መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እንኳን ለ2013 ዓ.ም የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት በሰላም አደረሳችሁ !

የትምህርቱ ርዕስ | እንኳን ለ2013 ዓ.ም የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት በሰላም አደረሳችሁ !

 

እኔን ጌታዬ

ከልዕልቶች ሳይሆን የነፍስ ጌጥ ካላት ከድንግል የተወለድህ ፣ ዘር ምክንያት ሳይሆንም ከብርሕት ደመና የተገኘህ የሕይወት ዝናብ ክርስቶስ ፤ እኔን ጌታዬ ፤ ስላልተቀበልኩህ አዝናለሁ ። በእኔ ዓለም መጥተህ ችላ አልኩህ ፣ ባንተ ዓለም መንግሥትን ልትሰጠኝ እየጠበቅኸኝ ነው ። ሰማየ ሰማያት የማይችሉህ በናዝሬት ብሥራትህን ፣ በቤተ ልሔም ልደትህን ፣ በዮርዳኖስ ጥምቀትህን ፣ በኢየሩሳሌም ሞትህን ፣ በደብረ ዘይት ምጽአትህን ያደረግህ ፤ እኔን ጌታዬ በበረት ወድቀህ እኔ ግን በቤት አደርኩኝ ። አልጋ ቢጠብ እንኳ መሬት ወርጄ አላስተናገድኩህም ፤ ጎረቤት ለምኜ የዛሬን አሳድሩልኝ አላኩህም ። 

የዘላለም አባት ሳለህ ሕፃን የተባልህ ፣ ዓለማትን በመዳፍህ ይዘህ በድንግል እቅፍ ያደርህ ፤ እኔን ጌታዬ ከከብቶች አንሼ ልብስ እንኳ ባይኖረኝ እስትንፋሴን አላሞቅሁህምና ኀዘን ያዘኝ ። ከምሥራቅ የመጡ ሰብአ ሰገል ሲሰግዱልህ የቅርቡ እኔ ግን ሞትህን ስመኝልህ ፣ ነገሥታት አምነውህ እኔ ድሀው ስክድህ እኔን ጌታዬ አብጄ እንጂ ጤነኛ ሆኜ አይደለምና ይቅር በለኝ ። ዮሴፍና ሰሎሜ ሲያገለግሉህ እኔ ግን ለማይሞላው ኑሮዬ ስሮጥ ፣ ቀኑ አልበቃ ብሎኝ በሌሊትም ስማስን ፤ እኔን ጌታዬ ችላ አልኩህ ። ዓለምን ሳትለያት ወደ ዓለም የመጣኸው ፣ የሰጠኸውን የምትቀበል እንጂ የባሕርይውን የሚሰጥህ የሌለ ፣ እኔን ባለጠጋ ለማድረግ አንተ የበለሶን ቅጠል ለበስህ ። እናትህ ቢጨንቃት ወደ ከብቶቹ እስትንፋስ አስጠጋችህ ። የሚራገጡ ከብቶች ተንበርክከው በትንፋሻቸው አሞቁህ ፣ እኔን ጌታዬ ብራቆት የሚያምርብኝ እኔ ነበርሁ ። አንተ ግን ስድቤን ወስደህ ክብርን ፣ ነውሬን ወስደህ ጽድቅን ሰጠኸኝ ። ሰው ከብት ብሎ ይሳደባል ፣ ባንተ ላይ ግን በሩን ዘግቷል ። ሰው አህያ ብሎ ያዋርዳል ፣ አህያ ግን በዕለተ ሆሳዕና አንተ ተሳፍረህባታል ። አህያ ተሸክማህ ኢየሩሳሌም ገባህ ፣ ሰው ግን መስቀል ይዞ ጠበቀህ ። ከከብቶቹ ከአህዮቹ ያነስን ፣ የገነባኸውን መቅደስ የምናፈርስ ነን ። እኔን ጌታዬ እኔን በመውደድህ አዘንኩልህ ።  

የጥበብ ሰዎች ከሩቅ መጡ ፣ እኔ ግን አንድ የፍልስፍና መጽሐፍ አንብቤ ክርስቶስ ማነው ? አልኩህ ፣ እኔን ጌታዬ ያልካድከኝን ካድኩህ ። ባለጠጋ አገሮች በእግዚአብሔር እናምናለን ሲሉ ፣ የእኔ ድሀ አገር ግን ስምህን ለመጥራት አፈረች ፤ እኔን ጌታዬ መሬትን ዘርግተህ ከመሬት ከፍ አድርገን ሰቀልንህ ። ሩቅ መንገድ ተጉዞ የመጣ ፣ ከሰማይ ወደ ምድር የተዘረጋ እንዳንተ ያለ የሩቅ አገር እንግዳ የለም ። እኔ ግን እንግዶቼን ዘመናይነትን ፣ የወረት ፍቅርን አስበልጬ ቸለል አልኩህ ። እኔን ጌታዬ ስሸሽህ ትከተለኛለህ ። ሰው የለኝም እያልኩ ስጨቀጭቅህ ፣ ያሉትም ሰዎች የጨው ውኃ ሆነው መልሰው ሲያስጠሙኝ ፣ አንተ ግን ሰው ሆነህ መጣህልኝ ። እኔን ጌታዬ ሳልስምህ አለፍኩኝ ። 

አንተ የሰው ልጅ ካልተባልህ እኔ የእግዚአብሔር ልጅ አልባልምና ፣ ሁለተኛ ልትወልደኝ ሁለተኛ ልደት ከድንግል የተወለድህ ፣ እኔን ጌታዬ ከሚጫወቱ ሕፃናት መሐል ጎትቼ ሳላቅፍህ ዘመን አለፈብኝ ። ያለፈውን ዕድሜዬን ብትመልሰው ማንም ሳይጋራኝ ላንተ ብቻ እኖርልህ ነበር ። ለባከነው ጊዜ ሲቆጨኝ እየባከነ ያለው ዛሬ ተረሳኝ ። እኔን ጌታዬ እባክህ ለራስህ አኑረኝ ። በሃያ የጠፋ ልብ በአርባ ይገኛል ፣ እኔን ጌታዬ እኔ ግን ልብ ካልሆንከኝ በስድሳም ወደ ማስተዋል አልመጣም ። እኔን ጌታዬ አንተን ብቻ አሰቃየሁህ ፣ የምፈልገውን በቅጡ ሳላውቅ በመቅበጥበጥ በጠበጥኩህ ።

እረኞችና መላእክት የተራራቁ ናቸው ። ልደትህ ግን አንድ አደረጋቸው ፣ ሰማይና ምድርን ያገኛኘ ልደትህ ቡሩክ ነው ። እኔን ጌታዬ ሳላስብህ ሌሊቱ ነጋብኝ ። የክፉዎችን ክፋት ሳስብ ያንተ ደግነት ተጋረደብኝ ። ስምዖን በታቀፈህ ጊዜ መኖርን ጠገበ ። የመኖር ልኩ መድኃኔዓለም እኔም በእምነት ልቀፍህና ከዚህች ዓለም ጋር ያለኝ ሰማንያ ይቀደድ ፤ ጋብቻውም ይፍረስ ። በመወለድህ ለዓለም ፍስሐ ሆነህ እናትህ ግን በነፍስዋ ሰይፍ አለፈ ። እጅግ ለሚወዱህ ሰይፍን የመደብክ ፣ ለራስህም ሳትሳሳ በመስቀል የሞትህ ፣ የመዳንን ጉዞ በልደትህ የጀመርህ ፤ እኔን ጌታዬ ሸክምህን ሳልካፈልህ ቀረሁ ። ዕዳህ ሳለሁ ልጄ ፣ ጠላትህ ሳለሁ ወዳጄ ፣ ዕውር ሳለሁ ብርሃኔ ፣ ብቸኛ ሳለሁ ዓለሜ ያለኝ ፍቅርህ ይባረክ !!! 

ነገን ከሰጠኸኝ ፣ ቀኑን ከልቡ ጋር ካደልከኝ ላመሰግንህ እተጋለሁ ። ዘንድሮን አይቻለሁ ፣ ነገም ያንተ ምሥጢር ነው ። ራሴን ለማሳየት ፣ መልኬ ቅላቴ ለማለት እጨነቃለሁ ፣ ነገ ሲፈርስ ላፍር ዛሬ በዚህ ውበቴ አንተን እጋርድበታለሁ ። እኔን ጌታዬ ፣ ራሴን ጨረታ ካወጣሁበት ፣ ልታይ ልታይ ካልሁበት አለማወቅ አድነኝ ። ልታይ ስል ስለጋረድኩህ ይቅር በለኝ ። የልደትህ በረከት ለእኔና ለሰው ልጅ ሁሉ ይድረስ ። አሜን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሐሙስ ታኅሣሥ 29 ቀን 2013 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም