናትን ተሻግሮ የሚያነሣው መልካሞችን ነው ። ክፉዎችን ለማስተማሪያነት ቢያነሣ እንኳ ለወቀሳ ግን ጊዜው አልፏል ። በፍርድ ክልል ውስጥ ያለ አይወቀስም ። ፍርዱንም የጨረሰ አይከሰስም ።
በእናቱ ሞት ላይ “እናቴ ሀብታሟ” እያለ ልጅየው ያለቅሳል ። አንዱ ሰውም “የእናትህን ሀብታምነት የምናውቀው የተዝካሯ ዕለት ነው” አለው ይባላል ። ይህ የሲዳምኛ ምሳሌያዊ አነጋገር ነው ። እናቴ ሀብታሟ እያሉ ማልቀስ ቀላል ነው ። ሀብቷ ግን መታሰቢያዋን ካላጠፋ እውነተኛ ነው ። አገር እናት ናት ። አገሬ ሀብታሟ እያልን ማልቀስ ይቻላል ። የሀብታምነቷ ምልክት ግን በጎ የሠሩትን ስታስብ ነው ። ታሪክ ያላቸው ተቀብረውባት ፣ ልብ ወለድ ታሪክ ያጻፉ ከነገሡባት ሀብታምነቷ ምን ላይ ነው ? ሀብታም የሚባሉ አገሮች ሁሉ ያለፈውን ቅርስና ያለፉትን ባለውለታዎች ያስባሉ ። የባለጠጋ አገር ምልክቱ ለትላንት እውቅና ለዛሬ ፣ የመኖር ነጻነት ሲሰጥ ነው ። ትልቁና እውነተኛው ሀብት የሰዎችን ውለታ ፣ ያለፉትን ባለታሪኮች አለመርሳት ላይ ያረፈ ነው ። ቤተ ክርስቲያን የቅዱስነት መዐርግ መስጠት ስታበዛ የሃይማኖት ተጋዳዮች እየበዙ ይመጣሉ ። አገር የደከሙላትን ማሰብ ስትጀምር ላገር የሚደክሙ ብዙዎች ይበዛሉ ። “አገሬ ለሠራላት አትሆንም” የሚል እሳቤ በትውልድ ላይ ካረፈ ያው ትውልድ አገርን ያጠፋታል ።
ስለ እግዚአብሔር የተነገው ግን ከዚህ ልዩ ነው፡- “እግዚአብሔር ፥ ቅዱሳንን ስላገለገላችሁ እስከ አሁንም ስለምታገለግሉአቸው ፥ ያደረጋችሁትን ሥራ ለስሙም ያሳያችሁትን ፍቅር ይረሳ ዘንድ ዓመፀኛ አይደለምና ።”
የእግዚአብሔር ሰዎችን መቀበል እግዚአብሔርን መቀበል ነው ። አምባሳደሩን መቀበል መንግሥቱን መቀበል ነውና ። ስላገለገላችሁ ይልና ስለምታገለግሉአቸውም ይላል ። የቆመ መልካምነት ሳይሆን አሁንም እየቀጠለ ያለ መልካምነት ነው ። መልካምነት “ነበር” የሚል ቃል አይስማማውም ። መልካምነት እንደ እስትንፋስ የማይቆም ነገር ነው ። ለቅዱሳን መልካም ማድረግ ለእግዚአብሔር ስም ክብር መስጠት ነው ። ቅዱሱ ሲጣልና ሲረሳ የማያምነው ዓለም እግዚአብሔርን ማለት ምን ጥቅም አለው ? እያለ ይዘባበታል ። የእግዚአብሔር ስም እንዳይሰደብ የምናደርገው ክርስቲያኖች እንዳይወድቁ በመደገፍ ነው ። ለእግዚአብሔር ሰዎች መልካም ስናደርግ ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር እየገለጥን ነው ። እግዚአብሔርን የት አግኝተን እንጋብዘዋለን ? እርሱ ከአገልጋዮቹ ጋር አለ ። እግዚአብሔር የአንድ ብርጭቆ ውኃን ዋጋ የማይረሳ ታማኝ አምላክ ነው ።
ውለታን መርሳት ዓመፀኝነት ነው ። ዓመፀኛ ገልብጦ የሚሄድ ነው ። ውለታን የሚረሳም ከፊቱ ያለውን ገበታ የሚደፋ ነው ። ሌላውን የሚረሳ እርሱም ይረሳልና ። ታሪክን የሚያጠፋ ታሪኩ ይጠፋል ። ትውልድን የሚያጠፋ ልጆቹን ያጠፋል ። ድሆችን የሚያጠፋ ዘመዶቹን ያጠፋል ። ነገ የሚታወስ ሰው ፣ የትላንቶቹን የሚያስብ ሰው ነው ። ያስተማሩንን ፣ ያገለገሉንን ፣ ያጽናኑንን ፣ አንድ ቀንም “አይዞአችሁ” ያሉንን ፣ አንደበት ሁነው የተሟገቱልንን ፣ ክንድ ሁነው የመከቱልንን አንረሳ ። የምናመልከው አምላክ የማይረሳ ነውና ። ከሰው ምንም አልተቀበልኩም ማለት በዓለም ላይ ትልቅ ውሸት ነው ። ደምሳሽ ትውልድ እንዳንሆን መጠንቀቅ ያስፈልገናል ። የትላንቱን ክፉ ሳይሆን መልካሙን ማሰብ ይገባናል ። ቅዱሳንን ማሰብ ብቻ ሳይሆን መሆንም ያስፈልገናል ። የአንድ አገር ታላቅነት የሚለካው የወደቁላትን ስታከብር ነው ። ክብር የሌለው አገር አያድግም ።
የዓይናችን ብርሃን አንተው ነህ ። ያላንተ ዓይን ጌጥ ብቻ ነው ። የጆሮአችንም የምሥራች የእግዚአብሔር ልጅ ሆይ አንተ ነህ ። ስለ ጽጌረዳ እሾህ ተናግረን አናውቅም ፣ ብዙ እሾሁን ረስተን አንዷን ጽጌረዳ እንወዳታለን ። የሰዎችን ብዙ ጥፋታቸውን ትተን አንድ መልካምነታቸውን እንድናጎላ እባክህ እርዳን ። ምጡን ረስተን ልጁን እንድናነሣ አግዘን ። ምጡን አልረሳ ብለን በምጡ የተወለዱትን እየረሳን ነውና ። መንፈሳዊ ዓይን ስጠን ። በፊትህ የጸለዩልንን ፣ በጎ ያደረጉልንን ፣ በክፉ ቀን ያልከፉብንን ባርክልን ። ይህ ቀንም ውለታ የማሰቢያና የማመስገኛ ቀን ይሁንልን ። ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 29
ግንቦት 29 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም