የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ የዓለማችን፣ የኢትዮጵያና የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ ባለውለታ ናቸው…!!

                  በፍቅር ለይኩን፡፡ (fikirbefikir@gmail.com)

                                                                            ቤተ ጳውሎስ፤ ረቡዕ፣ ሚያዚያ 10 2004 ዓ.ም.
እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ በ80 ዓመታቸው ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ ማታ በጭጓራ ካንሰር ምክንያት ከዚህም ዓለም በሞት መለየታቸውን የሰማሁት በድንጋጤና በሐዘን ውስጥ ሆኜ ነበር፡፡ በቅርብ ጊዜያት ውስጥ በኢትዮጵያ ስነ ጹሑፍ ውስጥ እጅግ ትልቅና ልዩ ስፍራ ያላቸውን ሰዎችን አጥተናል፤ ዛሬ ደግሞ በስነ ጥበብ ሀገራቸውን በዓለም መድረክ ያስጠሩትን ታላቅና ዓለማቀፋዊ ሰው ኢትዮጵያ ተነጥቃለች፡፡
እኚህን ታላቅ ሰው ለመጀመሪያ ጊዜ በአካል ለማየትና ንግግራቸውንም ለመስማት የታደልኩት በፋሽስት ኢጣሊያ ተዘርፎ ለ60 ዓመታት በሮማ አደባባይ ተተክሎ የቆየውን የአክሱም ሀውልት የማስመለስ የመጨረሻ ሂደትን አስመልክቶ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም የዩኒቨርስቲው ማኅበረሰብ፣ የታሪክ ተመራማሪዎች፣ የቅርስ ባለሙያዎች፣ የአርክቴክቸርና የምንህድስና ባለሙያዎች፣ ከባህልና ቱሪዝም ሚ/ር እና ከቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን የመጡ ከፍተኛ ባለስልጣኖች፣ የውጭ ሀገር ምሁራንና የቅርስ ተቆርቋሪዎችና ባለአደራዎች በተገኙበት በረከት ያሉ የጥናት ወረቀቶች በቀረቡበት ወቅት ነበር፡፡
ታዲያ በዚሁ ዕለት በቀረቡት የጥናት ወረቀቶች ላይ ከተሳታፊዎችና ከተጋባዥ እንግዶች ጋር ውይይት ተደርጎ ነበር፡፡ በዕለቱ በስብሰባው ላይ ተሳታፊ የነበሩት እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ስለ አክሱም ሀውልትና እንዲሁም በአውሮፓና በአሜሪካ በተለያየ ምክንያት ወጥተው ስለሚገኙ ቅርሶቻችንና የጥንት የብራና መጻሕፍቶቻችን በሰጡት አስተያየት እንዲህ ብለው ነበር፡-
በሀገራችን ኢትዮጵያ ለታሪክና ለቅርስ ያለን ግንዛቤና የምንሰጠው ዋጋ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡ ለዚህ ዓላማ የተቋቋሙ የመንግሥት ተቋማትም እምብዛም የተደራጀ፣ የተማረ የሰው ኃይልና ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የላቸውም፡፡ ዘመናኛው ትውልድም ለሀገሩ ቅርስና ታሪክ ያለው ስሱነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየደበዘዘ ነው፡፡ እኔ በግሌ በትምህርትና በሥራ በቆየሁባቸው በአውሮፓና በአሜሪካ በሚገኙ ታላላቅ ዩኒቨርስቲዎች፣ ቤተ-መጻሕፍቶች፣ ቤተ-መዘክሮችና ጋለሪዎች በተለያዩ ጊዜያት ከሀገራችን ተዘርፈው የተወሰዱ ቅርሶቻችንን በተለይም ደግሞ በርካታ ዕድሜን ያስቆጠሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የጥንት የብራና መጻሕፍቶቻችንን ለማየትና ለመመርመር ዕድሉን አግኝቼያለሁ፡፡ በዛ በሚደረግላቸው እንክብካቤና ልዩ ጥበቃም በእጅጉ ተደንቄያለሁ፤ በአንፃሩ ግን መለስ ብዬ  ደግሞ ሀገሬና ሕዝቤ ለእነዚህ የቀደሙ አባቶቻችን በብዙ ድካምና ልፋት የተዘጋጁና በብዙ ተጋድሎም ለትውልድ የተላለፉ ቅርሶቻችን ተገቢ የሆነው ጥበቃና እንክብካቤ ሳይቸራቸው የአቧራና የአይጥ መጫወቻ ሆነው ሳይ እነዚህ በውጭ ሀገራት ያሉት ቅርሶቻችን በዛው እንዳማረባቸው ተጠብቀው ቢቆዩና ባይመለሱስ ምናለበት ስል ራሴን እጠይቃለሁ… በማለት በቁጭትና በኢትዮጵያዊነት ብሔራዊ ስሜት የሰጡት አስተያየት ዛሬም ድረስ ትዝ ይለኛል፡፡
እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ እንደ ኢትዮጵያዊ ምሁርና የጥበብ ሰው በጥንታዊት ኢትዮጵያ ታሪክ፣ ነጻነት፣ ባሕልና ሥልጣኔ እንዲሁም በግዕዝ ቋንቋ፣ ጥንታዊትና ሐዋርያዊት በሆነችው በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖታቸው፡- እምነት፣ አስተምህሮ፣ ትውፊትና ስርዓት በእጅጉ የሚኮሩ ብቻ ሳይሆኑ ጠንቀቀውም የሚያውቁ የታሪክ ሰው፣ ቅርስ ተቆርቋሪና ጠባቂ፣ የኢትዮጵያችን የባሕል አምባሳደር እንደነበሩ በቅርብ የሚያውቋቸው ሁሉ የሚመሰክሩላቸው ነው፡፡ ለኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖታቸው የነበራቸውን ጥልቅ ፍቅርና ክብር ከገለጹባቸው መካከልም የአራዳው ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የመቅደሱ ግድግዳዎች የተዋቡት የጥበብ ትሩፋታቸው በዋናነት የሚጠቀስ ነው፡፡ እኚህን ዓለማቀፋዊና ታላቅ የጥብብ ሰው የቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ ባለውለታ ናቸው ማለቴም ለዚህ ነው፤ ስለሆነም ስራዎቻቸው ሊዘከሩና ትውልድ በሚገባ እንዲያውቃቸው ለማድረግ የእኛ ቤተ ክርስቲያኒቱ ወጣት ትውልድ መንፈሳዊ ኃላፊነትና ግዴታ እንደሆነ ይሰማኛል፡፡
ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ በሀገራቸውና በአውሮፓ ለረጅም ዓመታት የሥነ ጥበብ ሙያን የተማሩ ሲሆን በሀገራቸውና በዓለም አቀፍ ደረጃም በተለያዩት ጊዜያት በርካታ የስዕል አውደ ርዕዮችን በማቅረብ ትልቅ አድናቆትንና ክብርን ለመጎናጸፍ ችለዋል፡፡ በዚህ ልዩ ተስጥዖቸውና ችሎታቸው የተነሳም በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች ከሚገኙ ታላላቅ የጥብብ ሰዎች ጋር ለመገናኘትና ስራዎቻቸውንም ለሌሎች ለማሳወቅ ችለዋል፡፡ በስነ ጥበብ ስራዎቻችውም ለዓለማችን ሰላምን፣ ለሰው ልጆች አንድነትና እኩልነትን በመስበካቸውም በዓለማችን ከሚገኙ ታላላቅ መሪዎችና ፖለቲከኞች፣ ታዋቂ ሰዎችና የሃይማኖት አባቶች ጋር ለመገናኘት የቻሉ ዓለማቀፋዊ ዝናን እና ክብርን ያተረፉ የሥነ ጥበብ ሰው ነበሩ፡፡
ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የስነ ጥበብ ከፍተኛ ሽልማት ጀምሮ በሀገር ውስጥና በዓለም አቀፍ ደረጃ ከ90 በላይ የሚሆኑ ሜዳሊዎች፣ ሽልማቶችንና ዲኮራሲያኖችና የክብር ዜግነት ያገኙ ሰው ሲሆኑ፤ ለአብነትም በሐምሌ ወር 1997 ዓ.ም በአየርላንድ ዋና ከተማ በዱብሊን በተደረገው በ30ኛው የኪነ ጥበብ የባሕልና የሳይንሶች ዓለማቀፋዊ በዓል ላይ The International Biographical Center of Cambridge በስነ ሙያ ጥበብ የመጨረሻ ሽልማት የሆነውን Davinci Diamond የደቬንቺ አልማዝ የተባለውን ሽልማት ሰጥቷቸዋል፡፡
ይህንን ሽልማት በማግኘትም ብቸኛው አፍሪካዊ የሥነ ጥበብ ሰው ለመሆን በቅተዋል፡፡ በዚሁ በዓል ላይም The United Cultural Convention of the United States of America ለእኚሁ ታላቅ ሰው International Peace Prize ልዩ ሽልማትና፣ የክብር የሰላም አምባሳደርነትን ሰጥቷቸዋል፤ ይህም ሽልማትና የክብር ዲፕሎማ በዘር፣ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ፣ በባሕል በተከፋፈለች ዓለማችን ለዓለም ሰላምንና ፍትህን፣ ለሰው ልጆች እኩልነትንና አንድነትን ለማስፈን ለሚጥሩ ሰዎች የሚሰጥ ዓለማቀፋዊ ሽልማት እንደሆነ የድርጅቱ ኃላፊዎች በሽልማቱ ወቅት ገልጸው ነበር፡፡ ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌም በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ካገኟቸው በርካታ ሽልማቶች መካከል እነዚህ ለሁለቱ ዓለም አቀፍ ሽልማቶች ልዩ ክብርና አድናቆት እንደላቸው ገልጸው ነበር በአንድ ወቅት ስለዚሁ ሽልማታቸው በተደረገላቸው ቃለ መጠይቅ፡፡
እኚህ ታላቅ የጥበብ ሰው አጭር የሕይወት ታሪክ ከልጅነት ጀምሮ ጓደኛቸው በሆኑት በፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት በአማርኛና በእንግሊዘኛ ‹‹አፈወርቅ ተክሌ አጭር ሕይወት ታሪክና ምርጥ ስዕሎቹ›› በሚል ርዕስ ባቀረቡት መጽሐፍ መግቢያ ላይ አስተያየታቸውን ያሰፈሩት በደርግ ዘመነ መንግሥት የባሕልና የስፖርት ጉዳይ ሚ/ር የነበሩት ሻለቃ ግርማ፡- ‹‹የሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ምርጥ የሥዕል ሥራዎች በሺህ ዓመታት አንዴ ብቅ እንደሚሉ የፈጠራ ሰዎች ውድና ብርቅ የሥነ ጥበብ ውጤቶች ናቸው፡፡ አብዛኛዎቹ ሥዕሎቻቸው ጠንካራ የሀገር ፍቅር ስሜትና የተፈጥሮ ውበትን ሕያው በሆኑት ታዋቂ ሥራዎቻቸው አንጸባርቀዋል፤ በጥንታዊነቷና በታሪካዊነቷ በርካታ የምርምርና የጥናት ሰዎችን ለምትስበው እናት ኢትዮጵያ የሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ምርጥ የሥነ ጥበበብ ሥራዎች ተጨማሪ ጌጥና ኩራት ናቸው፡፡›› ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተው ነበር፡፡
እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ በዚች የነገሥታት መናገሻና መዲና በነበረችውና አሁን በተረሳችው አንኮበር ተወልደው እንዴት ለእዚህ ዓይነት ዓለማቀፋዊ እውቅና እና ዝና ሊደርሱ እንደቻሉ በተጠየቁበት በአንድ ወቅት እንዲህ በማለት መልሰው ነበር፡- ‹‹አገራችን በብዙ ነገሮች ቀደምት በመሆኗ እንደምትታውቅና እንደምትደነቅ ሁሉ እኔም በዚህ የሙያ መስክ የአገሬን ስም እንዳስጠራ የኢትዮጵያ አምላክ ፈቃድ የሆነ ይመስለኛል፡፡›› በማለት እጅግ ከፍተኛ ትህትና እና የሀገር ፍቅር ስሜት ባለው ሁኔታ መልሰዋል፡፡
ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ በሀገራችን በኢትዮጵያና በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቁባቸው በርካታ የስነ ጥበብ ስራዎች አሏቸው፤ ከእነዚህም መካከል ‹‹እናት ኢትዮጵያ›› በሚል የሳሉት ስዕላቸው ስራዎቻቸውን እንዳጠኑ አንዳንድ ሰዎች የዚህ ስዕል መነሻ የሆናቸው በተለያዩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናትና ገደማት የሚገኙት የቅድስት ድንግል ማርያም ምስለ ፍቁር ወልዳ ስዕል እንደሆነና በልጅነታቸው ሀ ሁ የቆጠሩባትና በጥምቀት የሥላሴን ልጅነት ያገኙባት ቤተ ክርስቲያን በእናት ፍቅር አምሳል ምን ያህል በውስጣቸው ተስላ እንደቀረች የጠቆሙበት እንዲሁም ለእናት ምድራቸው ያላቸውን ሕያው ፍቅር በበሩሻቸው የገለጹባት ድንቅ ሥራቸው እንደሆነ አስተያየት ይሰጣሉ፡፡
እንዲሁም አፍሪካውያን ከቅኝ ግዛት ቀንበር ስር ለመውጣት በሚያደርጉት የሞት ሽረት ትግል የነጻነትና የአይበገሬነትና የጥቁር ሕዝቦች ነጻነትና አይበገሬነት ልዩ መገለጫ በሆነችው ኢትዮጵያ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲቋቋም የአፍሪካውያንን ታላቅ ስልጣኔ፣ አኩሪ ባሕል፣ ታሪክና ነጻነት በበሩሻቸው ቀለም በድርጅቱ መስብሰቢያ አዳራሽ እውን ያደረጉት እኚሁ ታላቅ የጥበብ ሰው ነበሩ፡፡ በድርቅ፣ በጦርነትና በረሃብ የተጎሳቆለችውን እናት ሀገራቸውን ኢትዮጵያን በብሩሻቸው የገለጹበት ‹‹ዋይ ዋይ የት ትሄዳለህ›› የሚለው የጥበብ ስራቸውም በሀገራችን በወቅቱ በደረሰው አሰከፊ ድርቅና ረሃብ የደረሰባቸውን የልብ ስብራትና ጥልቅ ሐዘን የገለጹበት ስራቸው ነው፡፡ በአራዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ የሚገኙ የእሳቸው የእጅ አሻራ ያረፈባቸው መንፈሳዊ ስዕሎችም ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ባለውለታ መሆናቸውን ሚጠቁሙና ለእምነታቸው ያላቸውን ልዩ ፍቅርና ክብር የገለጹበት ሌላው የሚጠቀስ የጥበብ ትሩፋታቸው ነው፡፡
የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት እንደገለጸው እኚህ ታላቅ የጥበብ ሰው ሥራዎቻቸው ሁሉ የኢትዮጵያና የኢትዮጵያውያን ሁሉ ነው ብለው በተናዘዙት መሠረት አልፋ ተብሎ በሚጠራው መኖሪያቸውና የጥበብ ሥራዎቻቸው ቤተ መዘክር እስከ ሕይወታቸው ፍጻሜ ድረስ የተጠበቡባቸውን ሥራዎቻቸውንና እጅግ ድንቅና ልዩ በሆነ ኢትዮጵያዊ የሥነ ሕንጻ ጥበብ የተሰራውን አልፋ ስቱዲዮአቸው መጎብኘት የምንችልበት ዕድል ለወደፊት እንደሚፈጠር አሳባለሁ፡፡ የእኚህን ታላቅ የጥበብ ሰው ነፍስ እግዚአብሔር ከአብርሃም፣ ከይስሐቅና ከያዕቆብ አጠገብ ያኑርልን!
ሰላም! ሻሎም!   
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ