መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » እውነቱ የት ነው ?

የትምህርቱ ርዕስ | እውነቱ የት ነው ?

“ሀብታም ይደኸያል ፣
ሐኪምም ይሞታል ፣
ጎበዝ ይሸነፋል ፣
ብልህ ይሳሳታል ፣
የበራውም ጠፍቶ ፣
የሠሩት ይፈርሳል ፣
ጌጥም ሆነ ጥበብ ፣
ውበት ሆነ ክብርም ፣
ያማረበት ነገር ፣
ማስቀየሙ አይቀርም ።

እስካሁን የማይቀር ነገር ቢኖር ሞት ነው ። ሌሎች ነገሮች በምናልባት ላይ የተንጠለጠሉ ናቸው ። ሞት ግን እርግጥ ነው ። የመቃብር ስፍራዎችን ቢያንስ በወር አንድ ቀን መጎብኘት መልካም ነው ። ብዙ ያስተምረናል ፣ ትሑት ያደርገናል ። መንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ብንሄድ ከቆመው ኃያል የሞተው ኃያል ፣ ካለው ምሁር መቃብር ያለው አዋቂ እንደሚበዛ እንረዳለን ። በዋናው በር ስንገባ ፊት ለፊታችን ሦስት ፓትርያርኮች ዐርፈዋል ። ከጀርባው ከቤተ ልሔሙ በስተቀኝ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ዐርፈዋል ። ትልቁ ማዕረግ ጵጵስና ነው ። እርሱ አይበቃንም ብለው ፓትርያርክ  ለመሆን ይመኙ የነበሩ ፣ በተሰጣቸው ሳይደሰቱ ያለፉ ይኖራሉ ። ግን ፓትርያርክም ጳጳስም በዚህ ስፍራ ዐርፈዋል ። በዋናው በር ስንገባ በስተቀኛችን ሦስት ጠቅላይ ሚኒስትሮች በስተግራችን አንድ ጠቅላይ ሚኒስትር በመካነ ዕረፍት ውስጥ አሉ ። ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተ ወልድና ጠቅላይ ሚኒስትር ልጅ እንዳልካቸው በግፍ ተገድለው ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ ከሹመት በኋላ ሃያ ዓመት ታስረው አሁን በዚህ ስፍራ ዐርፈዋል ። ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም በዚህ ስፍራ ተወስነዋል ። ደራሲ ከፈለግን ከዋናው በር በስተቀኝ ሐዲስ ዓለማየሁና ማሞ ውድነህን እናገኛለን ። እውቅ ዲፕሎማቶች ፣ የታወቁ የጦር ጀግኖች በዚህ ስፍራ አሉ ። ዓለም ኃላፊ ነው ። አለሁ ያለም አንድ ቀን አይኖርም ። የሁልጊዜ ባለሥልጣንና ጀግናም አይኖርም ። ጠባቂ ሁሉ ሞትን መመለስ አይችልም ። ሐኪምም ለራሱ አያውቅም ። አገር እየቆረሰ ይሰጥ የነበረ በሦስት ክንድ ከስንዝር መሬት ተወስኗል ። መሬት ሊረግጥ ይጸየፍ የነበረ ከመሬት በታች ውሏል ። የወርቅ ልብስ ይለብስ የነበረ ድንጋይ ተጭኖታል ። ሲመጣ መንገድ ያዘጋ የነበረው አሁን አጠገቡ ልጆች ተቀምጠው ይጫወታሉ ፣ ማን መሆኑም አይታወቅም ። ጎብኚዎችም ብዙ ተነግሯቸው ማንነቱን መረዳት አይችሉም ።

በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና በቤተሰባቸው ያልተሰየመ ከተማ ፣ ያልተሰየመ ተቋም አልነበረም ። ዛሬ ግን አንዱም የለም ። የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩንቨርስቲ አሁን አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ተብሏል ። ተፈሪ መኰንን ይባል የነበረው ዛሬ እንጦጦ ቴክኒክ ት/ት ቤት ተብሏል ። የልዑል መኰንን መታሰቢያ ሆስፒታል ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ተብሏል ። ልዕልት ፀሐይ ሆስፒታል ዛሬ የጦር ኃይሎች ሆስፒታል ተብሏል ። ልዕልት ዘነበ ወርቅ ሆስፒታል አለርት ተብሏል ። ዐስበ ተፈሪ ይባል የነበረው ከተማ አሁን ጭሮ ተብሏል ። ዛሬ ላይ የምንኖርለት ስማችን ፣ የምንጋደልለት ክብራችን አንድ ቀን ይሻራል ። የደመቅንና የማንረሳ ሲመስለን እንረሳለን ። እንደ ነበረ ያለ ፣ እንዳለም የሚኖር ምንም ነገር የለም ። በዚህ ሁሉ ውሸት ውስጥ የደከመው ማንነታችን እውነት የት ነው ? ይላል ።

ለዘመናት የዘለቁ ፓርቲዎች የምዕራቡ ዓለም የልብ ኩራት ናቸው ። ሪፐብሊካንና ዲሞክራት የሚባለው የአሜሪካ ሁለት ፓርቲ ሦስተኛም ሲጨምር አይታይም ። ወጣትም አይመርጥም ። ታዲያ ሁለቱም ፓርቲ አንድ ዓይነት ሲሆን የተለያየ ጨዋታ ለአገሩ የሚጫወት ነው ። ያቺን አገር ማንም የዓለም ሕዝብ እንዳይወቅስ ዕዳውን ፓርቲዎቹ ይሸከማሉ ። አንደኛው የሚያስፈልገውን ስደተኛ በገፍ ያስገባል ፣ ሁለተኛው እያገደ ያበርዳል ። አንደኛው ብዙ ባጀት በመባጀት ገንዘብ ይበትናል ፣ ሁለተኛው ሲመጣ ይቆጥባል ። እንዲህ እያጫወቱ ይቀጥላሉ ። ታዲያ ለዘመናት የዘለቁ ፣ ተተኪ ፖለቲከኞችን ያፈሩ ፓርቲዎች ይፈራሉ ። በቻይናም የኮሚኒስት ፓርቲው የአገሩ ሕዝብ አምላክም ፣ ቤተ ክርስቲያንም ተደርጎ ይታሰባል ። እነዚህ ሁሉ ሐረገ ትውልዶች እውነትነት የላቸውም ። አንድ እውነተኛ አለ ። እርሱም ሐረገ ወይን ኢየሱስ ክርስቶስ ይባላል ። እውነት ነውና ደስ ያሰኛል ። እውነት ነውና ምዕራፍ ይሰጣል ። እውነት ነውና ከፍለጋና ከመንከራተት ያድናል ። ወይን ግንዱ አያምርም ፣ ቅጠሉና ፍሬው ግን ያምራል ። ባየነው ጊዜ እንወደው ዘንድ ደም ግባት ያልነበረው ፍሬው ግን የጣዕም አውራ የሆነው ፣ ዘንካታው ፣ ከሰማይ እስከ ምድር የተዘረጋው የአብ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። የሚቆይ ነገር ለፈለጋችሁ የነበረውም የሚኖረውም እግዚአብሔር ብቻ ነው ።

እርሱ ራሱ፡- “እውነተኛ የወይን ግንድ እኔ ነኝ ፤ ገበሬውም አባቴ ነው ።” ብሏል ።

ተሸክመንህ የምንዞረው ወንጌል ኢየሱስ ፣ የተሸከምከን ኃያል መሢሕ ምነው እንዲህ በርተህ ፍጥረት አላወቀህም ? በገዛ ቤትህ ፣ በገዛ ዓለምህ እንደ ባይተዋር ለምን ተገፋህ ? አለሁ እያሉ ብዙዎች ጠፉ ፣ መጣሁ እያሉ ብዙዎች ቀሩ ። አንተን እውነት የሆንከውን ፣ ከምሰሶ ይልቅ ቤትን ያጸናኸውን አለመውደድ ምንኛ መበደል ነው ! አንተ የአብ ጸዳል እባክህ ብራ ፣ እባክህ አብራ ፣ እባክህ ፍቅር ይብራ ። ነፍስ ሁሉ አውቃህ በብርሃንህ ትጋረድ ። ለብሰን የተራቆትን ፣ አግኝተን ያልረካን ነንና አሁን አድነን ። እስክትመጣ እስክንመጣ በሰላም አኑረን ። አሜን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 16 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም