የትምህርቱ ርዕስ | እንግዳ ተቀባይ

 “እንግዲህ ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል፤ … እንግዳ ተቀባይ” 1ጢሞ. 3፡2
እንግዶችን መቀበል ከጥንት ጀምሮ የእግዚአብሔር ሰዎች ተግባር ነው ። ሰዎችን በእንግድነት እንቀበላለን ብለው ራሱን እግዚአብሔርንና ቅዱሳን መላእክትን ተቀብለዋል ። አብርሃም ሥላሴን በቤቱ አስተናግዷል ። ይህም በየዓመቱ ይዘከራል ። ይህ የሚያሳየን እንግዳን መቀበል በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ተግባር መሆኑን ነው ። የተለያየ የቅድስና ተግባር የነበራቸው ሰዎች በቅዱስ መጽሐፍ ታሪካቸው ሰፍሯል ። እግዚአብሔርን በቤታቸው ያስተናገዱ ግን እንግዳ ተቀባዮች ብቻ ናቸው ። እግዚአብሔርን እንቀበላለን ብለው ይህን ተግባር አልጀመሩም ። እግዚአብሔርም በእግዚአብሔርነቱ ግርማ ወደ እነርሱ አልመጣም ። እነርሱ ሰዎችን እየተቀበሉ ሳለ አንድ ቀን ግን እግዚአብሔርንና ቅዱሳን መላእክትን ተቀበሉ ። እግዚአብሔር እንግዳ ተቀባዮችን ይወዳል ። እንግዳ መቀበል በሕገ ልቡና ፣ በሕገ ኦሪት ፣ በሕገ ሐዲስ የጸና ትእዛዝ ነው ። ጻድቁ አብርሃምና ጻድቁ ሎጥ እንግዳ የተቀበሉት በሕገ ልቡና ዘመን ነው ። እንግዳ መቀበል በተፈጥሮ በውስጣችን የተቀመጠ ሕግ ነው ። ያንን ሕግ ካልፈጸምን ደስተኛ ልንሆንና ከራሳችን ጋር ልንስማማ አንችልም ። አብርሃም እንግዳ ተቀባይ ባይሆን ኑሮ እግዚአብሔርን በቤቱ አያስተናግድም ነበር ።

እግዚአብሔር እኛን የሚለካን ለሰዎች ባለን የፍቅር ገጽ ነው ። ለዚህ ነው ሐዋርያው፡- እግዚአብሔርን ማንም ከቶ አላየውም ፤ እርስ በርሳችን ብንዋደድ እግዚአብሔር በእኛ ይኖራል ፍቅሩም በእኛ ፍጹም ሆኖአል ያለው ። 1ዮሐ. 4፡12 ። እግዚአብሔርን ያየው ማንም የለም ፣ እግዚአብሔርን ግን በእንግዶች ላይ ማየት ይቻላል ። የምናየውን ወገናችንን ስንቀበል አንድ ቀን የማናየውን እግዚአብሔር በቤታችን እንቀበላለን ። እግዚአብሔር የልባችን ብቻ ሳይሆን የቤታችንም እንግዳ ሁኖ ይመጣል ። ተዘጋጅተን መጠበቅ ያለብን ለሞት ብቻ ሳይሆን ራሱ እግዚአብሔር ሊመጣ ይችላልና ብለንም ነው ። ጻድቁ አብርሃም እንግዳ ባይቀበል ኑሮ እግዚአብሔር ወደ ቤቱ አይመጣም ነበር ። በቤቱም የተሰማው የሣራ የመውለዷ ተስፋ አይነገርም ነበር ። አብርሃምም ለሎጥና ለሰዶም ሰዎች ምልጃ አያቀርብም ነበር ። ጻድቁ አብርሃም እግዚአብሔርን በቤቱ በመቀበሉ የበረከት በረከት የሆነው እግዚአብሔር ወደ ቤቱ ገባ ። የዛሬ ዓመትም እንደሚወልድ ተስፋ ሰጠው ። ለሎጥም በመማለድ ሕይወቱን አተረፈለት ። ለከተማይቱም መጥፋት ተጨንቆ ጸለየ ። አብርሃም እንግዳ ይቀበል የነበረው የፍቅር ሰው ስለነበረም ነው ። የሀብታቸውን ልክ ለማሳየት ግብር የሚያበሉ መኳንንትና መሳፍንት አሉ ። አብርሃም ግን እንግዳ ይቀበል የነበረው የፍቅር ሰው ስለነበረ ነው ። በዚህም ለሚጠፉ ከተሞች ማለደ ። በሰዶም አልፈረደም ፣ ለሰዶም ሕዝብ ግን ማለደ ። እግዚአብሔር የሰዶምን መጥፋት የነገረው ምሥጢሩን ለወዳጆቹ ስለማይሸሽግና እንዲጸልይም ነው ። የወንድሙ ልጅ ሎጥም ከዚያ ጥፋት የዳነው አብርሃም ስለጸለየለትም ነው ። የሚጸልይለት ወዳጅ ያለው ከጥፋት ያመልጣል ።
ሎጥም ከተማይቱን የሚያጠፉና እርሱን ግን የሚታደጉ መላእክትን በቤቱ ተቀበለ ። ዘፍ. 19፡1-2 ። ሎጥ ምግብና ውኃ ማቅረብ ብቻ ሳይሆን እንግዶቹን ከልጆቹ በላይ ከለላ ሰጥቷቸዋል ። እነዚያ እንግዶች ግን ቅዱሳን መላእክት መሆናቸውን አላወቀም ነበር ። አውቆ ቢቀበል ኑሮ ድንቅ አልነበረም ። የማይቀበል የለምና ። እንግዳ በቤታችን የተማጸነ ነውና ራሳችንን ልንሰጥለት እንደሚገባ ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ይነግሩናል ። ዘፍ. 19፡4-11 ፤ መሳ. 19፡16-24 ። በአገራችን እንኳን ሰውን ግንድን የተማጸነ አይነካም ። እንግዳም የተማጸነ ነውና ሊነካ አይገባውም ።
በማናውቀው አገር ስንሄድ ግራ እንጋባለን ። ቅርቡ ሩቅ ይሆንብናል ። ቀጥሎ ምን ይገጥመን ይሆን የሚል ስጋት ያድርብናል ። ሰዎች ትንሽ ነገር ሲያደርጉልን ትልቅ ያደረጉልን ያህል ይሰማናል ። የከተማውን ሰው ሁሉ ዓይን ዓይኑን እናያለን ። ፍቅርና ስጋት ይቀላቀልብናል ። እንግዶችም እኛ ጋ ሲመጡ ይህ ስሜት ስላላቸው ነው እንግዶችን ተቀበሉ የተባልነው ። እግዚአብሔር አምላክ እስራኤልን ካስጠነቀቀበት አዋጅ አንዱ፡- የወይንህንም ቃርሚያ አትቃርም፥ የወደቀውንም የወይንህን ፍሬ አትሰብስብ ለድሆችና ለእንግዶች ተወው እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝ” የሚል ነው ። ዘሌዋ. 19፡10 ። ዳግመኛም፡- እናንተ በግብፅ ምድር እንግዶች ነበራችሁና ከእናንተ ጋር የሚቀመጥ እንግዳ እንደ አገር ልጅ ይሁንላችሁ ፥ እርሱንም እንደ ራስህ ውደድ እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝ” ብሏል ። ዘሌዋ. 19፡23 ። ይልቁንም ስደትን ያየ ሰው ለእንግዶች ማሰብ አለበት ። ካለን ነገር ላይም ለእንግዶች ሳናስቀር ፈጽመን መብላት የለብንም ። ገበሬ ለዘር ሳያስቀር ፍሬውን ሁሉ አይበላም ። እኛም ለራሳችን ብቻ ማዋል ለቀጣይ ዘር አልባ መሆን ነው ።
የመጨረሻው ቀን ጥያቄ እንግዳ ሆኜ ተቀብላችሁኛል የሚል ነው ። የመጨረሻው ቀን ጥያቄዎች ስድስት ናቸው ። ተርቤ አብልታችሁኛልና፥ ተጠምቼ አጠጥታችሁኛልና፥ እንግዳ ሆኜ ተቀብላችሁኛልና፥ ታርዤ አልብሳችሁኛልና፥ ታምሜ ጠይቃችሁኛልና፥ ታስሬ ወደ እኔ መጥታችኋልና።” ማቴ. 25፡35 ። አንዱ ባንዱ ይናበባል ። እንግዳ የተራበ ፣የተጠማ ፣ የታረዘ ፣ የታመመ ፣ የታሰረ ነው ። እንግዳ ፍቅርን የተራበ ነው ። እንግዳ ሰላምን የተጠማ ነው ። እንግዳ ለአገሩ ባዳ ለሰዉ እንግዳ ነው ፤ እንግዳ ሸፋኝ ዘመድ የታረዘ ነው ። እንግዳ ስሜቱ የታመመ ነው ። እንግዳ ባለማወቅ የታሰረ ነው ። ቅርብ ተጉዞ ሩቅ የሄደ የሚመስለው ነው ። እንግዳን መቀበል ራሱን ጌታን መቀበል ነው ። ይህንን ለጻድቃን ገልጦላቸዋል ። በመጨረሻው ቀን የነገረ መለኮት ጥያቄ የለም ፣ በመጨረሻው ቀን ብሉያትና ሐዲሳትን አመስጥሩ አንባልም ። የመጨረሻው ቀን ጥያቄ እንግዳ ተቀብላችኋል ወይ የሚል ነው ።
ኤጶስ ቆጶስ እንግዳ ተቀባይ መሆን አለበት ። እግዚአብሔርን ወክሎ በቤተ ክርስቲያን የተቀመጠ ነውና ስለ እግዚአብሔር ሁኖ እንግዳ መቀበል አለበት ። ቤተ ክርስቲያን የእንግዶች ማረፊያ መሆኗን የደጉ ሳምራዊ ታሪክ ይነግረናል ። ሉቃ.10፡34 ። ትልቁ ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ እርሳቸውን ለመክሰስ የመጡትን በቤታቸው እንግድነት አስቀምጠው በችሎት ደግሞ ይዳኙ ነበር ።በቤተ ክርስቲያን ለጥምቀት እየተሰናዱና እየተማሩ ያሉ ንዑሰ ክርስቲያን እንግዶች ናቸው ። ኤጲስ ቆጶስ ሊቀበላቸው ይገባል ። ሕፃናት እንግዶች ናቸው ። በዓለም በረሃ ሲማስኑ የኖሩ እንግዶች ናቸው ። አግኝተው ያጡ ሰዎች እንግዶች ናቸው ። ኤጲስ ቆጶስ እነዚህን ሁሉ መቀበልና እንደ ፍላጎታቸው ማርካት ይጠበቅበታል ።
ከምንረሳቸው ነገሮች አንዱ ይህ ነውና ሐዋርያው፡- እንግዶችን መቀበል አትርሱ፤ በዚህ አንዳንዶች ሳያውቁ መላእክትን እንግድነት ተቀብለዋልና” አለ። ዕብ. 13፡1 ።
በእንግዳ ምክንያት በትዳራቸው ላይ ጭቅጭቅ የሚያስነሡ ወገኖች አሉ ፤ አለማወቃቸው በረከታቸውን አሳልፈው ሰጥተዋል ። አንድ ቀንም እነርሱ እንግዳ ሁነው እንደሚሄዱ ረስተዋል ። ይልቁንም ይህን ዓለም ለቀን ስንሄድ በሰማይ እንግዶች ነንና በዘላለም ማረፊያው እንዲቀበለን እኛም በታማኝነት እንግዶች እንቀበል !
በረከቱን ያድለን !
1ጢሞቴዎስ 38
ጥር 13 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም