መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ከፊቴ ገለል በል !

የትምህርቱ ርዕስ | ከፊቴ ገለል በል !

የጻድቃንን ጥበብ መታዘዝን ፣ ዓለሙን ከሠራው ጋር መስማማትን እንዳልመርጥ ፣ አላሳልፍ ያልከኝ እልኸኝነት ከፊቴ ገለል በል ። በሄደበት ሁሉ ጌታዬን እንዳልከተል ደስታዬን የምትዋጋ ፤ በቤተ ልሔም ልደቱ የድሀ ልጅነቴን ፣ በግብጽ ስደቱ በወገን መገፋቴን ፣ በናዝሬት ዕድገቱ የቀደመ ታሪኬን ፣ በዓርብ መከራው የተዛባ ፍርዴን እንዳልቀበል የምታደርገኝ አንተ እኔነት ከፊቴ ገለል በል ። የተጠሩትን በር ላይ ቆሜ እንድመልስ ፣ የተመረጡት ላይ ጭቃ እንድለጥፍ ፣ የተወደዱትን እንዳጠለሽ የምታደርገኝ አንተ ቅንዓት ከፊቴ ገለል በል !

የሞላውን ምስጋና እንዳጎድል ፣ የበዛውን ውዳሴ እንዳሳንስ ፣ የተደረገልኝን እንዳላይ ፣ የተሰቀለውን ጌታ እንዳላስተውል የምታደርገኝ አንተ ማጉረምረም ከፊቴ ገለል በል ። ለታመነልኝ አምላክ እንዳልታመን ፣ የወደዱኝን እንድጠላ ፣ ያከበሩኝን እንዳዋርድ ፣ የቀረቡኝን እንድርቅ ፣ ትላንተ የሰጡኝ ላይ እንድጨክን የምታደርገኝ አንተ ከዳተኝነት ከፊቴ ገለል በል !

በእግዚአብሔር መቻል እየተጠራጠርሁ ፣ በራሴ መቻል እንድታመን የምታደርገኝ ፣ የተዋረደውን ሰዋዊ ፍልስፍና ከመለኮት መገለጥ ጋር ቁመት የምታለካካኝ አለማመን ሆይ ከፊቴ ገለል በል ። ድንቅ ያደረገውን ኢየሱስ ክርስቶስን ስሙን እንዳቃልል ፣ ደሙን እንዳላከብር ፣ ሞቱን እንዳልናገር ፣ ትንሣኤውን እንዳልመሰክር የምታደርገኝ አንተ ይሉኝታ ከፊቴ ገለል በል ። ስለ አቋም ትቼ ስለ አቋቋም ፣ ስለ ማወቅ ችላ ብዬ ብዬ ስለ መታወቅ ፣ ሥራን ጠልቼ ስፍራን እንድወድ የምታደርገኝ አንተ ከንቱነት ከፊቴ ገለል በል ። በቂም ቋጥረህ ዓይኔን ያጨለምህ ፣ በበቀል አሰማርተህ የአምላኬን ምሕረት ያስረሳህ ፣ የመላእክትን ወዳጅነት ሳይሆን የሰውን ሸርታታነት እንዳስብ የምታደርገኝ አንተ ዓለማዊነት ከፊቴ ገለል !

ጌታ ሆይ ! አንተ በሰማይ ታከብረኛለህና ፣ ሥራዬን ጨርሼ በምድር አከበርሁህ ለማለት አብቃኝ ። የሚሰማ ሁሉ አሜን ይበል !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ተጻፈ ሰኔ 27 ቀን 2015 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም