ሙቀቱ ጨመረ ከማለት አንድ ዛፍ ተክያለሁ ወይ ? ብሎ መጠየቅ መልካም ነው ። ተፈጥሮ ሲጠብቁት ይጠብቃል ። ያለ እርሱ ማማር የለምና ክረምቱ አስጠላ አትበሉ ። ለማኙን ስታዩ ሠርቶ አይበላም ወይ ? አትበሉ ፣ የሚሠራውን አላቀረባችሁምና ። ዳኛው በቅን አይፈርድም ወይ ? አትበሉ ፣ ደግ ምስክር አልሆናችሁምና ። አትዋሹ ፣ ዳግም የሚያምናችሁ አታገኙምና ። አትኩሮት ለማግኘት ሳያማችሁ አመመኝ አትበሉ ፣ የታመማችሁ ቀን ልማዱ ነው ትባላላችሁና ። ሠራተኛው በጥራት አልሠራውም ብላችሁ አትዘኑ ፣ እርሱን የቀጠራችሁት ስለማትችሉ ነውና ። የቤት ወጪ እንዴት አለቀ ? አትበሉ የኪሳቸው ገንዘብ እንዳለቀው ነውና ። ጓደኛችሁን መሥዋዕትነት ከፍላችሁ አጠገቡ ቁሙ ፣ ፍቅርን የሚያኖረው የከፈሉለት ዋጋ ነውና ። በቀላሉ አንድን ነገር ለማግኘት አትሹ ፣ ይቀልባችኋልና ። ነጻ ስጦታን አትናቁ ፣ መግዛት አትችሉምና ።
በሁሉ ላይ አስተያየት ለመስጠት አትከጅሉ ፣ ስለ ሁሉም ነገር አታውቁምና ። ቀጠሮ ማክበርን አትርሱ ፣ የሰው ዕድሜ እየጨረሳችሁ ነውና ። ዕድሜ ሲገፋ እንኳን የሚያፈቅር የሚጣላም ይጠፋልና ወዳጃችሁን አጥብቃችሁ ያዙ ። አስታርቃለሁ ብላችሁ እንዳታጣሉ የሰማችሁትን ክፉ ነገር አታውሩ ። የማይወዱአችሁ ጋር እልህ አትጋቡ ፣ የሚወዱአችሁ አሉና ። ቆዳችሁን አታዋድዱ ፣ እኔ ተፈላጊ ነኝ ብላችሁ አታስቡ ፤ ሁሉ ይጠላችኋልና ። ሳላችሁ በሥርዓት ስጡ ፣ ከሌላችሁ አትሰጡምና ። እገሌ ለምን አልሰጠም ? አትበሉ ፣ የምታዝዙት በራሳችሁ ኪስ ነውና ።
የሚያስተዛዝን ሳለ ኀዘናችሁን ግለጡ ፣ የብቻ ኀዘን አይወጣምና ። ለንዋይ ብላችሁ ወዳጃችሁን አትለውጡ ፣ ገንዘቡ ሲገኝ ወዳጅ ይናፍቃልና ።
ከብራችሁ ፣ ደምቃችሁ ዋሉ !
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 25 ቀን 2013 ዓ.ም.
እውነት 5
ለልባችሁ የቀረላችሁን አሳብ እስቲ ግለጡ ። እግዚአብሔር ሰላሙን ይስጣችሁ !