የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ክረምትና ሞት

“ስለዚህ ምድር ብትነዋወጥ፥ ተራሮችም ወደ ባሕር ልብ ቢወሰዱ አንፈራም።” (መዝ. 45፡2 ።)

የዓለምን ከንቱነት ለመግለጥ የአገራችን ሰዎች እንዲህ ብለው ይገጥማሉ፡-

ምን ጌታ ቢሆኑ ፣ ባለ ዋርዳ በቅሎ ፣ ባለ ማር እሸት ፣
አሽከር ቢያደገድግ ፣ ቀንና ሌሊት ፣
ድጓ ቢተረጎም ፣ ቢነበብ ዳዊት ፣
በቅሎ ቢያሰግሩት ፣ ተጎንደር ይፋት
መቅረቱን አይቀርም ክረምትና ሞት ።

ክረምት ጊዜውን ጠብቆ ይመጣል ፣ ይቀራል ተብሎ አይታሰብም ። ሞትም እንደ ክረምት በጊዜው ይመጣል ። ቢዘገይም ይቀራል ተብሎ አይታመንም ። የትኛውም የኑሮ ደረጃ ሞትን አያስቀረውም ። ሁሉም ወደዚያው ነው ። ስለዚህ ከእግዚአብሔር ውጭ ስሜ ትልቅ ነው ፣ ጀርባዬ ጥብቅ ነው ፣ ጎተራዬ ሙሉ ፣ አሽከሬ እልፍ ነው ብሎ መመካት አይገባም ። በማንኛውም ጊዜ ተነሥቼ ከአዲስ አበባ ኒውዮርክ ፣ ከዳን እስከ ቤርሳቤህ የምበርር ነኝ ብለን ብንመካም ከሞት የሚሸሽግ ዋሻ እስካሁን አልተገኘም ። ክረምት የደረቀውን መሬት ያረሰርሳል ፣ ሞትም ጻድቃንን ከወዳጅ እግዚአብሔር ጋር ያገናኛል ። ያን ቀንም እንባ ከዓይን ይታበሳል !

በዚህ ዓለም ላይ ከሚያደናግሩ ነገሮች አንዱ የተራሮች መሰወር ነው ። ነቢዩ፡- “ተራሮችም ወደ ባሕር ልብ ቢወሰዱ አንፈራም” ብሏል ። በእስራኤል ዘንድ ትልቁ ተራራ ፣ የክብር ሰው ዳዊት ነው ። ዳዊትም ተራሮች ነበሩት ። ሰዎች “የእኔ ጀግና እገሌ ነው ፣ የእኔ ምሳሌ እገሊት ናት” ይላሉ ። እንደ ተራራ የገዘፉ ፣ ከሩቅ የሚታዩ ፣ ይጎድላሉ ተብለው የማይሰጉ ፣ የተጠለላቸውን የማያስነኩ ሰዎች ሊሆኑ ይችላሉ ። ተራሮች የሚሰወሩበት ጊዜ ግን ጥቂት አይደለም ። በጉቦና በሌብነት ምክንያት ተሠሩ የተባሉ ሕንፃዎች ይሰወራሉ ። በውኃ ጥም ሲሰቃዩ የነበሩ የገጠር ሰዎችን ለማርካት የተቆፈሩ የውኃ ጉድጓዶች ይሰወራሉ ። በእርዳታ የተቆፈረ አንድ የውኃ ጉድጓድን ለመመረቅ ሄደን “እዚህ ጋ ነበረ” ብለውን አዝነን ተመልሰናል ። ለሌለው ጉድጓድ ግን ከመጠን ያለፈ ገንዘብ ወጪ ሆኗል ። ያን ቀን የተሰማኝ ሐፍረት ፣ አየሩን ሳይቀር ፈርቼ ተመልሻለሁ ። የጋበዙኝም ጭው ብለው እነርሱን ለማጽናናት ሞክሬአለሁ ። ሕንፃ ሲሰወር ፣ የውኃ ጉድጓዶች ሲጠፉ “የት ነው ያለሁት ? በሕልሜ ነው ወይስ በውኔ ?” ያሰኛል ። ብዙ ያወራንለት ነገር ፣ ለምርቃት ሰው የጋበዝንበት የእጃችን ፍሬ ምትሐት ሆኖ ሲሰወር በሐፍረት አንገት ያስደፋል ።

የእንጦጦ ተራራን ሽቅብ ስናየው እንውላለን ። ይህ ተራራ ድንገት ቢሰወርና ከጀርባው ያለ ከተማ ቢታየን ከመደሰት እንደነግጣለን ። የከፍታዎች መለኪያ ሲጠራ “ከባሕር ጠለል በላይ…” ተብሎ ነው ። አሁን ግን ተራሮች ወደ ባሕር ልብ ተሰወሩ ። ብዙ ሰው የገዛ አእምሮውን የሚጠራጠረው ፣ አለሁ ወይስ የለሁም ብሎ ራሱን የሚደበድበው ተራሮች ሲሰወሩበት ነው ። ቆይ መጣሁ ብለውን ገብተው ፣ በገቡበት ቤት በጓሮ በር የጠፉ ሰዎች ቆመን እንድንውል ፣ በኀዘን እንድንጎዳ አድርገውናል ። ለአገር ምሳሌ ፣ ለትውልድ አርአያ የሚሆኑ ሰዎች ከስፍራቸው ሲታጡ ደንግጠናል ። በዝምታቸው የምናከብራቸው ሲናገሩ “ምነው ዝም ብለው በቀሩ” ብለናል ። እንደ ተራራ የገዘፉብን ብዙ ሰዎች ናቸው ። ከቦታቸው ታጥተው ወንዝ ለወንዝ ሲሄዱ ፣ በጎሣ በሽታ ሲለከፉ እናዝናለን ። ብዙ ያወራንላቸው ፣ “የእኔ ትልቅ” ብለን የእወቁልኝ ማስታወቂያ የሠራንላቸው አንሰው ሲገኙ ፣ ከእነርሱ መውረድ በላይ የእኛ ማመን ያበሳጨናል ።

ይህ ዘመን ተራሮች የሚሰወሩበት ዘመን ነው ። መደልደል ቢሆን እሺ እንላለን ። ወደ ባሕር ልብ ፣ ከልኬት ቍጥር ውጭ ሲሆኑብን ዓለምን እንፈራለን ። ፈላስፎችን የተከተሉ ፣ ምድራዊ ዝነኞችን ያፈቀሩ ፣ በውጫዊ ነገር ለሰው የዘፈኑ ይደነግጣሉ ፣ ይፈራሉ ። ሁሉ ሲንሸራተት ፣ በከፍታው ነዋሪ የሆነ ፣ የዘመናት ዘመን የሆነ ፣ ለዘመኑ ዘመን የሌለው መድኃኔ ዓለም ግን ከፍርሃት ያድናል ። የታመናቸው ሊጥሉን ፣ ያየናቸው ሊሰወሩብን ይችላሉ ። የእውነት መዝገበ ቃላት ያደረግናቸው ፣ “እነርሱ ካሉማ ጨለማም ብርሃን ነው” ብለን የዘመርንላቸው ሊሰወሩ ፣ ሊታጠፉ ፣ በበሉበት ግብር ሊቀሩ ይችላሉ ። ክርስቶስን ካላየን ከክርስቶስ ርስት መድረስ አይቻልም ። የነፍስ መንገድ ረጅም ነውና እርሱን ብቻ መሪ ካላደረግን ፍርሃት ቶሎ ይከበናል ። እግዚአብሔር ረዳታችን ከሆነ ግን ያመነው ቢከዳን ፣ ያከበርነው ቢያዋርደን ጉዞው ይቀጥላል ።

“ልብ እየጠበበ ጨጓራ ሲሰፋ ፣
ታዋቂ ሰው በዝቶ አዋቂ ሰው ጠፋ ።”

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 16 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ