የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ!

ለመጠመቅህ ሰላም እላለሁ !

ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ! ሁሉ በዮርዳኖስ ቢሰበሰብ በደል አስጨንቆት ነው ፣ አንተ ግን ወደ ዮርዳኖስ የሄድኸው ጽድቅን ልትፈጽም ነው ። ሁሉ ወደ ዮርዳኖስ ቢሄድ በሚበልጠው በዮሐንስ እጅ ሊጠመቅ ነው ፣ አንተ ግን ወደሚያንስህ ወደ ዮሐንስ ሄድህ ። ሁሉ ወደ ዮርዳኖስ ቢሄድ በደል ተጭኖት ነው ፣ ሲመለስ በዕረፍት ነው ፤ አንተ ግን ዘላለማዊ ቅዱስ ነህ ። ሁሉ ወደ ዮርዳኖስ ቢሄድ ስለ ራሱ በደል ነው ፣ አንተ ግን ስለ ዓለሙ በደል ነው ። በዮርዳኖስ ነገሥታት አልተገኙም ፣ አንተ የነገሥታት ንጉሥ ግን ተገኝተሃል ። ሁሉ ወደ ዮርዳኖስ ቢገሰግስ ዮሐንስን መጥራት ስለማይችል ነው ፣ አንተ ግን ዮሐንስን “መጥተህ አጥምቀኝ” ልትል ሲገባህ የገሰገስህ ነህ ። ሁሉ ወደ ዮርዳኖስ ቢሄድ ጸጋን ሊቀበል ፣ ምሥጢረ ንስሐን ሊፈጽም ነው ፣ አንተ ግን ጸጋን ልትሰጥ ነው ።

ሰው ራሱን ተጸይፎ ከፊቱ ካለው ኃጢአተኛ ጀርባ ተሰልፏል ፣ አንተ ግን በኃጢአተኞች ሰልፍ ውስጥ ማንንም ሳትጸየፍ ቆመሃል ። እስራኤል ዮርዳኖስን መሻገራቸው የነጻነታቸው የመጨረሻ በር ነው ። ጥምቀትንም የጸጋና የቤተ ክርስቲያን በር አድርገህ ልትሰጠን በዮርዳኖስ ተጠምቀሃል ። በዮርዳኖስ ትይዩ ጌልጌላ ይታያል ፣ የግብፅ ነውር የተወገደበት የሸለፈት መቃብር ማዶ ቆሟል ። አንተም የሚጠመቁ ሁሉ ለዓለም ሞተው ፣ ላንተ ይኖሩ ዘንድ ጥምቀትን ባርከሃል ።

በተቀደሰው ጥምቀትህ የባሕርይ ልጅነትህ ተመሰከረ ፣ የእኛም ልጅነት በጥምቀት ይገኛል ። በጥምቀትህ ምሥጢረ ሥላሴ ተገለጠ ፣ እኛም በሥላሴ ስም እንጠመቃለን ። በጥምቀትህ ሰማይ ተከፈተ ፣ እኛም ስንጠመቅ መንግሥተ ሰማያትን እንወርሳለን ። በጥምቀትህ ልጅነትህ ተመሰከረ ፣ እኛም በጥምቀት በተቀበልነው መንፈስ ቅዱስ የጸጋ ልጅነታችን ተመስክሮልናል ። ጠላት “እናንተ የተጣላችሁ ናችሁ” ሲለን መንፈስህ ለመንፈሳችን የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁ ይለናል ። በጥምቀትህ ትሕትና ተገለጠ ፣ የተጠመቁ ሁሉ ትሑታን ይሆኑ ዘንድ አንተ አዘዝህ ። አንተ ያከበርከውን ጥምቀት እንዳናቃልል ፣ ምሥጢራትን እንዳናሳንስ እርዳን ።

ለተቀደሰው ጥምቀትህ ሰላም እላለሁ !!!

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 11 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ