“እንግዲህ በጌታ እስር የሆንሁ እኔ በተጠራችሁበት መጠራታችሁ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እለምናችኋለሁ፤” ኤፌ 4÷1
በሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ መልእክታት ውስጥ በአዲስ ምዕራፍ ላይ እንግዲህ የሚል ንግግር እናስተውላለን ። ይህ የሚያሳየን ያለፈው ምዕራፍ እንዳላለቀና የአሁኑ ምዕራፍም መጀመርያ እንዳልሆነ ነው ። “እንግዲህ” እና “ነገር ግን” የሚሉ መነሻዎች ሲገጥሙን መልእክቱ ሰንሰለታማ መሆኑን ፣ ያሁኑን ምዕራፍ ለመረዳት ፊተኛውን ምዕራፍ ማየት እንደሚገባን ፣ ዳግመኛም የጀመርነውን ምዕራፍ ጨርሰን ማንበብ እንደሚያስፈልገን የሚጠቁም ነው ።
“እንግዲህ” በሚለው መክፈቻ ከትናንቱ የተቀበልነው እንዳለ ፣ ዛሬም የምንቀጥለው እንጂ የምንጀምረው ነገር እንደሌለ እንረዳለን ። እኔ ከማንም ያልተቀበልኩ ነኝ የሚል አስተሳሰብ ልቡሰ ሥጋ ጋኔን የሚደርግ ነው ። ለትናንት ክብር እንዳይኖረን ፣ የእኛም ነገ ላይ እንዳይከበር የሚያደርገው “እንግዲህ” የሚለው ማያያዣ ሲበጠስ ነው ።
ትናንትም ነገም የሌለው ትውልድ የሚፈጠረው “እንግዲህ” የሚለው ድልድይ ሲሰበር ነው ።
ዛሬ ማዕከላዊ ነች መነሻም መድረሻም አይደለችም ። ሕይወት መግቢያ እና ማጠቃለያ እንዲኖራት “ትናንት” እና “ነገ” ያስፈልጓታል ። ትናንትን ብቻ ማዘከርም ለዛሬ በማይተርፍ ጉራ ውስጥ ያኖራል ፣ ነገን ብቻ ማለትም መንገዱ እንዲጠፋን ያደርጋል ። የምንሄድበት እንዳይጠፋን የመጣንበትን ማስታወስ ግድ ነውና ።
አናሳ ታሪክ ፣ አናሳ ቤተሰብ ፣ አናሳ አገርና አናሳ ቤተ ክርስቲያን የሚፈጠረው ዛሬ ብቻ የሚል ጣዖት ሲመለክ ነው ።
ዛሬ ብቻ የሚል የአራዊት እና የጅቦች ጉባዔ ነው ። “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” አለች አህያ ይባላል። እንዲህ ያለች አህያ አናውቅም ፣ ያሉ ሰዎችን ግን እናውቃለን ። የመጠጥ ስብስብ ፣ የበልተን እንሙቶች ጉባዔ ፣ አባትም ልጅም የለን የሚሉ የአሳብ ምልምሎች ጥርቅም ዛሬን ብቻ ይኖራል ።
ጥርስ ከላይ ከንፈር ፣ ከሥር ምላስ አለው ። ከንፈር ካባ ነው ፣ ያለ ከንፈር የሰው ልጅ አስፈሪ ፍጡር ነው ። ምላስም ከማጣጣም ባሻገር እንደየአቅሙ ይፈጭ ዘንድ ለፊት ጥርስ ቀላሉን ወይም የሚነጨውን ፣ ለኋላ ጥርስ ከባዱን ወይም የሚፈጨውን ምግብ ታደላድላለች ። ምላስና ጥርስ በመልክና በአቅም ቢለያዩም በአንድ ቤት ውስጥ በስምምነት ይኖራሉ ። ዛሬ እንደ ጥርስ ሲሆን ከንፈር ትናንት ፣ ምላስ ደግሞ ነገ ነው ። የትናንት ትውልድ የክብርን ዋጋ ያውቃልና ክብር ይሰጥሃል ፣ የነገ ትውልድ ደግሞ ፈጣን ነውና ይላክልሃል ። ሽማግሌዎች የትናንት ፍሬዎች ፣ የዛሬ ጭማቂዎች ፣ ልጆች የዛሬ አበባዎች የነገ ፍሬዎች ናቸው ።
ትናንት ሰገባው ፣ ዛሬ ሰይፉ ፣ ነገ ድሉ ነው ። ሰገባ ሰይፍን ያበርዳል ፣ የትናንት እውነተኛ ሽማግሌዎችም የሚያስታርቁ ናቸው ። ሰይፍ ተፈሪ ነው። ይከፍላል ፣ ይቆርጣል ፣ ይገርዛል ። በሰይፍ መፈራት እንጂ ክብር ላይገኝ ይችላል ። ዛሬ ኃይለኞች ከሆንን የነገን ድል ለማግኘት መታየትና ማብረቅረቅ ብቻ ሳይሆን ወደ ሰገባው መከተት አለብን ። ትናንት ሥር፣ ዛሬ አገዳ፣ ነገ ፍሬ ነው ። ምንም ባይታይ አገዳውና ፍሬውን የተሸከመው ሥሩ ነው ። “ማን ላይ ቆመሽ ማንን ታሚያለሽ?” እንዲሉ ።
የዛሬዋን ቤተክርስቲያን እና አገር ያስረከቡ ትልልቆች ዋጋ ሲሰጣቸው፣ የዛሬው ትውልድ እኔም ዋጋ አለኝ ብሎ በጎ ለመሥራትና ሌብነትን ለመጸየፍ ይበቃል ። ትናንት የሌለው ዛሬ ፣ ነገ የሌለውን ዛሬ ይፈጥራል ።
የዛሬ ባለትዳሮች የትናንትን እጮኝነት ፣ ነገ ደግሞ በክርስቶስ ወራሾች የሚሆኑበትን እኅትነትና ወንድምነትን ሊያስቡ ይገባል ። ብዙ ጊዜ በእጮኝነት ሁለት ዓይኖች ይከደናሉ ፣ በትዳር ሁለት ዓይኖች ይገለጣሉ ፣ በሽምግልና አንዱ ዓይን ስህተት ሲያይ አንዱ ይጨፍናል ። እጮኝነት የወደደውን መልአክ ማድረጉ ፣ ትዳር ሰይጣን ነው ብሎ መሳሉ ተገቢ አይደለም ። ብስለት ግን ሰውን፣ ሰው ማለት ተገቢ እንደሆነ ያምናል ።
የዛሬ አገልጋይ የትናንት መምህሮቹን ክዶ በቀጥታ ከሰማይ ሰማሁ ቢል ፣ የነገ ደቀ መዛሙርትን ሊያፈራ አይችልም ። የዛሬ ሹም አገር የጀመረችው እኔ ስቀባ ነው ካለ የትናንትናዎቹን እያሳዘነ ፣ የነገዎቹን እየገደለ ይመጣል ። “እንግዲህ” የሚለውን ንግግር የአሁን ትውልድ ሲጠቀመው ብዙ አይሰማም ። ሲመጡ “እንዴት ዋላችሁ?” ሲሄዱ “ደህና ዋሉ” የማያውቁ ትውልዶች “እንግዲህ” የሚለውን መጠቀም አይችሉም ። የትናትናዎቹ ደካማዎች ቢሆኑም የእኛን እንጨምርበት እንጂ እነርሱን በመንቀፍ የራሳችንን ዘመን አንፈጽመው ። “ሙት መውቀስ ድንጋይ መንከስ” እንዲሉ ። ትናንት የሌለው አገር፣ ነገ ብሎ የሚጠራው ሀብት የለውም ።
የተነሣንበትን አሳብ አንዘንጋ ። ሐዋርያው “እንግዲህ” ያለው ምዕራፍ ሦስትን ሲደመድም እግዚአብሔር አብን ፣ እግዚአብሔር ወልድንና ቤተ ክርስቲያንን የሚሞሽረውን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን በማንሣት ነው ። እግዚአብሔር አብ ልጁን ሰጠን ፣ ልጁም ቤተ ክርስቲያንን ሰጠን ፣ መንፈስ ቅዱስም ለቤተ ክርስቲያን ጸጋን ሰጠ ።
“እንግዲህ በጌታ እስር የሆንሁ እኔ በተጠራችሁበት መጠራታችሁ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እለምናችኋለሁ፤” ኤፌ 4÷1።
በዚህ ክፍል ጥሪ የተባለው እምነትም ምግባርም አይደለም። የተመደብንበት የጸጋ ድልድል ነው ። ሁሉም በጸጋው ቢተጋ ጎዶሎዋ ዓለም በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሙሉ ትሆናለች ።
“እንግዲህ” የምንል ያድርገን ።
ዲያቆን አሸናፊ መኮንን
ነሐሴ 7 2013 ዓ.ም