የትምህርቱ ርዕስ | ከሁሉ በፊት

“እንግዲህ እግዚአብሔርን በመምሰልና በጭምትነት ሁሉ ጸጥና ዝግ ብለን እንድንኖር ፥ ልመናና ጸሎት ምልጃም ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረጉ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ ።” /1ጢሞ. 2፡1-2 ።/
እግዚአብሔር በመኳንንት የሚፈርድ አምላክ ነው ። መኳንንት የሕዝብ ፈራጆች ናቸው ። እግዚአብሔር በሚፈርዱት ላይ የሚፈርድ የመኳንንት አለቃ ነው ። ነገሥታት ከበላያቸው ያለው ሕዝብ ሳይሆን እግዚአብሔር ነው ። ስለዚህ በቅን ሊያስተዳድሩ ፣ በርትዕ ሊፈርዱ ይገባቸዋል ። ይልቁንም ሥልጣን ኮንትራትና ኪራይ በሆነበት በዛሬው ዘመን አጭር ዘመናቸውን በክብር ሊፈጽሙት ይገባል ። ኮንትራት በመሆኑ የሚያልቅ ነው ፤ ኪራይ በመሆኑ አከራዩ ጌታ እንደ ፈቀደ የሚያረዝመው ነው ። ነገሥታት በአጭር የሥልጣን ዘመን ዘላለማዊ ታሪክን ወይ በደግ አሊያም በክፉ ይጽፋሉ ። ብዙ ሰው ለአንድ ቀን ምነው ሥልጣን በኖረኝ ይላል ። ለሥልጣን አንድ ቀንም ብዙ መሆኑን የሚያሳይ ነው ። ለንጉሥ አንድ ቀን እንደ ሺህ ዓመት ትረዝማለች ፤ የሺህ ዓመት ልማትና ጥፋትም በአንድ ቀን ይፈጽማልና አንድ ቀን በሥልጣኑ ፊት እንደ ሺህ ዓመት ነች ። በሁለተኛው ዓለም ጦርነት በጃፓን በሂሮሽማ ከተማ ላይ የተጣለው የአቶሚክ ቦምብ እ.አ.አ ነሐሴ 6 ቀን 1945 8፡15 ደቂቃ ላይ የወደቀ ሲሆን በዚህ ቅጽበት ከተማይቱ ወድማለች ፤ 70 ሺህ ሕዝብም ሞቷል ። የአቶሚክ ቦምቡ ባደረሰው የጨረር አደጋ ቀስ በቀስ 70 ሺህ ሰዎች አልቀዋል ። ይህ የነገሥታት የአንድ ቀን ውሳኔ የወለደው ነው ። የሥልጣን ዘመን አጭር ቢሆን እንኳ የሺህ ዓመት ቅራኔን ለመፍታት ይረዳል ፤ የሺህ ዓመት ጠባሳን ለማስቀመጥም አቅም ይሆናል ።

ንጉሥ ዳዊት፡- “ለንጉሥ ከቀን ላይ ቀን ትጨምራለህ” ይላል ። /መዝ. 60፡6 ።/ ይህን የሚናገረው በመገለጥ ብቻ ሳይሆን በንግሥናው ውስጥ በማለፍም ነው ። ንጉሥ ሁሉን ቢያዝም ለራሱ ግን አንድ ቀን መጨመር አይችልም ።በንግሥናው አንድ ቀን በዚህ ዓለም ላይ መቆየት ወይም ወደ ኋላ መቅረት አይችልም ። እግዚአብሔር ሁሉንም በሞት እኩል አድርጎታል ። ስላለህ አትኖርም ስላጣህ አትሞትም የሚባለው ለዚህ ነው ። ንጉሥ በአንድ ቀን ውስጥ ብዙ ጥያቄዎችንና ውሳኔዎችን ሲያሳልፍ የሚውል ነውና አንድ ቀን ለንጉሥ ብዙ ናት ። በየቀኑ የዕድሜ ኮንትራት የሚታደስልን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው ።  በዕድሜ ምጽዋት እኛና ንጉሡ አንድ ነን ።
 
በብሉይ ኪዳን ከሚቀርቡት አምስት መሥዋዕቶች አንዱ የኃጢአት መሥዋዕት ነው ። የኃጢአት መሥዋዕት የሚያቀርቡት ሰዎች ማንነትና የመሥዋዕቱ መጠን ተገልጦአል ። ዘሌዋ. 4 ይህን ይገልጻል ። አቅራቢዎቹ አራት ሲሆኑ፡- ካህኑ ፣ ማኅበሩ/ምእመናን/ ፣ መኰንኑና ዜጋው ናቸው ። ካህኑ የሚያቀርበው መሥዋዕት ወይፈን ነው ። ማኅበሩም ወይፈን ያቀርባል ። መኰንኑ ተባት ፍየል ያቀርባል ። ዜጋውም እንስት ፍየል ያቀርባል ። የወይፈን ዋጋ የዛሬው ዘመን ግርድፍ ግምት ብንሰጥ 10 ሺህ ብር ይሆናል ። ተባት ፍየል ሦስት ሺህ ብር ሲሆን እንስት ፍየል ሁለት ሺህ ብር ይሆናል ። የካህኑና የምእመኑ የኃጢአት መሥዋዕት አንድ ዓይነት ነው ። ምእመናን በካህናት ኃጢአት ሊጽናኑ ቢችሉም ሁለቱም የሚያቀርቡት ግን አንድ ዓይነት ዋጋ ነው ። ካህኑና ምእመኑ በአማኝነት አንድ ናቸውና ። የሚለያዩት በሥራ ድርሻ ነው ። ካህኑም ምእመኑም ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡት በአማኝነት ነው ። የመኰንኑና የዜጋው መሥዋዕት ግን ቀለል ያለ ዋጋ ያለው ነው ። ቢሆንም ከዜጋው መኰንኑ የበለጠ ተጠያቂ ነው ። ከአገር መሪዎችና ከዜጎች በላይም ካህናትና ምእመናን ተጠያቂ ናቸው ።
ሐዋርያው ጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ወይም ምእመናን ስለ ነገሥታት ያለባቸውን ግዴታ እየተናገረ ነው ። “እንግዲህ እግዚአብሔርን በመምሰልና በጭምትነት ሁሉ ጸጥና ዝግ ብለን እንድንኖር ፥ ልመናና ጸሎት ምልጃም ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረጉ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ ።” 1ጢሞ. 2፡1-2
አንድ ክርስቲያን እንዴት መኖር አለበት ከተባለ እግዚአብሔርን በመምሰል ፣ በጭምትነት ፣ ጸጥና ዝግ ብሎ ነው ። ይህ እንዲሳካ ግን ለሰዎች ሁሉ ለነገሥታትና ለመኳንንት ልመና ፣ ጸሎት ፣ ምልጃም ፣ ምስጋናም ሊደረጉ ይገባል ።
እግዚአብሔርን መምሰል ከእግዚአብሔር የተወለዱ ሰዎች የሚያሳዩት መልክ ነው ። ሰው አስቀድሞ ሲፈጠር በአርአያ ሥላሴ ስለ ተፈጠረ የእግዚአብሔር የመልኩ ነጸብራቅ ነው ። ሰው ትንሹ ቅዱስ ፣ ትንሹ ጌታ ነው ። መስተዋት ንጹሕ ሲሆን ብቻ ብርሃን ያስተላልፋል ። እንዲሁም ንጹሕ ልብ ስንይዝ የእግዚአብሔርን መልክ ለዓለም እንገልጣለን ። ሰው የተፈጠረው እግዜር በምድር ተብሎ ሕይወቱ እንዲወደስ ነው ። የእግዚአብሔር መልክ ፍቅር ፣ ርኅራኄ ፣ ይቅር ባይነትና ምሕረት ነው ። ይህን እንዳንገልጥ ግን ብዙ ክፉ ሰዎችና ክፉ ነገሥታት እንቅፋት ሊሆኑብን ስለሚችሉ ለሰዎች ሁሉና ይልቁንም ለነገሥታት መጸለይ ይገባል ።
ጭምትነት የምእመናን መልክ ነው ። ጭምትነት የእግዚአብሔርን ክብር የዓለምን ከንቱነት ከመረዳት ይመነጫል ። ሲያዩት ደስ የሚያሰኝ ምእመን ጭምት የሆነ ነው ። ጭምት እግዚአብሔርን ተሸክሞ የሚዞር መሆኑ ይታወቃል ። ጭምት ለመሆንም ግን በዙሪያችን ያሉ ሰዎችና በበላያችን ያሉ ሹሞች ወሳኝ ናቸው ። በክፉ ሰዎች ተሳዳቢ የሚሆኑ ፣ በክፉ ነገሥታት ጫካ የሚገቡ አማኞች ጥቂት አይደሉም ። ስለዚህ ጭምት ሁኖ ለመኖር ስለ ሁሉ መጸለይ ይገባል ።
ጸጥታ ክርስቲያኖች የሚታወቁት ነው ።      ጸጥታ ድምፅ አለው ። ጸጥታ ይናገራል ። የሚናገሩ ሰዎች ጸጥታ ላይኖራቸው ይችላል ። ጸጥ ያሉ ሰዎች ግን እየተናገሩ ነው ። ጸጥታ የክርስቶስ ሰላም ምልክት ነው ። የሚጮኽ ውስጡ የሚጮኽበት ነው ። ጸጥ ለማለት ግን ዙሪያው ሰላም መሆን አለበት ። ስንቱ ጸጥተኛ እየጮኸ እንደሆነ እያየነው ነው ። ለዚህ መድኃኒቱ  ጸሎት ነው ።
ዝግታ የክርስቲያን መልክ ነው ። ክርስቲያንነት መታወቂያው ጠባይ እንጂ የአባልነት ደብተር አይደለም ። ቀደም ቀደም ማለት አደጋ አለው ። ችኮላ ረግጦ ሲያይ ፣ ዝግታ ግን አይቶ ይረግጣል ። በዝግታ ለመራመድም ሆነ ለመኖር ዙሪያውና መንግሥቱ ሰላም መሆን አለበት ። ለዚህም መጸለይ ግድ ይላል ።
ልብ አድርጉ ሐዋርያው ጳውሎስ ይህን መልእክት በሚጽፍበት ጊዜ የነበረው ንጉሥ ኔሮ ቄሣር ነው ። ሐዋርያውን አስሮ ከለቀቀው በኋላ ቀጥሎ ይገድለዋል ። ሐዋርያው ጸልዩ የሚለው ለዚህ ንጉሥ ነው ።
ከሁሉ በፊት ለነገሥታት ለሚመሩን ፣ ለመኳንንት ለሚያስተዳድሩን መጸለይ ይገባል ። እኛ በጸሎት ካልጋረድናቸው የሰይጣን ፍላጻ ያገኛቸዋል ። የሚያጠፉትም በአቅማቸው መጠን ነው ። ድንጋይ የያዘ ያንን ሲወረውር ኒውክለር የጨበጠም ያንኑ ይወረውራል ። ጥፋት እንደ አቅም ነው ። የነገሥታት ሰላም መሆን የሕዝብ ሰላም ነው ።
ለሰው ሁሉና ለነገሥታት የሚደረገው፡- ልመናና ጸሎት ምልጃም ምስጋናም” ነው ። ልመና እግዚአብሔር እንዲረዳቸው ነው ። ጸሎት እኛን ሲያዩ ሰላም እንዲሰማቸው ነው ። ምልጃ ከክፉ ሁሉ እንዲጠብቃቸው ነው ። ምስጋና ሰዎችንና ነገሥታትን የሰጠን እግዚአብሔር መሆኑን አውቀን በደስታ እንድናወድስ ነው ። ሰዎችና ነገሥታት በረከቶቻችን እንዲሆኑ ጸሎት ፣ ልመና ፣ ምልጃ ፣ ምስጋና ሊኖር ይገባል ።
እግዚአብሔር በብዙ በረከት ይባርካችሁ !
1ጢሞቴዎስ /23/
ታኅሣሥ 15 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም