መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እናትነት

የትምህርቱ ርዕስ | እናትነት

 

እስር ያለው አእምሮ ላይ ነው ። ሰው በቤተ መንግሥትም ቢታሰር እስር ከባድ ነው ። ነጻነትን ማጣት በዚህ ዓለም ትልቁ ቅጣት ነው ። ሰዎች በብሕትውና አርባ ዓመት ከአንድ ጠባብ በኣት ላይወጡ ይችላሉ ። የአገር ድንበር የሚጠብቅ ወታደር በአንድ ምሽግ ለብዙ ጊዜያት ሊያሳልፍ ይችላል ። በሕግም ይሁን በእገታ እስር ከባድ ሁነት ነው ። እኔን አያገኘኝም የምንለው አይደለም ። ክፉ ስለ ሠራን ብቻ ሳይሆን እንደ ዮሴፍ ከክፋት ጋር አልተባበርም በማለታችንም ወኅኒ ልንወርድ እንችላለን ። በእስር ቤት ከነገሥታት እስከ ሎሌዎች ይገኛሉ ። በጥንቱ የነገሥታት ልጆች የሚታሰሩበት “አምባ” ተብሎ የሚጠራው ለአገራችን የእስር ቤት ታሪክ እንደ መነሻ ሁኖ የሚጠቀስ ነበረ ። የእስር ቤት ኃላፊዎች፡- “ለጥንቱ እስር ቤት ፣ ከርቸሌ ይባል ነበር ፣ አሁን ግን ማረሚያ ቤት ብለነዋል ። ሰው የሚማርበት ስፍራ ነው” ይላሉ ። ከማጎር የተሻለ ትምህርት መኖሩ ግን ያጠራጥረኛል ። ጌታ የታሰረን ጠይቁ ማለቱ እጅግ ትክክል ነው ። እስረኞችን ለማስተማርም ለመርዳትም በምሮጥበት ዘመን እስረኛ ማለት ማን እንደሆነ ፣ እስርም ምን ማለት እንደሆነ አውቄአለሁ ። እኔ በምሯሯጥበት ዘመን በአንድ ማረሚያ ቤት ሁለት ጠቅላይ ሚኒስትሮች ታስረው አይቻለሁ ። የደርግ ዘመን ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩትን ሰውም ደጋግሜ አነጋግሬአለሁ ። ለይቅርታ መጽሐፌም ደስታቸውን ለመግለጥ ፣ ለወጠኝ የሚሉትን ሌላ መጽሐፍ እንዳነብ ጋብዘውኛል ። እነዚህን ባለሥልጣናት በምጎበኝበት ቀናት ሁሉ እስር ከባድ እንደሆነ ተረድቻለሁ ። ብዙ የደርግ ባለሥልጣናትም ንስሐ ገብተው ከእግዚአብሔር ጋር ታርቀው እስር ቤቱ ገዳም ሲሆንላቸውም አይቻለሁ ፣ ተሳትፌአለሁ ።

ከሳምንት በፊት አንድ ወዳጄ ታስሮ እርሱን ለመጠየቅ ሄድኩኝ ። የጥየቃ ሰዓቱ ሃያ ደቂቃ ይቀረዋልና እግሬ ወደ ኋላ ቀረት እያለ ወደ እስር ቤቱ ደጃፍ ሲቃረብ አንድ እጅግ የጎሰቆሉ ፣ የኮሰመኑ ፣ ያለቁ ፣ ኑሮ እብድ ያስመሰላቸው ፣ ችግር አናታቸው ላይ ወጥቶ ያሰከራቸው እናት ላይ ዓይኔ አረፈ ። የተቀመጡት ፖሊስ አጠገብ ነው ። በአጠገባቸው ቀድመው የመጡ ሦስት የሚሆኑ ዘመናዊ ወጣቶች አሉ ። በእነርሱ መሐል የተቀመጡት እናት ግን ጉስቁልናቸው ደምቆ ይታያል ። ጥሩ የለበሰ ዓይን ውስጥ እንደሚገባ እኒህ እናትም ጉስቁልናቸው ከሩቅ ይታያል ። ብዙ ድሆችን ያየሁ ይመስለኛል ፣ የእኒህ እናት ጉስቁልና ግን ልዩ ሆነብኝ ። አንድ ችግር ውስጥ እንዳሉ ግን ተጠራጠርሁ ። ችግር ቁመናቸውን አሳጥሮታል ፣ በተፈጥሮም አጭር ናቸው ። ድህነት ደግሞ በብረት ዘነዘና ወደ ታች እየመታ መሬት ቀብሯቸዋል ። ሰውነታቸው አልቋል ። ሠላሳ ኪሎ የሚመዝን ሰው አይቼ አላውቅም ፣ ከአርባ ኪሎ እንደማይበልጡ ግን እርግጠኛ ነኝ ። አንጀታቸው ወደ ውስጥ ስለሰመጠ እጃቸው ሸለቆውን ለማግኘት ወደ ውስጥ ገብቷል ። የልብሳቸው አዳፋ የጎዳና ልጆችም እንደዚህ ሲቆሽሹ አላየሁም ። የፊታቸው ትካዜ የልባቸውን ስብራት በደንብ ይገልጣል ። ነጠላ ልብስም የላቸውም ። አሮጊትነቱ የሚፈቅደውን አለባበስ ድህነት የሚባለው ባለጌ ገፏቸዋል ። ወዲያው ላያቸው ሰው ይህችን ዓለም ከመርገም ውጭ ምንም ሊል አይችልም ። አብሮኝ የነበረው መንፈሳዊ ልጄ እንዳያቸው ኪሱን ዳበሰ ። “ቆይ እስቲ” ስለው “ምን ቆይ ይባላል” ብሎ ከመቶ የዘለቀ ከሁለት መቶ የተጠጋጋ ብር ሰጣቸው ። እርሳቸውም ተቀብለው፡- “ክፉ አይንካህ ፣ እንደ እኔ ከመሆን ይሰውርህ” ብለው በተሰላቸ መንፈስ መረቁት ። ንግግር እንዳስጠላቸው ግልጽ ነው ። 

ፖሊሱን ግን፡- “ኃላፊው ይኖራል  ልጄ የት እንዳለ እጠይቀው ነበር ፤ ያውቀኛል ይነግረኝ ነበር” አሉት ። ፖሊሱም “የለም” ብሎ አጭር መልስ ሰጣቸው ። ፖሊሱ ጫማው ጫፍ ላይ ያለውን ጭቃ በእስፖጅ ለመጥረግ ወደ እጅ መታጠቢያ ኮረና ወዳመጣው መታጠቢያ ሄደ ። እኛም ሰዓቱ እስኪደርስ አጠገባቸው ተቀመጥን ። “ልጅዎ ምን አድርጎ ነው ” ስንላቸው “ከተከራይ ጋር ተጣልቶ ነው ፣ ያመዋል ሕመሙ ሲነሣበት ቢጣላቸው አሳሰሩት” አሉ ። ተከራይ ሲሉ እኒህ ሴት ቤት ያከራያሉ ማለት ነው ብለን ንቅት አልን ። በግርምት “ያከራያሉ ወይ?” ብለን ጠየቅናቸው “አዎ” ብለው በተሰላቸ ድምፅ መለሱልን ። … ምን ዓይነት ቤት ይሆን ? እንጃ ።

ወደ ውስጥ ስንገባ ልጃቸው ዘመድ መጠየቂያው ላይ ቆሟል ። ልጁ እርሳቸውን ይመስላል ። የድሮ መልካቸው እርሱ ላይ ይታያል ። ያ ልጅ ቀጭን ፣ አጠር ያለ ፣ ንቁ ፣ ቆንጆ ፣ አለባበሱ ዲያስፖራ የሚመስል ቁምጣ የለበሰ ነው ። ፊቱ ግን እንደ ድሀ ልብስ በየአቅጣጫው ተሰፋፍቷል ። ግንባሩ ላይ አንድ ስፌት ወደ ጎን አለ ፣ አፍንጫው ላይ ሌላ ስፌት ወደ ታች አለ ። አገጩ ላይ አሁን ወደ ጎን የተሰፋ ይታያል …። እርሳቸውም፡- “አለህ ልጄ” ብለው በደከመ ድምፅ ጠየቁት ። እርሳቸው የሚያውቁትና ሊያውቁት የሚፈልጉት ነገር ሕመሙ ሲነሣበት ቍጠኛ ይሆናል ፣ ከሰው ጋር ሲጣላ ይታሰራል ብለው ነው ። አይ የእናት አንጀት ። ልክ ሲያያቸው አፈጠጠባቸው ። እርሳቸውም አንገታቸውን ሰበር አደረጉ ። የትዝብት ሳቅ ሳቀባቸው ። የጭካኔ ፈገግታ አየሁበት ። “ምን ልትሠሪ መጣሽ ?” ብሎ አፈጠጠባቸው ። እርሳቸውም ወዲያው ጨመቱ ። “አልነገርኩሽ ?” አላቸው ። በዚህ ጊዜ ሆዳቸው ውስጥ አጥብቀው ይዘዋት የነበረውን ሁለት ሽልጦ እንካ ብለው ሰጡት ። እቤት የጋገሯት ትመስላለች ። “አምጪ” ብሎ ከተቀበለ በኋላ ሲያፈጥባቸው ድምፁንም ፣ የጭካኔ ፊቱንም ለማየት ጊዜም አልነበራቸውም ። ያቺን ደጅ ላይ የተቀበሉአትን ገንዘብ ሙሉ በሙሉ ሰጡት ። እርሱም የመንጠቅ ያህል ተቀበላቸው ። በዚህ ጊዜ ውስጤ እሳት ነደደ ። “በሥርዓት አነጋግራቸው ፤ ስላንተ ተጨንቀው ደጅ ላይ ተቀምጠው ነበር ። ሥርዓት ይዘህ አናግራቸው” አልኩት ። አጠገቡ ያለውን ወዳጄን ረስቼዋለሁ ። ወዳጄም እስር ላይ ነውና ይህን  ልጅ አደገኛነቱን ያወቀ ይመስል ገርመም አደረገኝ ። እኔ ግን ትዝም አላለኝም ። 

በዚህ ጊዜ ደንገጥ አለና፡- “እሺ ዋልሽ ወይ ?” ብሎ አናገራቸው ። መቼም ዱርዬ አካባቢውን በመምሰል የተካነ ነው ። “እነ እገሌ ምን አሉ ?” አላቸው ። አጭር መልስ ሰጡ ። “የቤት ኪራዩ ደርሷል ተቀበልሻቸው ወይ ?” አላቸው ። እርሳቸውም፡- “አልተቀበልኩም ደርሷል እንዴ ?” አሉት ። እርሱም በዓይኑ እያወራ “ተቀበያቸው” አላቸው ። መልእክቱ ቶሎ ይዘሽ ነይ ማለቱ ነው ። እርሳቸውም “እሺ” ብለው አንገታቸውን ደፍተው ሲወጡ እኔም ቶሎ ጠይቄ ተከተልኳቸው ። …

እኔም እኒህን ሴት በቁም የቀበራቸው ፣ ተንቀሳቃሽ ሬሳ ያደረጋቸው ፣ እንደ ነቀዝ በልቶ የጨረሳቸው ይህ ልጅ እንደሆነ ተገነዘብኩ ። አይፈልጋቸውም ፣ እርሳቸው ግን ባይፈልጋቸውም ይፈልጉታል ። እየወጣን እያለን፡- “እንዲህ አይሁኑ ፣ ልጅም ራስን ሲጥሉ አይወድም ።  ለራስዎ አስቡ” አልኳቸው ። “አይ ሁሉም ሰው እንዲህ እያለ ይመክረኛል ፣ አቃተኝ እንጂ” አሉ ። … እርሳቸውም ወደ መንገዳቸው ሄዱ ፣ እኔም አብረውኝ ከመጡት ወገኖቼ ጋር እያዘንኩ ወደ ቤቴ ተመለስኩ ። ከጠያቂው እስረኛው የሚያምርበትን አገር እያሰብኩ ወደ ቤቴ መጣሁ ።

ያ ልጅ አይፈልጋቸውም ፣ እርሳቸው ግን ይፈልጉታል ። እግዚአብሔርም “ላልፈለጉኝ ተገለጥሁ” አለ ። /ኢሳ. 65፡1/ “እግዚአብሔር ብቸኛ እንዳይሆን ሰግቶ እናትን ፈጠረ” ያሉኝ ባልቴት ትዝ አሉኝ ። 

እግዚአብሔር ከታሰርንበት ሊፈታን ስንት ዘመን ፈለገን ። አንተ አባታችን ነህ ፣ አንተ እናታችን ነህ መባሉ እውነት ነው ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሰኔ 26 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም