መግቢያ » ትረካ » ከጣራዬ በታች አትግባ » ከጣራዬ በታች አትግባ/2/

የትምህርቱ ርዕስ | ከጣራዬ በታች አትግባ/2/

“ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም፡- ‘እኔ መጥቼ እፈውሰዋለሁ’ ብሎ ፈጣን መልስ ሰጠኝ ። ባሪያዬን እወደውና እንከባከበው የነበረው ዝናን ፈልጌ ፣ ተራማጅ አስተሳሰብ ያለው ሰው ለመባል ወድጄ አልነበረም ። ፍቅር የመጣብንና የሚወድቅብን ነገር ነው ። ፍቅር ከመዐርግ ፣ ከኑሮ ደረጃ ብቻ ሳይሆን ፍቅር ከሞት በላይ አሸናፊ ነው ። ፍቅርን ኃያል ያሰኛት የእግዚአብሔር ልጅ የሰው ልጅ እንዲሆን ግድ ስላለችው ነው ፣ በዚህም አላበቃችም እስከ ሞት አደረሰችው ። ከልጅነቴ ጀምሮ ሰውን ልንመራው እንጂ ልንገዛው አይገባም ብዬ አስብ ነበር ። በታላቋ ሮማ ስልጣኔ ውሾች ወደ ቤተ መንግሥት ተጠግተዋል ፣ ከነገሥታት ግብር ላይም ውሾችን ማየት የተለመደ ነው ። እንዲነገርልን የምንፈልገው ግን እንኳን ለሰው ለውሻም መብት ቆመናል የሚለው ነው ። እውነቱን ግን ስናየው የሰውን ቦታ ለውሾች ሰጥተን ራሳችንን እያታለልን መሆናችን ነው ። ሮማውያን የሰውን ዘር ሳይሆን ሮማዊ ሰውን ብቻ ያከብራሉ ። እግዚአብሔር የፈጠረውን ሰው ሳይሆን በቋንቋና በቤተሰብ የሚመስላቸውን ብቻ ይወዳሉ ። ለዚህ ነው የባሪያ ፍንገላ በግዛታችን እየበዛ የመጣው ። ሰው እንደ ከብት ታጉሮ ሲሸጥ ከማየት የበለጠ ምን የሚያሳዝን ነገር አለ ? ባሪያዬን የምወደው ፣ ያገለገለኝን የማገለግለው ፣ ልጄ ብዬም የምጠራው የነጻነት አስተሳሰብ ከእኔና ከቤቴ ስለሚጀምር ነው ። በአደባባይ ስለ ነጻነት የሚያወሩ ቤታቸውን ግን ቅኝ የያዙ ብዙ ሰዎች አሉ ። ስለ ሴቶች ነጻነት እያወሩ በቤት ሚስታቸውን የሚያስጨንቁ ፣ ሰው እኩል ነው እያሉ ባሪያ የሚፈነግሉ አያሌ ናቸው ።

ክርስቶስም ‘እኔ መጥቼ እፈውሰዋለሁ’ ሲለኝ ታላቅ ነገር በውስጤ ተሰማኝ ። እቤታችን ትተናቸው የመጣናቸውን ሕሙማን በክርስቶስ ፊት በጸሎት ስናቀርባቸው ፈውስን ያገኛሉ ። ያልተቀበልነው ስላልጸለይን ነው ። እግዚአብሔር ለእኔ ብለው ከሚለምኑት ለእገሌ ብለው ሲለምኑት ፈጥኖ ይሰማል ። ፍቅር ነውና በፍቅር ይለመናል ። ስለ ሰው መጸለይ ምክንያቱ ፍቅር ብቻ ነው ። እኔ ስለ ባሪያዬ አደባባይ ወጣሁ ፣ ክርስቶስ ደግም ባሪያዬን ሊፈውስ ወደ ጓዳዬ እመጣለሁ አለ ። እርሱ በእልፍኝ የለመኑትን በአደባባይ ይመልሳል ፣ በአደባባይ የለመኑትን በእልፍኝ ይመልሳል ። ችግሬ ከቤት ሳይወጣ ሊፈውስልኝ ሲችል ለምን ዛሬ በአደባባይ ፈወሰው ? ብዬ አሰብሁ ። በአንዱ ችግር ብዙዎችን ለማስተማር ነው ብዬ በአንደኛው ልቤ መለስሁ ። በክርስቶስ ንግግር ውስጥ ብዙ ነገሮችን ተማርሁ ። ‘እኔ’ ብሎ በመናገሩ ሙሴን ‘እኔ ነኝ’ ያለው እርሱ መሆኑ ታወሰኝ ። እኛ እኔ ብለን ብንናገርም የተናገርነውና የሆነው የተለያየ ነው ፤ እርሱ ግን እኔ ባዩ እርሱ ነው ። ‘አንተ ግን ያው አንተ ነህ’ ብዬ ዝቅ አልኩኝ ። ‘መጥቼ’ የሚለው ቃሉ ደግሞ እኔ ባዩ እርሱ ትሑት መሆኑን አሳየኝ ። ‘እፈውሰዋለሁ’ በማለቱ ደግሞ እርሱ የሚሞክር ሳይሆን የሚያድን መሆኑን ፣ ማዳኑም ሂደት የሌለበት ቅጽበታዊ እንደሆነ ገባኝ ። እርሱ አምላክ ካልሆነ በቀር እንዴት እንዲህ ሊል ይችላል ? 
ሴቷ ጋዜጠኛ ንግግሩን አቋረጠችው ። ስሜት ውስጥ ገባች ። የእርስዋ የታመመ የቤቷ ነገር ትዝ አላት ። ቃለ ምልልሱ ስብከትና የናፍቆት ወሬ መሰለ ። ‘እኔ መጥቼ እፈውሰዋለሁ ማለቱ የሚገርም ነው ። ማዳንና አለማዳናቸው ሳይታወቅ ሐኪሞች ካልመጣችሁ ይላሉ ። ሄደንም በፍቅር ለመቀበል ይቸገራሉ ። ምን ዓይነት ትሑት አዳኝ ነው’ አለች ። እርሱም ቆይ ልቀጥልልሽ በማለት ትረካውን ፣ የተደረገለትን ቀጠለ ። የሚናገረው ስለራሱ መዳን ይመስል ነበር ። ከታማሚው የአስታማሚው በሽታ ይበረታል ፣ ፈውሱም ከተፈዋሹ የአስታማሚው ፈውስና ደስታ ይበልጣል ። በሽተኛውስ የሰጠውን የሚችልበት ጸጋ አብሮት አለ ። አስታማሚው ግን እምነት ካልረዳው በአሳብ ይወዘወዛል ፣ በግምት ይሰቃያል ፣ እንዲህ ቢሆንስ እያለ በጥንቆላ አሳብ ይጨነቃል ። መቶ አለቃው የተሟላ ቁመናና ዲሲፕሊን ብቻ ሳይሆን የንግግር ችሎታም የነበረው ፣ እያስረገጠ የሚናገር ፣ እየመጠነ የሚሰነዝር ነበር ።
‘እኔ መጥቼ እፈውሰዋለሁ’ ሲለኝ ለእኔ ታላቅ ክብር ቢሆንም ሁለት ነገሮች ትዝ አሉኝ ። የመጀመሪያው እርሱ ይገባበት ዘንድ ቤቴን ብቁ ሁኖ አላገኘሁትም ። ሁለተኛው እርሱ ቻይ ነው ። ቃል ቢናገር ብላቴናዬ እንደሚፈወስ እርግጠኛ ነበርሁ ። ጌታ ሆይ በቤቴ ጣራ በታች ልትገባ አይገባኝም ነገር ግን ቃል ብቻ ተናገር ብላቴናዬም ይፈወሳል አልኩት ። በእርሱ የቅድስና ብርሃን ፊት ስቆም ማንነቴ ታየኝ ። ፍቅሩም ለንስሐ ጋበዘኝ ። ከማንም ሰው ጋር በቅድስናም በኃጢአትም እኩል ነን ብዬ አምን ነበር ። አሁን ግን ፊቱን ሳያጠቁር የተቀበለኝን ፣ በሥልጣን ቃል በትሕትና ያናገረኝን ፣ ለእኔ ሕይወት ፣ ለሞቴ ሞት የሆነውን እርሱን ወደ ቤቴ በድፍረት መጋበዝ አቃተኝ ። ከጣራዬ በታች ብዙ ጨለማ አለ ። በደጅ ምኩራብ ያሠራ ፣ ሕዝባችንን የሚወድ እያሉ የአይሁድ ራቢዎች ቢያሞግሱኝም እኔ ግን በቤቴ የረካሁ አልነበርሁም ። በደጅ ብስቅም በቤቴ ግን ያንን ለመድገም አቅም ያንሰኝ ነበር ። እንደ ማሽላ እያረሩ መሳቅ የእኔ መገለጫ ነበር ። ኑሮዬን ገነት ላደርገው እፈልጋለሁ ። ጥሩ ሰው መሆን ግን ላለመጎዳት ዋስትና አይሆንም ። እንደውም መልካም ሰው ስንሆን በብዙ ለመጎዳት ዝግጁ መሆን አለብን ። በዋጋ የሚያፈቅሩ በበዙበት ዓለም ነጻ ፍቅር ጥርጣሬ ውስጥ ይወድቃል ። ትዳሬ ከሰው ጋር ሳይሆን ከመልአክ ጋር የጀመርሁት ጉዞ አድርጌ ስዬው ነበር ። ከልኩ በላይ መጠበቄ ቤቴን የሁከት መድረክ አደረገው ። ከጣራዬ በታች ያሉ እንደ እኔ እንዲያስቡ እፈልግ ነበር ። እነርሱ ግን እንደ እኔ ሳይሆን እንደ ራሳቸው ናቸው ። እንደ እኔ እኔም አልሆንሁም ብዬ የምጽናናበት ጊዜ ብዙ ነው ።
ደግሞም የራሴን ትንሽ ሥልጣን አስታወስሁና ጌታዬን ለምን አደክመዋለሁ ? አልኩኝ ። እኔ መቶ ሰው የማዘዝ አቅም አለኝ ። ና የምለው ይመጣል ሂድ የምለው ይሄዳል ። ጌታዬም በደዌያትና በአጋንንት ላይ ሥልጣን አለው ። ቄሣር ሮም ተቀምጦ ሶሪያ የሚያዋጋን በመገኘቱ ሳይሆን በቃሉ ነው ። ቃል ይህን ያህል አቅም ካለው የመለኮት ቃልማ የበለጠ አቅም አለው ብዬ አመንሁ ። ጌታዬም ይህን እምነቴን ሲሰማ ተደነቀ ። በእስራኤልም እንዲህ ያለ እምነት አላገኘሁም አለ ። በእርሱ ስደነቅ ልቤ ጠነከረ ፣ መንፈሴ ጎለመሰ ፣ የተጫነኝ ቀንበር ተሰበረ ። ጌታዬ አድናቂ ነው ። በሚሰድቡኝ ካዘንሁ በሚያደንቀኝ ጌታ መደሰት አለብኝ ። እርሱ ደግሞ ክቦ መናድ አያውቅበትም ።
ብላቴናዬም ከዚያች ሰዓት ጀምሮ ተፈወሰ ። ከቤቴ ስወጣ ቤቴ በኀዘን ድባብ ተውጦ ነበር ። አሁን ግን የደስታ ብርሃን ተለኩሶበት ገጠመኝ ። ብላቴናዬ ተፈወሰ ። ዛሬ ወደ ሮም እየገባሁ ሳለሁ ብዙ የሮም ወጣቶች በመንፈስ እንደ ታመሙ ተሰማኝ ። ወልዶ የሚደሰተውን ያህል ወልዶ የሚሰጋ እንዳለ ሰረገላውን ያከራየኝ ነጂ ነግሮኛል ። የእኔ ብላቴና የተፈወሰው በጸሎት ነው ። እነዚህም ወጣቶች የሚፈወሱት በጸሎት ነው ብዬ አምናለሁ ።
ጋዜጠኞቹ ዓይኖቻቸው በእንባ ተሞላ ። በዓይነቱ ልዩ የሆነውን ተአምር ለመዘገብ በመብቃታቸው ደስታቸው ልዩ ሆነ ። ገና ቤቱ ሳይገባ ስላደከሙት ምስጋና አቀረቡ ። እርሱ ግን የጌታዬን ማዳን ባወራሁ ቊጥር ኃይሌ ይታደሳል ፣ ጉልበት የሚጨርስ የዓለም ወሬ ነው አላቸው ።
ተፈጸመ
ሰኔ 11 ቀን 2011 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም