የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

እኔ ግን አለሁ !!!

ያፈገፈገን አይቼ ወደ ኋላ ስል ፣ እንደገና በፍቅርህ ገመድ ስበኸኝ ፣ በቤትህ እኔ ግን አለሁ ። አስጨናቂ ዘመናት ፣ ላያልፉ የመጡ የሚመስሉ እነዚያ ቀናት አልፈው ፣ በሕይወት እኔ ግን አለሁ ። እያንዳንዱ እርምጃዬን ጠላት ሲከታተለው ፣ ጠላቴን ሳትገድለው እኔን አድነህ እኔ ግን አለሁ ። ለድርድር ሳቀርብህ ፣ መስቀልህን ትቼ ወርቅ ስሸከም ሁሉን አሳጥተኸኝ ፣ አንተ ብቻ ትርፍ ሆነኸኝ ፣ ከነድካሜ እኔ ግን አለሁ ። በነበሩት ሳዝን ፣ ባለው ሳልረካ ፣ በሚመጣው ስሰጋ አቅሜን ብጨርስም ፍቅር ዋስ ሆኖኝ እኔ ግን አለሁ ። የሚወክለኝ ባይኖርም ፣ ብቻዬን የምወዛወዝ ቢመስለኝም ፣ ሥራዬን እየሠራህልኝ እኔ ግን አለሁ ።

አሳዛኝ ሆኜ ሰዎችን ባቆስልም ፣ እሾሃማ ሆነው ሰዎች ቢያደሙኝም ይቅር ብለኸኝ ፣ እኔ ግን አለሁ ። ለመታረም ዕድል ቢኖረኝም ፣ እኔ ግን “ንጹሕ ነኝ” ብዬ በእልህ ብቆምም ሳትጸየፈኝ እኔ ግን አለሁ ። ምግባር ሳይኖረኝ ጸጋህን ብገፋም ፣ የመልካምነት ምኞት እንጂ ኑሮው ባይሳካልኝ ፣ ሁሉን እስክረዳው ታግሠኸኝ እኔ ግን አለሁ ። ጳውሎስን መሆን እያማረኝ ሳውልን ስሆን ፣ በክፉ ብጀምርም በመልካም ለመጨረስ ስጥር ፣ “አይዞህ በርታ” እያልከኝ እኔ ግን አለሁ ። ከኅብረት ለማስወጣት ጠላቴ የሰውን እንከን ሲያሳየኝ ፣ መንፈስህ ግን “ወደ ራስህ ተመልከት ያን ጊዜ ነጻ ትወጣለህ” እያለኝ ፣ በግልግል እኔ ግን እስካሁን አለሁ ።

ለሥርዓት እየተጠነቀቅሁ ፣ ፍቅርን ስደፈጥጥ ፣ የተገለጸ ውድቀት ይዤ የተሰወረ የሰውን በደል ሳስስ ፣ “ተው ልጄ” እያልከኝ እስከ ዛሬ አለሁ ። ተከራካሪነቴን “ለእግዚአብሔር ክብር ነው” ብልም ለራሴ የበላይነት ነበረ ፣ ፈጥረህ አትጥልምና እኔ ግን አለሁ ። አይረባም ተብዬ ተጥዬ እንዳልኖርሁ ፣ አይረቡም ብዬ ሰውን ስገፋ እገረማለሁ ። ያስመረረኝ ድህነት በሰው ላይ ወድቆ ሳየው እጨክናለሁ ። አንተ ግን የረከሰውን ልቤን አጥበህ ከእኔ ጋር ልትኖር መቍረጥህን አውቄአለሁ ። ትዕግሥትህ የመኖር ምሥጢር ሆኖኝ እኔ ግን አለሁ ። ተማሪዎችህን ሳይ እየቀናሁ “እኔ ለዚህ ክብር እበቃ ይሆን ወይ” ስል ዛሬ ግን ደቀ መዝሙርህ ሆኛለሁ ። በሩቅ የምሰማህ ባለ ዝና ስቀርብህ በልጠህ አገኘሁህ ። ዓመታትን አሳልፈህ ፣ ሊያሳልፈኝ የመጣውን አሳልፈህ እኔ ግን አለሁ ።

ካንተ ካልረዳህ በቀር ማንም አይረዳም ። ለክፉ ቀን ያሉት ራሱ ክፉ ቀን ይሆናል ። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በጸጋህ ለምልሜ እኔ ግን አለሁ ። የነገውንም አንተ ታውቃለህ ። ለመኖር አቅም ትሆነኛለህ ። እኔ ግን አለሁ ክበር ተመስገን !!!!

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ተጻፈ ነሐሴ 15 ቀን 2015 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ