መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » አዲስ ኪዳን » የማቴዎስ ወንጌል » ከነቢይ የሚበልጠው መጥምቁ ዮሐንስ

የትምህርቱ ርዕስ | ከነቢይ የሚበልጠው መጥምቁ ዮሐንስ

(ማቴ. 11 ፡ 9)

የዘመን መለወጫ ቅዱስ ዮሐንስ ተብሎ ይጠራል ። ይህ በሁለት ምክንያት ነው ። የመጀመሪያው ዮሐንስ መጥምቅ በሰማዕትነት ያለፈው መስከረም ሁለት ቀን ነው ። በዚህ ምክንያት መስከረም አንድ “ቅዱስ ዮሐንስ” ተብሎ ይጠራል ። ሁለተኛው ዮሐንስ መጥምቅ የብሉይ ኪዳን መጨረሻ የአዲስ ኪዳን መጀመሪያ ነው ። የነቢያት መጨረሻ ፣ የሐዋርያት መጀመሪያ ይባላል ። አሮጌው ዘመን አልፎ ወደ አዲሱ ዘመን ስንሻገር ፣ የሽግግር አገልጋይ በሆነው ነቢይ “ቅዱስ ዮሐንስ” መባሉ ተገቢ ስያሜ ነው ።

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ብዙ ስሞች አሉት ። ነቢይ ይባላል ። ስለ መሢሑ መምጣት ተናግሯል ። ሕዝብን ለንስሐ ጋብዟል ። ስለ ፍትሕ መጓደል ነገሥታትን ገሥጾአል ። ሕዝብን አጽናንቷል ። የነቢያት ተግባር የሚመጣውን ክርስቶስ መግለጥ ፣ ሕዝብን ለምጽአተ ክርስቶስ ማሰናዳት ነው ። በደለኛውን ለንስሐ መጋበዝ ፣ ነገሥታትን መንገድ መምራት ፣ ሁሉን በእኩል ዓይን አይቶ መገሠጽ ነው ። የነቢይን ስም የሚወድዱ የነቢይን ሥራ ግን የማይወድዱ ብዙ ናቸው ። ነቢይነት ጸጋም ፣ ጥሪም ነው ። የሥራ መስክ ፣ ራስን የሚቀቡበት የዘፈን ውድድር አይደለም ። ነቢይ የሕዝብ አጫዋች ፣ የቀለድ መሥሪያ ቤትም አይደለም ። ነቢይ ዓለምን የናቀ ፣ ከንብረት ውድድር የራቀ ፣ በመንፈስ የረቀቀ ፣ ወደ ሰማይ የመጠቀ ነው ። ዕድል ፈልጎ የሚቀማ ሳይሆን ዕድል እያለው እንደ ሙሴ ቤተ መንግሥትን ንቆ ምድረ በዳ የሚመሽግ ፣ እንደ ኢሳይያስ አዝማደ መንግሥትነትን ተጸይፎ የሕዝብ ወገነተኛ የሚሆን ነው ።

ክርስቶስ ስለ መጣ በዚህ ዘመን የነቢይን ተግባር ሰባኪ ይዞታል ። የመጨረሻውን መልእክት በውድ ልጁ ስለሰማን በዚህ ዘመን ነቢይ አያሻም (ዕብ. 1 ፡ 2) ። አንድም ነቢይ “እንዲህ ዓይነት ልብስ የለበስህ” እያለ የግምት ሥራ አልሠራም ። በዚህ ዘመን ክርስትናን ለማቃለል ፣ ሰውን የከሀዲነት ወዶ ገብ ለማድረግ የተነሡ አጽራረ ክርስቶሶችን እያየን ነው ። የኢየሱስን ስም እየጠሩ ሲጨፍሩ ፣ ቅዱሳንን ሲያቃልሉ ፣ ተራ ንግግር ሲናገሩ እያየን እየሰማን ነው ። የክርስቶስ ስም መቀለጃ ሲሆን ክርስቲያን ተብለን ተባባሪ ሆነን እንስቃለን ። በክርስትናው ላይ የተጋረጠውን አደጋ ግን አልተገነዘብንም ። በወንጌል ስም የገባው የምዕራባውያን እንቅስቃሴ መጀመሪያ ክርስትናውን ያቃልላል ፣ ቀጥሎ ባዶ እጅን አስቀርቶ ከሀዲ ያደርጋል ። ቅዱሳንን ስለናቁ እነዚህን ሰዎች ስንነቅፍ እንውላለን ፣ ክርስቶስንም እያቃለሉት ነውና ተዉ ልንል ይገባናል ። የቤተ ክርስቲያን መሠረትም ጉልላትም ኢየሱስ ክርስቶስ ነውና ።

መጽሐፍ ቅዱስን ፣ አማናዊውን ክርስቶስን ለማስጠላት በዓላማ እየሠሩ ያሉ ፣ ክርስትና ላይ እንዲህ ሲቀልዱ እያየን ተግባራቸውን መሳቂያና ቀን መግፊያ እያደረግን በመሆናችን እግዚአብሔር ይጠይቀናል ። ሰውን የምኞት ዛር እንዲቆራኘው ፣ ያልሠራበትን እንዲዘርፍ ፣ የእርሱ ያልሆነውን እንዲከጅል የሚያስተምሩ የብልጽግና ወንጌል ሰባኪዎች ፣ ለምድሪቱ ጭንቀት ሆነዋል ። የአፍሪካ ወንጌል ተብሎ የሚጠራው “ታገኛለህ” የሚል ስብከት ነው ። ድሀውን ማጓጓት አገልግሎት አይደለም ። ለድሀ ለመስጠት የሚፈተኑ ፣ ድሀን ግን “እንዲሁ ታገኛለህ” በማለት በምኞት የሚያመክኑ በነቢይ ስም ራሳቸውን የሚጠሩ ናቸው ። ነቢይ ነኝ የሚል በግድ ተአምራት ያደርጋል የሚል አመለካከትም እንዲዳብር አድርገዋል ። ነገር ግን ነቢይ የሆነው ዮሐንስ መጥምቅ እንዲህ ተብሎ ተነግሮለታል ። “ብዙ ሰዎችም ወደ እርሱ መጥተው፡- ዮሐንስ አንድ ምልክት ስንኳ አላደረገም ፥ ነገር ግን ዮሐንስ ስለዚህ ሰው የተናገረው ሁሉ እውነት ነበረ አሉ ።” ዮሐ. 10 ፡ 41 ።

ወደ እግዚአብሔር ቤት የምንመጣበት ዓላማ እቤታችን የደበቅነውን ለማወቅ አይደለም ። የምናውቀውን ሲነግሩን መደሰት ሞኝነት ነው ። የማናውቀውን መፍትሔና ነገረ እግዚአብሔር ቢነግሩን የተሻለ ነው ። ብዙዎች በሐሰተኛ ነቢይ ነን ባዮች ፣ በሐሰተኛ ፈዋሾች ትዳራቸው ፈርሷል ። ድናችኋል ተብለው በበሽታቸው ፈጥነው ሞተዋል ። አንዳንዶችም የተተነበየልኝ አልደረሰም በማለት እግዚአብሔርን ተቀይመውና ክደው ወደ ኋላ ተመልሰዋል ። “እግዚአብሔር ብሏል” አሏቸው እንጂ እርሱ ለማለቱ እርግጠኛ አይደሉም ። እግዚአብሔር በዚህ ዘመን በተጻፈው ቃሉ እንጂ በርግጠኝነት ከቃሉ ውጭ የሚናገርበት ሰው የለም ። ቢናገር እንኳ የተጻፈውን ቃል አጽድቆ እንጂ ሽሮ አይናገርም ። ክርስትና መመዘኛ አለው ። በየዘመናቱ የአቋም ለውጥ የሚያደርግ ፣ በለውጥ ላይ ያለ ሃይማኖት አይደለም ። ክርስትና ሰውን ይለውጣል ፣ ያድሳል እንጂ ትምህርቱ አይለወጥም ፣ ሃይማኖቱም አይታደስም ። የድሮ ጠንቋይ አፍሮ በሰባት መጋረጃ ተከልሎ ይጠነቁል ነበር ። ቢያንስ ሐፍረት ያለው ስልጡን ይመስላል ። ዛሬ ግን በአደባባይ ተራ ጥንቆላ ሲካሄድ ይታያል ። የሰው ገመና የገቢ ምንጭ ሆኗል ። የራስን ዝና ለመካብ የሌላውን ዝና መናድ ለሐሰተኞቹ ጭንቅ አይደለም ።

ከፈሪሀ እግዚአብሔር ይልቅ ፈሪሀ ሰይጣን በሕዝባችን ላይ ነግሦአል ። ለሁሉም ነገር ተጠያቂው ሰይጣን ነው ተብሎ ይነገራል ። የስካር ፣ የዝሙት መንፈስ ይባላል ። የሰው ተጠያቂነት ችላ ተብሏል ። ሰው ነጻ ፈቃድ ያለው ፍጡር መሆኑ ተዘንግቶ የስስት መንፈስ ፣ የመበተን መንፈስ እየተባለ ሁሉንም ነገር ማመናፈስ የዘመናችን መገለጫ ሆኗል ። በሚለብሱት ልብስ ፣ በሚሞቁት እሳት ላይ ሳይቀር አጋንንት ያርፋሉ ተብሎ ስለሚታሰብ ሁሉንም ነገር መገሠጽ ፣ ራስን በማሸበር መኖር እያየለ መጥቷል ። ዓለማውያንና ከሀድያን በሰላም እየተኙ አማኝ ነኝ የሚለው ግን ሲገሥጽ ፣ ሲፋለም ይውላል ፣ ያድራል ። የጦር ሜዳ ትራፊ ቃላትም የሐዋርያት ቃል እስኪመስሉ ይደመጣሉ ። ይወጋ ፣ ይውደም ፣ ይደምሰስ …. የሚሉ ቃላት የት መጡን ይተርካሉ ። በውስጥ በውጭ ትግል ውስጥ ያለች ቤተ ክርስቲያናችን አሁንም እውነት የሚናገሩና የሚገሥጹ ፣ የነቢይ ሥራና ሞገስ ያላቸው አባቶች ያስፈልጉአታል ።

አቤቱ አድነን ! ፈጥረህ ላልፈጠረ አትተወን !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 27 ቀን 2016 ዓ. ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም