መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እንዲህ ቢሆንስ » እንዲህ ቢሆንስ …? /6/

የትምህርቱ ርዕስ | እንዲህ ቢሆንስ …? /6/

“ባለቤቴ ትዳሩን በጣም የሚወድ ሰው ነው ። በታማኝነትም የምጠረጥረው አይደለም ፣ እርሱም ከብዙ ወንዶች መሐል ቢያየኝ በእኔ ይተማመናል ። ነገር ግን ቢሞትስ ፣ ልጆቹን ምን አደርጋለሁ ? እያልኩኝ እጨነቃለሁ ። በዚህም ምክንያት እርሱ ሳያውቅ የምተኛው በእንቅልፍ ኪኒን ነው” እያልሽ ይሆን ? ባለቤትሽ የሚያውቅሽ ከወላጆችሽ በኋላ ነው ። እግዚአብሔር ግን የሚያውቅሽ ከወላጆችሽ በፊት ነው ። በማሕፀን ሰውሮ የመገበሽ ማነው ? ገና ወላጆችሽ ሳያስቡሽ ዓለም ሳይፈጠር በፍቅር ያየሽ ማነው ? እግዚአብሔር አይደለም ወይ ? ከማሕፀን ስትወጪ ወላጆችሽን ፣ ከቤት ስትወጪ ባልሽን እንዲቀበልሽ ያደረገ ማነው ? አንቺን ሌጣዋን ያበዛሽ የሚወድሽ የሰጠሽ ወዳጅሽ እግዚአብሔር አይደለም ወይ ? ለሴትነት ምቾት በሌለበት ዓለም ላይ መንገድ ከሚያስቀሩ ፣ በአካል ፣ በጤና ፣ በክብር ከሚጥሉ ሽፍቶች ጠብቆ ለዚህ ያደረሰሽ ማነው ? አትችይም ተብለሽ አድገሽ እግዚአብሔር ባንቺ ሲችል አላየሽም ወይ ? በቅርፊት ውስጥ ያለች ጫጩት ጊዜዋ ሲደርስ ራሷ ሰብራ ወይም እናቲቱ ሰብራላት አሊያም ቅርፊቱ ተሰብሮ ትወጣለች ። ምናልባት አንቺም ራስሽ ሰብረሽ የወጣሽ ፣ ወላጆችሽ ባለ ራእይ ያደረጉሽ አሊያም ወቅቱ አግዞሽ እዚህ ደርሰሽ ይሆናል ። ነገር ግን በሁሉም ሥራሽን የሠራልሽ የሠራዊት አምላክ እግዚአብሔር ነው ። እርሱ ከበረታ ጋር ሳይሆን ከተጎዳ ጋር የሚቆም ፣ ባንቺ ላይ ያለውን የራሱን መልክ የሚያከብር ነው ።
ረቂቁን ዓለም ታዪ ዘንድ እግዚአብሔር በጥበብ ፈጥሮሻልና በትንንሽ ጉዳዮች አትዘግዪ ። የትውልድን አደራ ትሸከማለች ብሎ ማሕፀንሽን ዓለም ፣ ክንዶችሽን ትራስ ፣ ፍቅርሽ ጥላ አድርጎ ይህን ዓለም ከዚህ አድርሶታል ። አልችልም ባይነት ሲጠራሽ የእግዚአብሔር ሥራ አለብኝ በይ ። በትንሹ በጀት ገበታ መሙላት ፣ ባለቀው ዘይት በበረከት መኖርን ካንቺ ይልቅ የሚያውቅ ማነው ? ዓይኖችሽ መርማሪ የእግዚአብሔር አገልጋዮችን ችግር የምታዪ ፣ እግዚአብሔር ብቸኛ እንዳይሆን የእናትነት አንጀቱን የሰጠሸ ላንቺ አይደለም ወይ ? በራብ ዘመንም አገልጋይ ማስጠጋት በረከት እንዳለው የምታውቂ የሰራፕታዋ መበለት አንቺ አይደለሽም ወይ ? ተፈርቶ ነገር ግን ተርቦ የሚኖረውን ኤልሳዕን በር ከፍተሸ የተቀበልሽ ፣ በሰገነት ላይ ማደሪያ የሠራሽ የሱነም ትልቅ ሴት አንቺ አይደለሽም ወይ ? ዛሬ ነገሥታት እየነገዱብሽ ሥራ አስጀመርናት የሚሉሽ መቼ ሥራ ፈትተሸ ታውቂያለሽ? ጌጥሽ ቅድስና መሆኑን ረስተው በብልጭልጭ ነገር ሊያታልሉሽ የዘመቱት እንዴት አላዋቂዎች ናቸው ? ጓዳ ተቀምጠሸ የአደባባይ ሠራዊትን የምታሰለጥኚ ፣ አገር ሲደፈር ልብሽ ዘምቶ የምታዘምቺ አንቺ አይደለሽ ወይ ? የቤትሽን ገመና ሸፍነሽ ፣ ጦርነትን ያስቆምሽ አቢግያ ፣ የዳዊትን እጆች ከደም የከለልሽ ፣ የተቆረጠ እልቂትን የሻርሽ ጥበበኛ አንቺ አይደለሽም ወይ? ሳሙኤልን ወልደሽ ለእግዜር የሰጠሸ ፣ እግዚአብሔር መቻሉን ሲያሳይሽ መልሰሽ ለእግዚአብሔር የሰጠሸ አንቺ አይደለሽም ወይ ?
የሰማይ ማደሪያን በጸሎትና በእንባ ያራስሽ አንቺ አይደለሽም ወይ ? አዳም እንዳይቀየም በወንድ ጾታ ሰው ቢሆንም አምላክ ግን የተወለደው ከሴት ዘር አይደለም ወይ ? ከአዳም ጎን አንቺ ተገኘሽ ፣ ከድንግል ደግሞ ፈጣሪ ተወለደ ። ፍጡር ፈጣሪውን ወለደ የተባለው በአንቺ ላይ በተሠራው ሥራ ነው ። እውቀትን ፣ ጸሎትን ፣ ዝምታንና ትዕግሥትን ገንዘብ ስታደርጊ ባንቺ ዓለምን የሚለውጥ ሥራ እግዚአብሔር ይሠራል ።
አዎ ዘር ተቀብለሽ ልጅ አድርገሽ የምትሰጪ ፣ ትንሹን ፍቅር አብዝተሸ የምትመልሺ ነሽ ። መልካም ባል ብታገኚ የሠጠሸ የመልካሞቹ መልካም ፤ የሁልጊዜው መልካም እግዚአብሔር ነው ። የተሰጠሸ ነገር ስስት ሁኖ እንዲያከሳሽ ሳይሆን መልካም ነገር ከእግዚአብሔር ነው ብለሽ እንድታመሰግኚ ነው ። ጥሩውንም ባል ፍጹም ነው አትበዪ ። የጠላት ፍላጻ ውስጥ እንዳይገባ ባሌ የሚታይ መልአክ ነው ብለሽ አታውሪ ። የዘላለም ኪዳን ከእግዚአብሔር ጋር እንጂ ከሰው ጋር ያለው ኪዳን ሞት እንደሚፈታው አስቢ ። ሳሉ መዋደድ እንጂ ሲሞቱ መላቀስ ግብዝነት ነው ። ሁላችንም እንሞታለንና እገሌ ቢሞትስ ብለን አንጨነቅም ። ሞት ሁሉም ሰው የሚከፍለው የራሱ ዕዳ ነው ። በትክክል ለኖረ ሞት አሳሳቢ አይደለም ። ባልሽን አክብሪው ልጆችሽ ይፈሩሻል ። ባልሽን አስጊጪው አደባባዩ ይመርቅሻል ። ባልሽን ሸፍኚው አጥርሽ የማይደፈር ይሆናል።
እግዚአብሔር ላንቺ የሰጠሸ መርጦ ነውና ጉድለቱን እንደ ሙላት ተመልከቺ።የሚያናንቅ ሰነፍ መሆን ነውና ጎበዝ ሁኚ ። መኖሪያሽ የዘላለም አምላክ ነውና በሚዝል በሰው ክንድ ላይ አትንተራሺ ። ዕረፍት በማጣት እንዳይጎዳ ባልሽን ምከሪ ።  ኑሮዬ ይበቃኛል ካላልሽ ቤትሽ ይፈርሳል ። የሰው ልጅ ከምግብ ይልቅ የሚጠግነው ሰላም ነውና ሆደ ባሻ አትሁኚ ። ወንድ ልጅ ክብሩን ያመልካልና የስድብ ቃል ከአፍሽ አይውጣ ። በጓደኞቹን ፊት ድካሙን አታውሪ ። ሰዎች ዝም ብለው ያንቺን ብሶት የሚሰሙት የባሰ ጉድ በቤታቸው ተሸክመው ነው ። ልቅሶ የሌለበት ቤት የለም ። ጥርስ ፣ ልብስና አጥር የሸፈነውን እግዚአብሔር ብቻ ያውቀዋል ። በጣም ደስተኛ ለመሆን የሚሞክሩ ሰዎች በጣም ኀዘነተኛ መሆናቸውን እወቂ ። በምድር ላይ ካሉት ሁሉ ያንቺን ባል የሚመስል የለም ። ከሰው ሙሉ ያንቺ ጎዶሎ ያንቺ ነው ። በልጅ ተመክተሸ ባልሽን እንዳትረሺ ፣ ልጅ ለራሱ ነው ፤ ባልሽ ግን ላንቺ ነው ። ከደግ ልጅ ክፉ ባል ይሻላል ። ልጅ ምንም ደግ ቢሆን አምጣ ሲሉት ያሳቅቃል ። ባል ግን አምጣ ይባላል ።
ሞትን የሚፈራ በትክክል የማይኖር ነውና ብሞትስ ፣ ቢሞትስ ብለሽ አትስጊ።ራስሽንም አታውኪ ። ሞት ሲመጣ ከመጽናናት ጋር ነው ። ዛሬ ግን ያለመጽናናት በስጋት እንዳይጎዳሽ ተጠንቀቂ ። ነገ ያንቺ አይደለምና ዛሬን ኑሪ። ዛሬን በትክክል ከኖርሽ ለነገ ይተርፋል ። እግዚአብሔር ጓዳሽ ይባርክ።
ወደ ክርስቶስ መገስገስ 11
ጥቅምት 6 ቀን 2011 ዓ.ም.
ተጻፈ አዲስ አበባ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም