መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት

የትምህርቱ ርዕስ | እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት

እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ታዋቂ እንጂ አዋቂ አያደርግም ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት የሥጋ ጫናን እያቀለለ ነፍስን ግን በሸክም ያጎብጣታል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ብዙ የማያውቁ ሰዎችን ለጥፋት ያነሣሣል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት የዘመናትን ችግር ለወገን ያመጣል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ብዙዎችን መምራት ሳይሆን መንዳት ይፈልጋል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ሌሎችን ለመሥዋዕትነት እያስተማረ እርሱ ግን ይዘገያል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት እርስ በርስ በመጠፋፋት ይደመደማል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት በጅምላ ትውልድን ይጨርሳል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ለጥፋቱ ድንበር የለውም ። ይህችን ዓለም እያስጨነቋት ያሉት ካልተማሩት ይልቅ ፊደል የቆጠሩት ናቸው ። የዓለማችን ሀብት በጥቂት ሰዎች እጅ እንዳለ ሁሉ የዓለማችን ሰላምም በጥቂቶች ክፋት ይታወካል ። ተምረው የደነቆሩና ያልተማሩ ሰዎች የዓለምን ዕድሜ ለማሳጠር በኅብረት ይሠራሉ ።
ምድራዊ እውቀት አስተዳደግን ያጠነክራል እንጂ አይለውጥም ። ምድራዊ እውቀት የማይታወቁና የማይዳሰሱ ጓደኞችን ሲያመጣ ሲጩኹ የሚደርስ ጎረቤትን ግን ያሳጣል ። ምድራዊ እውቀት ሕግን ሲያስከብር ፍቅርን ግን ያስወጣል ። ምድራዊ እውቀት ለዛሬው ዋጋ ሲሰጥ የትላንትን ግን እንዳልነበር ያደርገዋል ።
በዘረኝነት ያደገ ሰው እውቀት የበለጠ ዘረኛ ያደርገዋል ። ያልተማረ ሲገድል የተማረው ደግሞ ጥይት ያመርታል ። ያልተማረ ሲተኩስ የተማረ ደግሞ የባከነውን ጥይት ከሟች ቤተሰብ ይጠይቃል ።
እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ከራስ ጋር ያጣላል ። ብዙ ሱሰኞች የሚወለዱት ከእውቀት ስፍራ ነው ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ሞቶ መኖር ነው ። እግዚአብሔር የማይከብርበት እውቀት እምነት ሳይሆን ስሌት ያለበት ነው ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ትዕቢት እንጂ ትምህርት አይሰጥም ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ኀዘነተኛ የሚያደርግ ነው ። እግዚአብሔር በሌለበት እውቀት ውስጥ ብስጭት አለ ። አእምሮንም እውቀትንም የሰጠውን እግዚአብሔርን የማያከብር እውቀት ተሳዳቢ ያደርጋል። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት አመንዝራ ወይ ተቺ ያደርጋል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ግለኛ እንጂ ማኅበራዊ አይደለም ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ያልተማሩትን እንደ ፈጠራቸው አድርጎ ያስባቸዋል ። ስለዚህ ጦርነትን እየቀመረ ይሰጣቸዋል ። እግዚአብሔርን የማያውቅ እውቀት ሁሉንም ነገር የሚተምን ለገንዘብ እንጂ ለኅሊና እርካታ የማይኖር ነው ። እግዚአብሔርን የማያውቅ እውቀት ወላጅን የሚዳፈር ፣ “ምን እሰጣለሁ ?” ሳይሆን “ምን እቀበላለሁ ?” ብሎ የሚኖር ነው ።
እግዚአብሔርን ሳያውቁ የዓለምን እውቀት የሚያውቁ ሰዎች ክፋትና ስስት ያጠቃቸዋል ። ለድሆች ከማዘን በሚሰጥ ሰው ይበሳጫሉ ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት የሽማግሌን ገጽ የማያፍር ፣ ንጉሥን የማያከብር ፣ እግዚአብሔርን የማይፈራ ነውና በሁለት ሰይፍ የሚቀጣ ነው ። እግዚአብሔርን ገሸሽ ያለ እውቀት ግዙፍ ሰይጣን የሚያደርግ ነው ። ከባሕር አሸዋ የበዛ ፣ ከሰማይ ሰሌዳ የሰፋ እውቀት የነበረው ሰሎሞን ከአምልኮተ እግዚአብሔር ሲለይ እውቀቱ ሳያድነው ወድቋል ። እግዚአብሔርን ገሸሽ የሚል እውቀት እኔን ይድላኝ እንጂ ለትውልድ ደንታ የለኝም ይላል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ለእልህ ብቻ ይኖራል ። እውቀት ብቻውን አይለውጥም ፣ ምድራዊ ፍልስፍና ኃጢአትን ቀላልና ምክንያታዊ ያደርጋል። ራስንም ይቅር ማለት ይለማመዳል ። እግዚአብሔር የሌለበት እውቀት ጸጸት የሌለበት ነው ። ጥፋቱም ረቂቅና ትውልድን የሚበክል ነው ። ያልተማሩ ሰዎች የሚጣሉት ለዕለት ነው ፣ አዋቂ የሚባሉት ግን የመቶ ዓመት የቤት ሥራ ጥለው የሚሄዱ ናቸው ። ያልተማሩ የሚባሉት ጠባቸው ከግለሰብ ጋር ነው ፣ አዋቂ የሚባሉት ግን ከአገርና ከትውልድ ጋር የሚጣሉ ናቸው ።
እግዚአብሔርን ማወቅ መሠረት መሆኑን ረስተህ ችላ አልከው ። ዛሬ ሁሉን ጨብጠህ ደስታ የምታጣው መሠረት የሌለው ቤት ስለሠራህ ነው ። እግዚአብሔርን ነፍገህ ለልጅህ ምድራዊ እውቀትን ብቻ ሰጠኸው ፣ ልጅህን ግን አጣኸው ። ያንተ ስም እንዳይሰደብ ብቻ ልጅህን በሥነ ሥርዓት አስጨነቅኸው ፣ ነጻ ሲወጣ ግን የታመቀ ኃጢአቱን አፈነዳው ። እግዚአብሔርን ማወቅና ማፍቀር ብታስተምረው ልጅህ እስከ ሞትህ ድረስ ያንተ ይሆን ነበር ። ከእግዚአብሔር ነጥሎ ልጅን እውቀት ጋ መሸሸግ የሚያፈስ ጣራ ውስጥ ማስጠለል ነው ። እግዚአብሔርን ማወቅ ከትምህርት ቤቶች ውስጥ እንዲወጣ ተደረገ ። ለራሱ ጌታ መሆን አቅቶት ይኸው ትውልድ ወደቀ ። ስለ እግዚአብሔር መናገር ፈሪ ትውልድ ማምረት ነው ፣ ሃይማኖትም አደንዛዥ ዕፅ ነው ተባለ ፣ ይኸው በምድር ላይ ካጋጠሙን አራዊቶች በጥቂት የሚለዩ ልጆችን አፈራን ።
በዕድሜ ውስጥ የሚያስፈሩ እግዚአብሔርን የማይፈሩ ናቸው ። እግዚአብሔርን የማይፈራ ሰው ለክፋቱ ከልካይ የለውም ። የተፈራራ ማኅበረሰብን መፍጠር ይቻላል ፣ የሚፋቀር ማኅበረሰብን መፍጠር ግን ልዩ እውቀት ይጠይቃል ።
እግዚአብሔር ማወቅ ፀሐይ ነው ፣ ምድራዊ እውቀት ሻማ ነው ። ፀሐይ በዳርቻ ሁሉ ትሰለጥናለች ፣ እግዚአብሔርን የሚያውቅ በሁሉ ቦታ ውድ ነው። ፀሐይ ለሁሉ ታበራለች ፣ እግዚአብሔርን ማወቅ ከዘረኝነትና ከራስ አጥር የሚያወጣ ነው ። ፀሐይ በነጻ ታበራለች ፣ እግዚአብሔርን የሚያውቅ ለአገሩ ለወገኑ መሥዋዕት ይሆናል ። ፀሐይ ለራስዋ አታበራም፣ እግዚአብሔርን የሚያውቅም ከእኔነቱ ይድናል ። ፀሐይ ጨለማን ታሸንፋለች ፣ እግዚአብሔርን የሚያውቅም ፍላጎቱን ያሸንፋል ። ፀሐይ ስትወጣ አራዊትና ሽፍታ ይገባል ፣ እግዚአብሔርን ማወቅ ሲመጣ የትውልድ ሸለፈት ይገረዛል።
የጥበብ መዝገብ የሆነውን ክርስቶስን የማያውቅ ፣ እንዴት አዋቂ ይባላል ? እግዚአብሔርን ማወቅ ያለበት እውቀት ብዙ ከመናገር ብዙ ይሠራል ። ችግርን ከማድነቅ ወደ መፍትሔ ይፋጠናል ። ዘመኑ አጭር መሆኑን ተረድቶ ለትውልድ አንድ ነገር ያበረክታል ። መማር የሚለው ቃል ሁለት ትርጉም አለው ፡- አንደኛ፣ ማወቅ ሲሆን ሁለተኛ፣ ምሕረት ማግኘት ነው ። እግዚአብሔርን ማወቅ ምሕረት ማግኘት ነው ። ምሕረት ያገኘ እውቀትም ሌሎችን የሚወድና የሚያፈቅር ነው ። እግዚአብሔርን ማወቅ ያለበት እውቀት ራስን መግዛት ያለው ነው ። ሰላም አግኝቶ ሰላም የሚሰጥ ነው ። ክፉውን ወደ በጎ በሚለውጠው እግዚአብሔር የሚደሰት ነው ። እያወቀ እንዳላወቀ የሚኖር ነው ። ሃይማኖት ያለውና መታመኑ የጸና ነው ። ለአደራ የሚበቃና ሥራውን በትጋት የሚፈጽም ነው ። እግዚአብሔርን ማወቅ ያለበት እውቀት ትሑትና ገና ለማወቅ የሚኖር ነው  ።
አለባበስህ ተስተካክሎ ኑሮህ ከተዘባረቀ ፣ ሥልጣኔ ገብቶህ የሕይወት ውል ከጠፋህ ፣ ብዙ ደርጅቶችን እያስተዳደርህ ቤትህ ከሸፈተብህ ፣ አገር እየገዛህ መንፈስህ ካመጸብህ መፍትሔው እግዚአብሔርን አሁንም አሁንም ማወቅ ብቻ ነው ። እግዚአብሔርን ማወቅ በራሱ ደስታ አይሆንህም ፣ በእግዚአብሔር እንደ ታወቅህ ስታውቅ ያን ጊዜ በዘላለም እቅፍ ታርፋለህ ።
ወደ ክርስቶስ መገስገስ 4
ተጻፈ በአዲስ አበባ
መስከረም 11 ቀን 2011 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም