መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እንደ ተናገረ ተነሥቷል

የትምህርቱ ርዕስ | እንደ ተናገረ ተነሥቷል

 “እንደ ተናገረ ተነሥቶአልና በዚህ የለም”ማቴ. 28፡6
“ሃሌ ሉያ ዮሴፍ ወኒቆዲሞስ
ገነዝዎ ለኢየሱስ በሰንዱናት
ለዘተንሥአ እሙታን በመንክር ኪን ።”
ትርጓሜ፡-
“ሃሌ ሉያ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ
ድንቅ በሚሆን ጥበብ ከሙታን ተለይቶ የተነሣ
ኢየሱስን በበፍታ ገነዙት ።” /ቅዳሴ/  
በዓለም ላይ ገደልሁ ብሎ የማያርፍ ጠላት ከባድ ነው ። አይሁድ ጌታን ገደልነው ብለው አላረፉም ። ጠላት ለጊዜው እንጂ እስከ ዘላለሙ መግደል አይችልም ፣ ሥጋን እንጂ ነፍስንም መግደል አይችልም ። ትንሣኤ የገዳዮችን አለመቻል ያሳየ ነው ። መግደል የሚችሉ ማሥነሣት አይችሉም ። “ከጅል ጠብ ጠብቀኝ” ብሎ መጸለይ መልካም ነው ፤ የጅል ጠብ ማለቂያ የለውምና ። ገዳይም ከገደለ ሟችም ከሞተ ሁለቱም ለምን አያርፉም ? ገዳይን የሚገድለው ሞት ሳይሆን ትንሣኤ ነው ። የገደለን ቢገድሉት ከክፋቱ ጋር ሞተ ፤ ገዳይ ሺህ ጊዜ የሚሞተው በትንሣኤ ነው ። መግደል እየቻለ የሞተ ክርስቶስ ነው ። ሰው እየቻለ እንኳን ሊሞት ሊገላምጡት አይፈቅድም ። የሰው ልጅ መግደል ይችላል ፣ የእግዚአብሔር ሥልጣን ግን ማሥነሣት ይችላል ። መግደል ማፍረስ ነውና ሙያ አይጠይቅም ፣ ትንሣኤ ግን ሙያ ይጠይቃል ። ገደልን ብለው እንዳይደሰቱ እግዚአብሔር ትንሣኤን ያውጃል ። መሞት ባይኖር ትንሣኤ አይኖርም ነበር ። ጠላት ባይኖርም ሞት የለም ነበር ። በጠላት ሰፈር ሞቶ በእግዚአብሔር ክብር መነሣት በእውነት ትልቅ ነው ። ሞት ጊዜያዊ ትንሣኤ ግን ዘላለማዊ ነው ። ሞት መጨረሻ አለመሆኑን ያበሰረን የክርስቶስ ትንሣኤ ነው ። አልዓዛር ቢነሣ ለራሱ ተነሥቷል ፣ ክርስቶስ ግን እኛን ይዞ ተነሥቷል ። መስፍኑ ጲላጦስ ክርስቶስ ከሞት መነሣቱን ከወታደሮቹ በየተራ ጠይቆ ከተረዳ በኋላ በትንሣኤው አመነ ። ይህንንም እምነቱን ለሮማው መንግሥት አሳወቀ ። በዚህ ምክንያትም ሰማዕት ሁኖ ሞተ ። የክርስቶስ ትንሣኤ ጠላትን ወዳጅ ፣ ገዳይን ሰማዕት ያደርጋል ። በመግደል ከምናሸንፋቸው በመነሣት የምናሸንፋቸው ብዙ ናቸው ። ከተነሣን ከክርስቶስ ጋር እንነሣ ። ገዳይ እንቅልፍ የለውምና እንቅልፍ አጡ ። ክርስቶስ ግን የወይን ስካር እንደ ተወዉ ኃያል ተነሣ ። ትንሣኤው ሞትን ማንቀላፋት እንድንለው አደረገን ። የተኙ ሁሉ ይነቃሉ ።

የመቃብሩ ጠባቂ ወታደሮች ጌታችን ዐርፎ ሳለ ነቁ ፣ ሲነሣ ተኙ ። እንደ በድን ሆኑ ። አይሁድ ለመግደል ሸንጎ እንደ ሠሩ ሲነሣ ሸንጎ አልሠሩም ፣ ትንሣኤውን አምነዋልና ። ሰው የመጨረሻ የጉዳት መሣሪያው መግደል ነው ። ትንሣኤ የሰውን አቅመ ደካማነት ያሳየ ነው ። በየቀኑ ስለ እርሱ እንገደላለንና በየቀኑ የትንሣኤው ኃይል ያስፈልገናል ። ጠንካራ ልብ እንኳን በተአምራት በትንሣኤውም አያምንም ። ብዙ ተአምራት ቢደረግ ተአምራቱን የሚያምን እንጂ ተአምር አድራጊውን የሚያምን ትውልድ አይነሣም ። እግዚአብሔር ኃይሉን የሚገልጸው እንዲያሳምነን ብሎ አይደለም ። እርሱ የሰውን ልብ የሚያንኳኳው በፍቅር ብቻ ነው ። ተአምራትን ለራሳችን ዝና የምንፈልገው ቢሆንም ለእግዚአብሔር ክብር ነው እንላለን ። በቤተ ክርስቲያን ያለ ማቋረጥ የሚሠራው የትንሣኤው ኃይል ነው ። የካህናት ምክር ፣ የአለቆች ሴራ ፣ የመኳንንት ፍርድ ፣ የጎበዞች ቍጣ ፣ የይሁዳ ክዳት ፣ የጴጥሮስ ፍርሃት ፣ የማርቆስ ልብሱን አውልቆ መሸሸ ፣ የደቀ መዛሙርት መበተን ሁሉም ጸጥ አሉ ። በሞተ ቀን ሰዎች ይጮኹ ነበር ፣ ስለዚህ እግዚአብሔር ዝም አለ ፤ በትንሣኤው እግዚአብሔር ሲናገር ሰዎች ጸጥ አሉ ። በቤት የተደበቁ ደቀ መዛሙርት ወጡ ፣ ከተማውንም የሞሉ ተሰወሩ ። ትንሣኤ ገዳዮችን ያሳፈረ ነው ። በትንሣኤ ዘጉባዔ በመጨረሻዋ ቀንም ገዳዮችን ሁሉ የሚያሳፍር መነሣት ይሆናል ። ሰይጣን እስከ ጊዜው ቢበርድም ለክፋቱ ተስፋ አይቆርጥም ፣ ገሀነም ለሚባል ርስት ይህን ያህል መድከሙ ይገርማል ። “ለወሬ የለው ፍሬ ፣ ለአበባ የለው ገለባ” ቢባልም ሰው አሁንም በክፋት ጠንክሯል ። ሟቹ ሰው ይገድላል ።

አይሁድ የሞት ፍርድ መስጠት ስለማይችሉ ጌታችንን ወደ ጲላጦስ ወሰዱት ። ወደ ጲላጦስ ማምጣታቸው ብቻውን እንዲሞት መፈለጋቸውን ይናገራል ። ሞት ቀረሽ ዱላና ጥፊ አውርደውበታል ፣ ትንፋሹ ስትዳከም ወደ ጲላጦስ አምጥተውታል ። ክርስቶስ ሲነሣ ግን ወደ ገዥው ጲላጦስ መሄድ አልቻሉም ። የትላንት መቻል የዛሬ መቻል አይደለም ፣ የኮሩ ሁሉ የሚያፍሩበት ቀን ይመጣል ። ደቀ መዛሙርቱ በፍርሃት ሦስት ቀን በኢየሩሳሌም ቆዩ ፣ በጌታ ትእዛዝ ደግሞ በኢየሩሳሌም ለአሥር ቀን ቆዩና በበዓለ ሃምሳ ወጡ ። ሁለት ዓይነት መሸሸግ አለ ። አንደኛው ኃይል አጥቶ መሸሸግ ሲሆን ሁለተኛው ኃይል ለመቀበል መሸሸግ ነው ። ደቀ መዛሙርቱ ጉቦ ከፍለው ወታደር ጉቦ በልቶ በድኑን እንዳያወጡት መቃብሩ በንጉሣዊ ማኅተም ታተመ ። ታሽጓል የሚለው ማኅተም ሳይቀደድ በዝግ መቃብር ክርስቶስ ተነሣ ። ማኅተማቸውን አልነካም ፣ የትንሣኤውን ማኅተም ግን በሚያምኑት ላይ አተመ ።
መሞቱን የሚያረጋግጥ የሕግ አስፈጻሚዎች ማረጋገጫ ነበረ ። መነሣቱንም ሕጋውያን አረጋግጠዋል ። የአፍ አማኞችና ያላመኑ ክርስቶስን በመስቀል አንድ ሆኑ ። የአፍ አማኞች ቍጥራቸው ከከሀዲዎች ጋር ነው ። በዚህ ሁሉ ውስጥ ሥጋውን እንጂ ፍቅሩን መግደል አልቻሉም ። ሥጋም ሞቶ ሕያው መሆን ይችላል ፣ ፍቅር ሞቶ ግን ሕያው መሆን አይቻልም ። ጌታ ሲነሣ ወደ ቀያፋ ግቢ ሳይሆን ወደ ደቀ መዛሙርቱ ሄደ ። እርሱ ለብሽሽቅ አልተነሣም ። ትንሣኤ ወደ ሞት የሚለወጠው ከሰው ጋር ውድድር ውስጥ ስንገባ ነው ። የመነሣቱን ነገር ደቀ መዛሙርቱ በከፊል ልብ ተቀበሉ ፣ ቶማስ ጣቴን በተወጋው ጎኑ ካላገባው አላምንም አለ ። ጠላቶቹ ግን አምነዋል ። ደቀ መዛሙርቱ ሞቱን ሲነግራቸው አላመኑም ነበር ። ጠላቶቹም በሞቱ ሰግተው ነበረ ። ይሁዳን ጠቋሚ ፣ ጲላጦስን ዳኛ ፣ የመያዣ ሰዓቱን እኩለ ሌሊት ማድረጋቸው ስጋት ነው ። ትንሣኤውን ግን በሙሉ ልብ አመኑ ። ጠላቶቹ ትንሣኤውን ያመኑት ሳይነሣ ነው ፣ ደቀ መዛሙርቱ ግን ተነሥቶም ማመን አቃታቸው ። መላእክት የገረማቸው ትንሣኤው ሳይሆን ሞቱ ነው ፤ ሰውን ግን የገረመው ሞቱ ሳይሆን ትንሣኤው ነው ። ጌታችን የወዳጆቹን ስጦታ የሚያከብር ቢሆንም የመግደላዊት ማርያምን ሽቱ ግን ሳይቀባ በእኩለ ሌሌት ተነሣ ። ሕያው ነውና የሙታንን ሽቱ አልተቀባም ። በድሆች ቤት የኖረው በባለጠጎች መቃብር ለሦስት ቀን ተጋበዘ ። ሁሉ በሁሉ ነውና ። መቃብር ቶሎ የሄደ እንግዳ ያለ ዛሬ አላየችም ። መቃብር መቃብር ሳትሆን የእንግዶች ማደሪያ ሆነች ። ቤት የሌለው ማዕድ አቅራቢ ክርስቶስ በምድረ በዳ ስንቱን አጠገበ ። በተውሶ መቃብር ተቀብሮ ላዋሱት መለሰ ። ሰባት አጋንንት የወጣላት መግደላዊት ማርያም የሌሊቱ ጨለማ ሳያስፈራት ገሰገሰች ። ከትልቁ ጨለማ የወጣ ትንሹን ጨለማ አይፈራም ። ትንሣኤው ያልጠበቁት ነገር የሚገኝበት ነው ። መግደላዊት ማርያም ቅዱስ በድኑን ስትፈልግ እርሱ ተነሥቷል ፤ ከፈን ስታስስ ብርሃን ለብሷል ፣ ከመሬት በታች ስትሻው እርሱ ከተማውን አጥለቅልቋል ፣ በጠባብ ዋሻ ስትፈልገው ሰፊው ዓለም አልቻለውም ።
ሞቱን ለማየት የወጣው ሕዝብ ግን ትንሣኤውን ለማየት አልወጣም ። ሞቱን ሺህዎች ተመለከቱ ፣ ትንሣኤውን ግን አሥራ አንድ ሰዎች አከበሩ ። ስንሞት ብዙዎች ይመጣሉ ፣ ስንነሣ ግን ጥቂቶች ይመጣሉ ። ዓለሙ የሬሳ ስፖንሰር ነው ። ዓለም ሞት አንጋሽ ነው ። ክርስቶስ ግን ሕይወት አክባሪ ነው ። ጨለማ ፣ አጋንንት ፣ መቃብር ፣ ሲኦል ፣ ሞት ያልቻሉትን የክርስቶስን ትንሣኤ ማንም አይችለውም ። በጥንተ ተፈጥሮ ዕለተ እሑድ የሥራ መጀመሪያ ነበረች ፣ የአዲሱ ዘመን ብሥራትም በዕለተ እሑድ ሆነ ። ዓለም ከተፈጠረበት እርካታ ክርስቶስ የተነሣበት ድል ይበልጣልና ይህች ቀን ለክርስቲያኖች የዝማሬ ቀን ሆነች ። በዚህች ሌሊት ከጨረቃ ፣ ከከዋክብት ፣ ከፋኖስ ተለየ የትንሣኤ ብርሃን አበራ ። ጨረቃና ከዋክብት ለሥጋ ያበራሉ ። ትንሣኤው ግን የነፍስ ብርሃን ነው ። ሥጋን መግደል የቻሉት ነፍስን መግደል አይችሉምና በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ነጻነትን ሰበከ ። መለኮት ግን ከሥጋውም ከነፍሱም ለቅጽበት እንኳ አልተለየም ።
ትንሣኤውን መረዳት ያልቻሉ ሰዎች ክርስቶስ ቅዱስ ስለሆነ ተነሣ ይላሉ ። ቅዱስ ባይሆን ኑሮ አይነሣም ማለታቸው ነው ። ስለዚህ ትንሣኤው የቅድስና ዋጋ ነው እያሉ ነው ። ክርስቶስ ግን የተነሣው በኃይልና በሥልጣን ነው ። ነገሥታት ሁሉ ሞታቸውን አያወሩም ። እነሣለሁ ብለውም አይናገሩም ። ቢናገሩም መተረቻ ሁነው ይቀራሉ ። እነሣለሁ ብሎ የተነሣው ግን ክርስቶስ ብቻ ነው ። እንደ ተናገረ ተነሥቷል ፣ በዚህ የለም ።
ጸሎት
ጌታዬ ሆይ የሕያውነትህን ሽቱ ከማርያም እንተ ዕፍረት ጋር ሆኜ ልቀባህ ።ሽቱ ብይዝም እንደ መግደላዊት ማርያም ሰዓቱ እንዳያልፍብኝ እባክህ እርዳኝ ። በምድር ተኝቼ በሰማይ ማገልገል እንዳያምረኝ ፤ ለማልኖርበት ዓለም ሰብስቤ ወደምኖርበት ዓለም ባዶ እጄን እንዳልሄድ እባክህ አንቃኝ ። ዮሴፍና ኒቆዲሞስ እየሳሙ የገነዙህ ፣ አንተ የፍቅር ዳርቻው ፣ ከአንተ በቀር ፍቅር የለምና እኔም በእምነት እስምሃለሁ ። በረድኤትህ መሰወር ፣ እኔነቴን ባንተ መሸፈን ፣ በትንሣኤ መዝሙር መሞላት እሻለሁ ። መሸነፍን ፣ መውደቅን ፣ ለጠላት እጅ መስጠትን ከእኔ አርቀው ። በዘላለም ክብርህ አሜን ።
የመስቀሉ ገጽ 5
ሚያዝያ 12 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን 
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም