የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

እንዳይለመድህ ብሎ መግደል

“እንግዲህ አሕዛብ ደግሞ በአእምሮአቸው ከንቱነት እንደሚመላለሱ ከእንግዲህ ወዲህ እንዳትመላለሱ እላለሁ በጌታም ሆኜ እመሰክራለሁ ።” ኤፌ. 4፡17።

ትምህርት ያለው ከሕይወት እንጂ ከሞት አይደለም ። ሰው የሚለወጠው በሕይወቱ እንጂ በሞቱ አይደለም ። የትላንት ስህተት በዛሬ ንስሐ ይካሳል ። እያንዳንዱ ቀን አዲስ ጉዞ ለመጀመር የተሰጠ ተጨማሪ ዕድል ነው ። ዛሬ ሲጨመርልን እግዚአብሔር በእኛ ተስፋ እንዳልቆረጠ እንረዳለን ። የተሸከማቸው ጌታ ሳይደክመው ላየናቸው የሚደክሙን ሰዎች ካሉ የስህተት መንገድ ላይ ነን ። ሰይጣን በሚያንሰው ኃጢአት ንጹሕ አድርጎ በሚበልጠው በትዕቢት የሚይዛቸው ሰዎች አሉ ። መፍረድ ወድቄ አላውቅም ፣ አልወድቅምም ብሎ እንደ ማሰብ ነው ። “እንዳይለመድህ” ብሎ መግደል ትርጉም የለውም ። እንዳይለመድህ የሚለው ቃል ስህተት ላይ ቆሞ የሚነገር ሲሆን ስህተትህን ልማድህ አታድርገው ማለት ነው ። እንዳይለመድህ ብሎ መቅጣት ግን የወላጅ ፣ የመምህርና የወዳጅ መሣሪያ ነው ። ወላጅም ወልዶ አሳድጓልና ፣ መምህርም አስተምሯልና ወዳጅም ለወዳጁ ዋጋ ከፍሏልና የመቅጣት መብት አላቸው ። ያልወለዱ ፣ ያላስተማሩ ፣ ያልወደዱ ሰዎች የመቅጣት መብት የላቸውም ። ልደት ፣ ትምህርት ፣ ፍቅር ሥልጣን ይሰጣሉ ። አባትነት ፣ መምህርነት ፣ ወዳጅነት ሥልጣን ነው ።

ቅጣት በቀል ከሆነ ፣ ቅጣት ጠላቴን አሁን አገኘሁት የሚል የሥጋ ደስታ ከሆነ መንፈሳዊ አይደለም ። ቅጣት ለረጅምና ለአጭር ጊዜ የሚቆይ ደወል ነው ። ደወልነቱም ሕመም አለው ። ሕመሙን እያስታወሰ ወደ ቀደመ ክፉ ተግባሩ እንዳይመለስ ቅጣት ያግዳል ። እንዳይለመድህ ተብሎ በደለኛ በትር ይመዘዝበታል ። የቅጣቱ መሠረት ፍቅር ፣ ግቡም የዚያ ሰው የሞራል ልዕልና ነው ። ዓላማውም ሰብሮ ማስቀረት ሳይሆን የተሻለ ሰው እንዲሆን መናፈቅ ነው ። አንተ በሥጋ ስትወድቅ እኔ በተስፋ ወድቄአለሁ ፣ አንተ ስትሰበር እኔ በልቤ አንክሻለሁ በማለት ወዳጅ ይቀጣል ። ቅጣት ወላጅ ሲያደርገው እንዴት እንዳሳደገው በማሰብ የትላንቱ መልአክ ልጅ እንዴት ሰይጣን ሆነ ? ብሎ ነው ። መምህር ሲያደርገው ከወላጆቹ እያለቀሰ የተቀበልሁት ያ የፍቅር ብላቴና እንዴት ከፋ ? ብሎ ነው ። ወዳጅ ሲቀጣ ለእኔ መልካም ማድረግ እየቻለ ሌላ ቦታ መልካም መሆን እንዴት አቃተው ? ብሎ ነው ። ቅጣት የተቀጪውን መልካምነት የሚናፍቅ ነው ። የሚከናወነውም በር ዘግቶ ነው ። ምክንያቱም ቀጪው ቢረሳው ጎረቤት የዚያን ሰው ጥፋት አይረሳውምና ። ቅጣት በር ዘግቶ ካልሆነ ጉዳት አለው ። የተናጋን አጥንት የበለጠ ማናጋት ነው ። በርግጥ ሕዝብን የበደለ ከሆነ በሕዝብ ፊት ቅጣት ይተላለፍበታል ። ቢሆንም እንዳይለመድህ ብሎ መግደል የጠላት እንጂ የወዳጅ ግብር አይደለም ።

እንዳይለመድህ የሚለው ቃል ዕድል የሚሰጥ ፣ ነገ ሌላ ሰው ሆነህ ላይህ እፈልጋለሁ የሚል ተስፋ ያዘለ ነው ። እንዳይለመድህ ብሎ መግደል ተገቢ አይደለም ። ዜማቸው መንፈሳዊ የሆነ ግጥማቸው ግን ሰይጣናዊ የሆነ ሰዎች የቀጣነው ለእግዚአብሔር ቤት ቅድስና ብለን ነው ይላሉ ። ያ ሰው በመውደቁ ግን ደስተኛ ናቸው ። ውድቀቱንም ያሰናዱት እነርሱ ሊሆኑ ይችላሉ ። እንዳይለመድህ ሲሉ አገልጋይ ይመስላሉ ፣ ሲገድሉ ደግሞ ከሰይጣን ይከፋሉ ። ወንድሞቻችንን ሰብረናቸው ተሰበሩ ብለን ስናወራባቸው ቅር አይለንም ። እንቅፋት በመንገዳቸው ትክክል አስቀምጠን ፣ የሚያጠምዱ ነውረኛ ሰዎችን ልከንባቸው ሲሰናከሉ በልባችን ደስ እያለን በአፋችን እናለቅሳለን ። ፖለቲከኞች ይህን ክፋት አያውቁትም ። ዓለማውያን እስከዚህ አይጠላለፉም ። በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ያሉ የሰይጣን የውስጥ ካድሬዎች ግን ያመነውን ለማስካድ ፣ የደከመውን ለመግደል በንቃት እየሠሩ ነው ። “አገልግሎት ሕይወቴ ነው ፤ በሕይወቴ የገባውን በሕይወቱ እገባበታለሁ” ብለው ሲናገሩ ሐፍረት አይሰማቸውም ። ክርስቶስ ሕይወታችን ካልሆነ አገልግሎት ሕይወታችን ቢሆንም ከመግደል አንመለስም ። ዛሬ በአገልግሎቱ ዙሪያ ያለው ጠብ የሱቅ ጠብ ነው ። ደምበኛዬን ወሰድክብኝ የሚል ክርክር ነው ። ባለሱቅም አቅርቦቱን ያሻሽላል እንጂ የእኛን ያህል አይጣላም ።

ሐዋርያው ግን “በጌታ ሆኜ እመክራለሁ” ይላል ። ቅዱሳን ሰዎች ሌላውን ሲመክሩ ቀድመው ንስሐ ይገባሉ ፣ ያለቅሳሉ ። “ጌታ ሆይ ፣ እኔ እርሱን ለመምከር ማን ነኝ ? በምክሬ እንዳልሰብረው እርዳኝ” ብለው ተማጽኖ ወደ ተሰቀለው ጌታ ያቀርባሉ ። ማንንም ሰው ሲያዩ የሚታያቸው የሰውዬው ክፋት ሳይሆን እግዚአብሔር ሲፈጥረው በእርሱ ላይ የነበረው አርአያ ሥላሴ ደግሞም የክርስቶስ የደሙ ዋጋ ነው ። ሐዋርያው በጌታ ሆኜ እመክራለሁ ማለቱ ብዙ ፍቺ አለው ። እኔ ሳልሆን የሚመክራችሁ በእኔ ያለው የፍቅር ጌታ ነው ማለቱ ነው ። እኔም በጌታ ምሕረት ተርፌ ለመምከር በቅቼ እመክራችኋለሁ ማለቱ ነው ። በደሌ የተተወልኝ ፣ የኋላ ታሪኬ አሳዳጅ የሆንሁት በክርስቶስ አክናፈ ምሕረት ተሸሽጌ እመክራችኋለሁ ማለቱ ነው ። ዛሬ በምክር ስም የሚሳደቡ ፣ በቅድስና ስም ሌላውን የሚያረክሱ ፣ በትዕቢት ተይዘው እገሌን በሌብነት ያዝሁ የሚሉ ምስኪኖች አሉ ። “ጦጣ ታስራ ትዘፍናለች” ይባላል ። መታሰሯን ረስታ ። እነዚህም በትልቅ ማዕሠረ ኃጢአት መያዛቸውን ረስተው ነጻ ነኝ ብለው ይዘፍናሉ ።

ሐዋርያው የትላንት ኑሮአችሁን የቅድሙን አስተሳሰባችሁን ፣ የቀደመ ጣዖታዊነታችሁን ደግማችሁ አትኑሩት ። ይህች ሰዓት የመለወጥ ዕድል ናትና ተለወጡ እያለ ነው ። እናንተ አሕዛብ ፣ እናንተ ርኵሳን እያለ የቀደመውን ታሪክ የስድብ ርእስ አላደረገባቸውም ። ሰውን የመምከር እንጂ የማስገደድ መብት ማንም የለውም ። መንገድ ማሳየት እንጂ በዚህ ካልሄድህ እንዲህ አደርግሃለሁ የሚባል ሰው ሊኖር አይችልም ። ስለ ድንግል ማርያም ከዘመርህ ይህን ጉድ አወጣብሃለሁ እያሉ የሚያስፈራሩ የዘመናችን የኢየሱስ ፖሊሶች የሚያሳፍሩ ናቸው ። እነዚህ በኢየሱስ ስም አፍሪካን የወረሩ የቅኝ ገዢዎች ልጆች መሆናቸውን እያስመሰከሩ ነው ። በእነዚህ ጨካኞች የወንጌል ሥራ ይጎዳል ። ክርስትናም በክፉ ይታያል ። በእነዚህ ሰዎች የተጎዱ ወደ ዓለም ተመልሰው ክርስትናን ሲበቀሉ ማየት ያሳዝናል ።

ያለፈው አልፏል ። ሰው የሚጠየቀው እውነት ከገባው ሰዓት ጀምሮ ነው ። ከሰማበት ሰዓት ጀምሮ ሳይሆን ከተሰማው ሰዓት ጀምሮ ነው ። እያንዳንዱ ሰዓት የመጀመር ዕድል ነው ። በእልህ መጥፋት የራስን ነፍስ የእኔ አይደለሽም ማለት ነው ። የበደሉንን ሳይሆን ያልበደለንን ጌታ ማሰብ የተሻለ ነው ። ግር እንዳይለን በስንዴው እርሻ ላይ እንክርዳድም አለ ። እስከ መቼ ካልን በቤተ ክርስቲያን ክፉዎች እስከ ዕለተ ምጽአት ይኖራሉ ። ሰው በክርስቶስ ይለካል እንጂ ክርስቶስ በሰው አይለካምና በርቱ ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 12 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ